መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » የምሕረት አዋጅ

የትምህርቱ ርዕስ | የምሕረት አዋጅ

ያጌጡ ከተሞች የደስታ ማስታወቂያ እንጂ ደስታ የላቸውም ። ሁልጊዜ ለመደሰት ሙከራ ይደረጋል ፣ ስሜት ጊዜያዊ መልስ አግኝቶ ወዲያ መከፋት ይጀምራል ። ልብን የሚያሳርፍ ደስታ ግን ከዓለማዊ ነገር ሊገኝ አይችልም ። ያማ ከሆነ ደስታ ሸቀጥ ፣ ወይም የፍለጋ ውጤት ሆነ ማለት ነው ። ደስታ የኑሮ ፍሬ እንጂ በተፈጥሮ የሚታደሉት አይደለም ። ፍሬ ነውና ሁሉም የሚኖረው እንጂ እገሌ ያለው ፣ እገሌ የሌለው ተብሎ እንደ ጸጋ የሚመደብ አይደለም ። የደስታ ፍሬ እንጂ የደስታ ጸጋ የለም ። ዓለም በዚህ ኃጢአት ደስታ ያጣውን ሰው ሌላ እንዲሞክር እየመከረች ከድጡ ወደ ማጡ ትነዳዋለች ። ዮሐንስ መጥምቅ ይህችን ዓለም ሲመንን አልተሳሳተም ። የደመቀ ከተማ ዕረፍት ቢሰጥ ኖሮ ተነሣሕያን ወደ ምድረ በዳ አይመጡም ነበር ። የበደለኝነት ስሜት በመጠጥ ፣ በሱስ ዝም ሊል አይችልም ። የበደለኝነት ስሜት ራስን በመቅጣት ፣ በችሎት ተገቢውን ፍርድ በማግኘት ረጭ የሚል አይደለም ። የበደለኝነት ስሜት ከእግዚአብሔር ምሕረት ጋር በመገናኘት ብቻ ይገሠጻል ።

ዮሐንስ መጥምቅ ይቅር ተብላችኋል የሚለውን የምሥራች ለመንገር የእግዚአብሔር ምሕረት ተጨባጭ እንዲሆንላቸው በውኃ ያጠምቃቸው ነበር ። ሰውዬው ንስሐ የገባበትን በደል እየቀሰቀሱ በአደባባይ ፣ የእግዚአብሔር ቀጪ ነን ብለው የሚናገሩ በዮሐንስ አገልግሎት ፊት መቆም አይችሉም ። የሃይማኖት ተግባሩ መግለጥ እንጂ ማጋለጥ አይደለም ። መግለጥ ሰውዬውን ሕመሙን አስረድቶ ለንስሐ ማብቃት ነው ። ይቅር አልተባልሁም የሚል ስሜት ቢሰማው እንኳ፡- “የውቅያኖስ ውኃ በቤት ጥራጊ አይቆሽሽም ፣ በእግዚአብሔር ምሕረት ፊት ያንተ በደል እንደዚህ ነው” እያሉ ያረጋጉታል ። ሰው ግን የሚዘምረውን ፣ የሚያስቀድሰውን ወገኑን ለማሸማቀቅ ፣ የሰውዬው ትላንት ላይ ቆሞ ይቀራል ። ኦ ንስሐ የምንገባው ሰዎች እንዲያምኑን አይደለም ፣ ከእግዚአብሔር ጋር ለመታረቅ ነው ። እርሱ ይቅር ካለን ማነው የሚከስሰን ? አንድ ክርስቲያን በአደባባይ የወንድሙን በደል ካወራ ክርስቲያንነቱ እያበቃ ነው ። ምክንያቱም ክርስቲያን የሆነው በክርስቶስ ደም ተከልሎ እንጂ በብቃቱ ተመዝኖ አይደለምና ። ዮሐንስ መጥምቅ ሆይ ምንኛ ቅዱስ ሰው ነህ ! የበደለ ያርፍ ዘንድ እንዲህ ትተጋለህ !

ውኃ የቆሸሸውን ያጥባል ፣ የዕለትና የዘመናት እድፍን ያጠራል ። በደለኛም በእግዚአብሔር ምሕረት አዲስ ሰው ሁኖ ይቆማል ። አንዳንድ ተነሣሕያን / ንስሐ ገቢዎች/ የማልቀስ አቅም የላቸውም ። ሁሉንም በደላቸውን ለማስታወስም ይቸገራሉ ። እግዚአብሔር ግን ከእኛ የሚፈልገው በደለኛ መሆናችንን ማመን ብቻ ነው ። የምሕረት ነጋዴዎች “ይህን ያህል ገንዘብ አምጣ ኃጢአትህ ይቅር ይባላል” ሊሉ ይችላሉ ። ምሕረቱ ግን ከደሙ የተነሣ ገንኖ ይኖራል ። ምሕረትን እንቀበለዋለን እንጂ አንሸምተውም ። የምንገዛው ምሕረት የለም ፣ የገዛን ምሕረት ግን አለ ። ማልቀስ ስላልቻለ ፣ ሁሉንም የኃጢአት ዝርዝር ስላልተናገረ ይቅር እንዳልተባለ የሚሰማው ይኖራል ። ንስሐ ግን የትግል ፍሬ ሳይሆን የደሙ ውጤት ነው ። “የልጁም የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ከኃጢአት ሁሉ ያነጻናል።” (1ዮሐ. 1 ፡ 7 ።) ከቤተ ክርስቲያን ምሥጢራት አንዱ ንስሐ ነው ። ንስሐ ምሥጢር ፣ ንስሐ ጸጋ ነው ።

ቢያነባ መጸጸቱን አመልካች ነው ፣ ውኃውም ምልክት ነው ። ይቅር ማለት ግን የእግዚአብሔር ፈቃድ ነው ። ዮሐንስ መጥምቅ የእግዚአብሔርን ምሕረት ተጨባጭ ለማድረግ በእጅ በሚዳሰስ መልኩ የይቅርታ ስሜት እንዲሰማቸው በውኃ ያጠምቅ ነበር ። ተነሣሕያኑ አሉ ፣ የንስሐ ሰባኪውም አለ ፣ ይቅር ባዩ ክርስቶስም ተገኝቷል ። ራሳችንን እንድናይ የሚያግዙን ውሉደ ክህነት የሆኑት የንስሐ ሰባኪዎች ይደነቃሉ ። ሰውን በድለሃል ማለት ከባድ ዋጋ ያስከፍላል ። መንግሥትን አጥፍተሃል ማለት ከምድረ ገጽ ሊያጠፋ ይችላል ። ሰውን በድለሃል ማለት እንዴት ደፈርከኝ ? ያሰኝ ይሆናል ። መንፈሳውያን አባቶች ግን ይህን የማድረግ ትልቅ ሥልጣን አላቸው ። ማንም የሥነ ልቡናና የሥነ አእምሮ ባለሙያ “ይቅር ተብለሃል” ማለት አይችልም ። ሥልጣን የተሰጣቸው ውሉደ ክህነት ግን ይቅርታን ያውጃሉ ።

“ይቅር ተብለሃል” ከሚል የበለጠ የምሥራች የለም ። ሰዎች በመጠጥና በሱስ ውስጥ የሚያልፉት ከበደለኝነት ስሜት ለመውጣትም ነው ። የሕሊና ክስ በእግዚአብሔር ምሕረት ካልሆነ በምንም ሊቆም አይችልም ። ሰይጣን እንድንበድል ያደርገናል ፣ ስንበድል ደግሞ ይከስሰናል ፣ ንስሐ ስንገባ “ይቅር አልተባልህም” እያለ በራሱና በሰዎች በኩል ይዋጋናል ። ዮሐንስ መጥምቅ ማማር በሌለው በረሃ የሚያምር የምሥራች ይናገር ነበር ። የሚታይ ውበት የሌለው ሰው እግሮቹ ያማሩ ነበሩ (ሮሜ. 10 ፡ 15) ። መልካሙን የምሥራች ያወራልና ። ዛሬም ኃጢአት የሚያስጨንቃቸውን ያህል ይቅር አልተባልሁም በሚል ስሜት የሚሰቃዩ አሉ ። ንስሐ እምነት ነው ። በደልንና ምሕረቱን ማመን ነው ። ይቅር አልተባልሁም ማለት “አንተ ይቅር አትልም” ብሎ እግዚአብሔርን መሳደብ ነው ።

ንስሐ የገባችሁ ወገኖች ይቅር ተብላችኋል ። ደስ ይበላችሁ ! የሚበልጥ ጸጋ ይጠብቃችኋል ። “እኔስ ለንስሐ በውኃ አጠምቃችኋለሁ፤ ጫማውን እሸከም ዘንድ የማይገባኝ ከእኔ በኋላ የሚመጣው ግን ከእኔ ይልቅ ይበረታል፤ እርሱ በመንፈስ ቅዱስ በእሳትም ያጠምቃችኋል” (ማቴ. 3 ፡ 11)።

በበዓለ ጥምቀቱ የሚነገረው የምሥራች ይህ ነው !

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥር 18 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም