መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የማላይህ ቦታ አጣሁ

የትምህርቱ ርዕስ | የማላይህ ቦታ አጣሁ

 የልብን ጩኸት የምትሰማ ፣ የነፍስን መቃተት የምታደምጥ ፣ የፍጥረት መሸበር ግድ የሚልህ ፣ እረኛ ያጣው መንጋ የሚያሳዝንህ ፣ መጠለያ አጥቶ የሚሮጠው የሚያራራህ ፣ መሪው ተነቅሎ የሚከንፈውን ሠረገላ በዓይንህ ጥቅሻ የምትመራ ፣ የመጨረሻዬ መጣ ላለው መጀመሪያን አክሊል አድርገህ የምትሸልም ፣ ምን ይሉኛል ብሎ ራሱን ያሰረውን ከአሉተኛ ትውልድ የምታድን ፣ የት ልድረስ ለሚለው መሸሸጊያ የምትሆን ፣ ራሱ ላስጠላው ዋጋ የምትሆን አንተ እግዚአብሔር ነህ ። ፍጥረት ሁሉ ይስማ አንተ ያህዌ ነህ ።
ከዓለም ፊት ማጥቆር በላይ ያንተ ፈገግታ ለእኔ ግሩም ነው ። አናውቀውም ተብሎ ከመካድ በላይ ከዘላለም በፊት ባንተ መታሰቤ ለእኔ ልዩ ነው ። ጆሮ አትስጡት ተብሎ ከሚዘመተው በላይ ጸሎቴን መስማትህ ዕፁብ ነው ። እንዳይነሣ እርገጡት ከሚባለው በላይ የተዘረጋልኝ እጅህ ለእኔ ትንሣኤ ነው ። ሌት የማስበው ፣ ቀን የማመላልሰው መኖሬን ነው ። እንደ ኖርሁ አውቃለሁ እንዴት እንደ ኖርሁ ግን ምሥጢሩ አንተ ጋ ነው ። ሳላየው ያጎረሰኝ እጅህ ጥጋቤ ነው ። በማላይህ ዘመን ሁሉ ታየኝ ነበር ። እስካይህ ብትጠብቅ ኖሮ እስካሁን በጨለማ ነበርሁ ። የእልፍኙም የበረሃው አምላክ አንተ ነህ ። ጌታውም ሎሌውም ላንተ ያው ነው ። የሰው ፍቅር እንጂ የሰው ደረጃ የለህም ። ከቦታ ፣ ከጊዜ ፣ ከሁኔታ ባይ ትሠራለህ ። እንዳማረብህ ያለኸው ሆይ የሚረግፈው ዓለም እንዳያታክተኝ አቅሜ ነህ ። እንደ ጸናህ ያለኸው ሆይ እልፍ ፣ እልፍ የሚለው ይህ ጊዜ እንዳያናውጠኝ ዓለቴ ነህ ። እንዳፈቀርህ ያለኸው የሚሰናበቱ ወዳጆች ተስፋ እንዳያስቆርጡኝ ዋሴ ነህ ።ስያዝ የምታስለቅቀኝ የክፉ ቀን ስንቄ ነህ ።
ጌታ ሆይ የማላይህ ቦታ የለም ። እልፍ ሠራዊት ሳይ የዚህ ሁሉ መጋቢ ማነው እላለሁ ። እንደ አንድ ሰው የምመግበው እኔ ነኝ ትለኛለህ ። ብዙ በሽተኛ ሳይ የዚህ ሁሉ አልጋ አንጣፊው ማነው እላለሁ ። ሠርቼ የማስነሣው እኔ ነኝ ትለኛለህ ። አያሌ ስደተኛን ሳይ የዚህ ሁሉ ተቀባይ ማነው እላለሁ ። አንተን አገር ያላመድሁ ለዚህም አለሁ ትለኛለህ ። ሺህ ሕፃናት ሲወለዱ የዚህ ሁሉ አሳዳጊ ማነው እላለሁ ። አንተን ያሳደግሁ ዛሬም ያው ነኝ ትለኛለህ ። የዓመታት ርዝማኔ ጠባይህን አይለውጠውም ወይ ስልህ እኔ እግዚአብሔር አልለወጥም ትለኛለህ ። የምከፍልበት መብራት ስንቴ ይሄዳል ፣ ያንተ ፀሐይ ግን በነጻ ይሰጠኛል ። የማልሰጋው ስጦታህ ቡሩክ ነው ።
መድኅኔ ሆይ አንተን የማልሰማበት  ቦታ የለም ። በነገሥታት አዋጅ ውስጥ እሰማሃለሁ ። አላርፍም ብሎ ምድርን ላጎሳቆለ የሰው ልጅ እግዚአብሔር ዓለም አቀፍ ሰንበት አወጀ እላለሁ ። ምድሩ ሲያርፍ ፣ ሰማይ ከሰው ብክለት ሲጸዳ ደስ ያለህ ይመስለኛል ። በጠቢባን ምክር ውስጥ እሰማሃለሁ ፣ የማላውቀውን የልቤን ትርታ ፣ የኩላሊቴን ሥራ ስሰማ አሁንም አንተን እሰማሃለሁ ። በጨዋታ መሐል እኔ ሰማይ ነኝ ። አንተ ደግሞ በምድር አለህ ፣ በወንድሜ ውስጥ አለህ ፣ በልቤ አለህ ። ከሰማይ ዝምታ ፣ ከምድር ዝርጋታ ውስጥ እንደገና ድምፅህን እሰማለሁ ። የድንበር መስመር የሌላቸው ሰማይና ምድር ሲያጫውቱኝ አሁንም እሰማሃለሁ ። በአበቦች ውበት ፣ በእንስሳት ገርነት ፣ በአራዊት አትንኩኝ ባይነት ውስጥ አንተን እሰማሃለሁ ። የፈጠርከውን አለመውደድ ትክክል አይደለህም ብሎ አንተን መስደብ ሆነብኝ ። የሌለህበት የለም ፣ እኔ የሌለሁበት አንተ አለህ ። ብዕር እያነባ ክብርህን ፣ ሰባኪ እየደከመ ገናንነትህን ፣ መላእክት እየታደሱ ልዕልናህን ፣ ድሆች እየተከዙ የምትመጣዋን ቀንህን ያወድሳሉ ። ይህችን ጽፌ እስክጨርስም ዕድሜዬን እሰጋለሁ ። ስለ ዕድሜ ምጽዋትህ ባለጠጋው ሆይ አመሰግንሃለሁ ።
ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ክብር ምስጋና ይገባሃል ። ከምታልቀዋ ከዛሬዋ ቀን እስከማይፈጸም ዘመን ፤ ከልባችን እስከ አርያም አሜን ። የሚሰማህ አሜን ይበል ።
የነግህ ምስጋና 18
መጋቢት 19 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም