ቤተ ጳውሎስ፤ ዓርብ ግንቦት 3 2004 ዓ.ም.
ማዘያው ከጠፋ የህፃን አንቀልባ
መልካሙ ተጣሞ ካጨድን ገለባ
አፅናኙ ተክዞ መፅናናትን ካጣ
የቆመ የሚመስለው ጎብጦብን ከመጣ
ረሀብ አጠውልጎት ህፃን ካለቀሰ
ጻድቅ መላ ጠፍቶት ሰይጣን ከቀየሰ
ብርታት አጎንብሶ ድካም ፀንቶ እግሩ
ይሁዳና ዴማስ ጽድቅ ከመከሩ
ሳዖልና ኬፋ ደግ ካልተስማሙ
ማየትና መስማት ካንተ ይሁንለት።
ፈትልን የሚፈትል ተራቁቶ ካደረ
ውለታ የበዛለት በሳቅ ካልዘመረ
በብዙ የተሾመ ጥቂት ካልታመነ
ልብን አሳራፊው ልቡ ከጨከነ
ሰባኪ እየካደ ዓለሙ ካመነ
አማኙ ሲታበይ ቀራጭ አጐንብሶ
የጽድቁን አዝመራ ከወሰደ አፍሶ
አቤቱ ለባሪያህ አይነልቡን አብራ
የቆምኩኝ ሲመስለኝ እንዳልወድቅ አደራ።
ሥራዬ የሞት ነው ጽድቄ የመርገም ጨርቅ
አቤቱ አድነኝ በድካሜ ሳትፈርድ
ብርታትህ ያቁመኝ አንተን እንድመስል
ማስተዋሌን አድስ ያለማመኔን ቃል፡፡