የትምህርቱ ርዕስ | የማን ሐዋርያ ነን ?

“የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ የሆነ ጳውሎስ” 1ጢሞ. 1፡1
ሐዋርያ ማለት ሂያጅ ፣ ገስጋሽ ፣ መልእክተኛ ማለት ነው ። በምሥጢራዊ ፍቺው ደግሞ በሥልጣን የተላከ ማለት ነው ። ሐዋርያ ንጉሣዊ መልእክትን ፣ የነጻነት ብሥራትን ይዞ ልዩ ልዩ ድንበሮችን ፣ ባሕሎችን ፣ ሕዝቦችን ለማብሠር የሚጓዝ ነው ። ሂያጅ ነው ስንል ዓላማ አድርጎ የሚጓዝ ነው ፤ የተላከ ነው ስንል የሕይወት መልእክትን የያዘ ነው ማለታችን ነው ፤ የሚሄዱ ከርታቶች ፣ የሞት ድምፅ የያዙ መልእክተኞች አሉና ። ሐዋርያነት በጉባዔ የሚሰጥ ሹመት ፣ ለራስ የሚያፈስሱት ቅባት አይደለም ። ሐዋርያነት ትእዛዝ ነው ። የትእዛዙም ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው ። ትእዛዙም ወደ አሕዛብ ሁሉ ሂዶ ወንጌልን መስበክ ነው ። ንጉሣዊ ትእዛዝ ነውና ወንጌልን ባልሰብክ ወዮልኝ የምንልበት ነው ። 1ቆሮ. 9፡16 ።

በሁሉም ሥርዓት አለሁ የሚሉ ፣ ራሳቸውንም የለውጥ ሐዋርያ ብለው የሚጠሩ ፣ ለአሙቁልኝ የሚጠሩ ፣ የራሳቸው ልቅሶ ባይሆንም ተከፍሎአቸው የሚያስለቅሱ ፣ ደረት ሳይመቱ የሰው ደረት በግጥምና በዜማ የሚያፈርሱ ሰዎችን ዓይናችን ጠግቧል ። የዘመን ሎሌ መሆን የማይሰለቻቸው ፣ ለመጣው ሁሉ የሚያዜሙ አያሌ ተለዋዋጮችን ምድር ተሸክማለች ። የዘመን ሎሌዎች ሲገለበጥ እየተገለበጡ ፣ እንደ እባብ እየተሸለቀቁ ፣ እንደ ንሥር ጠጉራቸውን እያደሱ የሚነሡ ናቸው ። ሐዋርያው “የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ” ብሎ ራሱን ሲጠራ የዘመን ሐዋርያ አይደለሁም ማለቱ ነው ።
የሌሎች ሕይወት እየጠፋ የእነርሱ ደመወዝ ሲቆረጥ የሚያማቸው ፣ በሌሎች ላይ የሚተኮሰው ከባድ መሳሪያን እንደ ቀላል እያዩ እነርሱን የወጋቸውን መርፌ ግን አጋነው የሚያወሩ ሰዎች አሉ ። ዓለም በሱናሚ እየጠፋ እነርሱ ግን እግራቸውን ጭቃ ስለነካው የሚያማርሩ ራስ ተኮር ሰዎች አሉ ። ምን አገኛለሁ እንጂ ምን እሰጣለሁ ? የማይሉ ፣ ማንንም ሰው ተጠቅመው የሚጥሉ ፣ ወላጆቻቸውን ሳይቀር ለጥቅም ብቻ የሚፈልጉ ራስ ወዳዶች እነዚህ የራሳቸው ሐዋርያ ናቸው ። በሄዱበት ሁሉ የሚያወሩት እኔ ፣ እኔ እያሉ ነው ። እነርሱ ያላማሰሉት ወጥ አይጣፍጥም ፣ እነርሱ የሌሉበት ውሳኔ አይጸድቅም ብለው የሚያምኑ ናቸው ። እነዚህ ሰዎች በመንፈሳዊ ቤት ሲኖሩም አደባባዩን የራሳቸውን ገድል በማውራት ያጣብቡታል ። ለራሳቸው ያላቸው ግምት ከፍ ያለና ፣ ሰይጣን በነፋስ የሞላው ትልቅ ፊኛ ነው ። የቴሌቪዥን መስኮት ባለበት ለመታየት አንገታቸውን የሚያሰልሉ ፣ ካልታዩ የሚሞቱ የሚመስላቸው ናቸው ። ስለ ግል ጥቅም እንጂ ስለ ጋራ ፍቅር ማሰብ እንኳ አይፈቅዱም ። ቀድመው ቦታ መያዝን ፣ ምርጡን ለእኔ ማለትን ተክነዋል ። ንጹሕ ልብስን እንጂ ንጹሕ ልብን ገንዘብ አላደረጉም ። በፈገግታ መሸኘት እንጂ ለሌላው መሥዋዕት መሆንን አይፈቅዱም ። ሁሉንም ነገር በስሌት እንጂ በእምነት ለማድረግ ይቸገራሉ ። እነዚህ ሰዎች ምድርን ያጎሳቁላሉ ። ልባቸውን ለማግኘት የመንፈቅ መንገድ መጓዝ ይጠይቃል ። የራሳቸው ሐዋርያ በመሆናቸው ስለ ራሳቸው አውርተው አይጠግቡም ። በክብራቸው አይደራደሩም ። ትልቅ ነን ብለው ያስባሉ ። የአገር ቁንጮም እንደሚሆኑ ይተነብያሉ ። ዝቅ አላሉምና ጌታ ሊያቀናቸው ይቸገራል ። ትልቅ ናቸውና አምላክ አያዛቸውም ። ቅዱስ ጳውሎስ ራሱን የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ ሲል የራሴ ሐዋርያ አይደለሁም እያለ ነው ።
አንዳንድ ሰዎች በደስታ የሚውሉት ሰው ፈገግ ካለላቸው ብቻ ነው ። ለማሳቅ ወጥቶ ሰው ያኮረፈበት ቀልደኛ እንደሚጨነቅ እነዚህ ሰዎችም ሰላማቸውን የመሠረቱት በሰዎች ስሜት ላይ ነውና የጠቆሩ ፊቶችን እንደ ጠቆረ ሰማይ ያያሉ ። ምድር ስትከዳቸው እግዚአብሔር እንደሚቀበላቸው ማመን ይቸገራሉ ። ቀትር ሲጨልምም ክርስቶስ እንደማይተዋቸው ይዘነጋሉ ። በዙሪያቸው ያሉት ሰዎች ሲበተኑ ግራ ይጋባሉ ። ስለዚህ ዘወትር የሚያጠኑት ስለ ሰው አያያዝ ነው ። ሰውን ከማጣት እግዚአብሔርን ማጣት ይመርጣሉ ።የሚያገለግሉትም የእግዚአብሔርን አሳብ ሳይሆን የሰዎችን ደስታ ነው ። ሐዋርያው ራሱን የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ ብሎ ሲጠራ የሰው ሐዋርያ አይደለሁም እያለ ነው ።
“እልህ ምላጭ ያስውጣል” ይባላል ። ተገቢ ግን አይደለም ። ለእልህ እሞታለሁ የሚሉ ብዙዎች ናቸው ። እልህ ሁሉ እውነት አይደለም ። በእልህ ያመኑትን መካድ ፣ በእልህ የካቡትን መናድ ፣ በእልህ ያፈቀሩትን ማርከስ ፣ በእልህ የሾሙትን መሻር የብዙ ሰዎች ጠባይ ነው ። እልህ ቆጥቦ አይጣላም ፣ እስከ መጨረሻው ይጣላል ። እልህ መዋደድ እንዳለ መጣላት ፤ መጣላት እንዳለ መዋደድ መኖሩን ይዘነጋል ። እልህ ቊጣ ያለበት ስሜት ነው ። በእልህ የሚሰብኩ ፣ በእልህ የሚዘምሩ አሉ ። እልህ በረከት የለውምና ቆይቶ ደስተኛ አይደሉም ። እልህ ግን እርካታ አለው ። ክፉ እርካታ ። የእልህ ክፉ እርካታን ከመንፈስ ቅዱስ እርካታ የማይለዩ ሰዎች እየገፉበት ይመጣሉ ። በእልህ አገር ይፈርሳል ። በእልህ ሌቦች ለሹመት ይታጫሉ ። እልህ ሞቼም ላሰቃያቸው ይላልና ጠቡ ከመቃብር ወዲያም ነው ። በእልህ የሚያመነዝሩ ፣ በእልህ በሽተኛ የሆኑ ፣ እንዳናደዱኝ ላናድድ ብለው የተቃጠሉ ብዙ ናቸው። ሐዋርያው ራሱን የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ ሲል የእልህ ሐዋርያ አይደለሁም ማለቱ ነው ።
እኛስ የማን ሐዋርያ ፣ የማን መልእክተኛ ፣ ምን ይዘን የምንገሰግስ ነን ?
1ጢሞቴዎስ /3/
ጥቅምት 29 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲአመ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም