የትምህርቱ ርዕስ | የበዛ ጥበብ

“ጸጋውንም በጥበብና በአእምሮ ሁሉ አበዛልን ።” ኤፌ. 1 ፡ 8 ።

ጸጋው ካስገኘልን ነገሮች ጥበብና እውቀት ተጠቃሽ ናቸው ። የመጀመሪያው ጥበብ ሲሆን ሁለተኛው አእምሮ ነው ። ጸጋው ድኅነት ሲሆን ድኅነትም ጥበብና እውቀትን አብዝቶልናል ። ጥበብ ምንድነው ብለን መጠየቃችን አይቀርም ። ጥበበኞች የሚባሉም ያለባበስ ቄንጥ ያላቸው ፣ በየመድረኩ ሰውን የማሳቅ አቅም ያዳበሩ አይደሉም ። ጥበበኞች ስንል ብልጦች ማለታችን አይደለም ። የአበላል መንገዱ የገባቸው እነርሱ ጥበበኛ አይባሉም ፣ የሚባሉት ቀማኞች ወይም ሕጋዊ ሌቦች ነው ። ጥበበኛ ዘመን የገባው ሳይሆን ዘመኑን ለእግዚአብሔር የሚያስገዛ ነው ። ጥበብ ከበላይ ያለውን እግዚአብሔር እንድንፈራ ፣ የበላዮችን እንድናከብር ታስተምራለች ። ፈሪሀ እግዚአብሔር በነፍስ በሥጋ ትፈውሳለች ። የበላዮችን ማክበርም ከውርደት ያድናል ። ጥበብ በአሁኑ ሁኔታ አትታጠሩ ፣ በአሁኑ ማግኘት ትዕቢት ፣ በማጣትም ድንጋጤ አይግባችሁ ትላለች ። ጥበብ የማትናገርበት ቀን የለም ፣ ሰዎች ግን የማይሰሙበት ዘመን ብዙ ነው ። ጥበብ ያጣ በአፉ እየደለለ ፣ በልቡ እየገደለ ይኖራል ። ጥበብ ያጣ ሁሉንም በብልጠት እይዛለሁ ብሎ በመጨረሻ እንደ ሞኝ ሁሉም ያውቀዋል ። ጥበብ በሚያልፈው ቀን የማያልፈውን ፣ በምድር ላይ ሰማይን ታስተምራለች ። በዓለም ላይ ድንቁርና የተስፋፋው ትምህርት ጠፍቶ ሳይሆን የሚማር ጠፍቶ ነው ።

ጥበብ አእምሮ ላይ የሚሰማን ደስ የሚል ጨዋታ ፣ ሰውን አታሎ መግባት ፣ ሁሉንም ላለማስቀየም እሺ ፣ እሺ ማለት አይደለም ። ጥበብ ፍትሕን መፈለግና ለእውነት ዋጋ መክፈል ነው ። ጥበብ እውነትን ያከበረ እንጂ የሠዋ ፍቅርን አትሻም ። ጥበብ ሞትን እያሰቡ ቅንነትን በየዕለቱ መጨመር ነው ። የትም ከፍታ ላይ ቢወጡ መውረድ ፣ ከመሬት በታች መሆን አይቀርም ። ያ ሁሉ ክብርና ዝና በሁለት ፊደል ይከተታል ። “ሞተ” በሚለው ይዘጋል ። ጥበብ ፈራሽነትን እያሰቡ ገዳይነትን መጠየፍ ነው ። እርሱ ሞቶ እኔ አልቀርምና ። ጥበብ ጥበበኞች ነን ከሚሉት እጅግ የራቀች ፣ ፈሪሀ እግዚአብሔር ባለበት ያደረች ናት ። ጥበብ በማስታወቂያ ኃይል የቆመች ሳትሆን የምትፈለግ ስውር እጅ ናት ። በዓለም ላይ ትልቁ ድንቁርና አዋቂ ነኝ ብሎ ማሰብ ነው ። ጥበበኛ ነን ሲሉ እጅግ መደንቆር ይከሰታል ። ዓለም ተጠበብሁ ብላ በመጨረሻ የሠራችው እንኳን ሰውን ቅጠል የማያስቀረውን የኒውክለር አረር ነው ። ጥበብ አውቆ ትሑት በሚሆን ሰው ልብ ውስጥ አለች ። የጥበብ መቀመጫው ነፍስ እንጂ ግድግዳ አይደለም ። በግድግዳቸው ላይ ሥዕል ስለሰቀሉ ጥበበኛ ናቸው ማለት አይደለም ። ጥበብ ግን ለጥበብ ዋጋ አላት ። ጥበብ በአገራችን እንደ ራቀን መጽሐፍ በቅናሽ ዋጋ ፣ ሥጋ በጭማሪ ሲሸጥ ማየት በቂ ነው ። ጥበብ የከዳው ትላንትን ፣ ዛሬንና ነገን ያበላሻል ። ትላንት የሌላትን ዛሬ የሚፈጥሩ የጥበብ ጠላቶች ናቸው ። ዛሬ ትላንት ከሌላት ነገም የላትም ።

ጥበበኞች የዛሬን ትውልድ ሳይዘነጉ ለነገው ትውልድ ያቅዳሉ ። ጥበበኛ የጥበብ ቃላት የሚናገር አይደለም ። እርሱንማ የመቅረጫ መሣሪያውም የቀረጸውን ይናገረዋል ። በቀቀንም የሰማችውን ስትደግም ትውላለች ። የገደል ማሚቱም ያስተጋባዋል ። ጥበብ ኑሮ ነው ። ጥበብ የሚሞቱለት ምክንያት ነው ። ምን ቢሞላ ነገ መጉደሉ ፣ ምን ቢጎድል ነገ መሙላቱ አይቀርም ። ጥበብ የሚያጸጽት ነገር ላለማድረግ ፣ ከመግደል መሞት እንደሚሻል ታስተምራለች ። ያዳነን የገደለው ጲላጦስ ሳይሆን የሞተው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው ። ጥበብ ለጆሮ በጣዕም ፣ ለዓይን በውበት ፣ ለልብ በዕረፍት መገለጥ ነው ። ጥበብ ክፉ ልማድን በበጎ ልማድ ትለውጣለች ። ጥበበኞች በማውገዝ ሳይሆን መልካሙን ነገር በማሳየት ሥነ ምግባርን ገናና ያደርጉታል ። ጥበበኛ ሳይታገል ሰዎቹ የያዙትን የተነቀለ ቦምብ መቀበል ይችላል ። ጥበብ ከሁሉም ፍጥረት ትምህርት እንዳለ አምኖ ማስተዋል ነው ። ጥበብ ቅድስናን በልብስ ፣ ቅንነትን በሽቱ የሚለውጥ አይደለም ። ጥበብ ሰውን በላይ ቁመናው አይለካውም ። ያማ ቢሆን ረጃጅሞች ለሰማይ ስለቀረቡ ሀገረ ሕይወትን በወረሱ ነበር ። ጥበብ ለጥበብ ክብር አለው ። ጥበብ ጠቢብን ያውቃል ፣ ያከብራል ። እውነተኛው ጥበብ ክርስቶስ ነው ።

ጥበብ መላውን ሕይወት የሚገዛ ፣ በትጋት ላይ ጥንቃቄን ፣ በትዕግሥት ላይ ደስታን የሚጨምር ነው ። እየተጉ የሚያፈርሱ ፣ እየታገሡ የሚከስሉ አሉና ። ጥበብ ሰዋዊ ፣ አጋንንታዊ ፣ ሰማያዊ ተብሎ ሊከፈል ይችላል ። ሰዋዊ ጥበብ ሕይወትን የቁስ ጥገኛ ሲያደርግ ፣ አጋንንታዊ ጥበብ ፌዝን ያነግሣል ። ሰማያዊ ጥበብ ጊዜን በትክክል ይጠቀማል ። ጠቢብ ከበደልሁ በዚያው ልጥፋ አይልም ። በደልን መቀነስ ቅድስና ፣ ለዓለምም መፍትሔ እንደሆነ ያውቃል ። በነቃ ቀን ቶሎ ይመለሳል እንጂ ሞት ላይ አይተኛም ። ጥበብ ከእግዚአብሔር ጋር የማያቋርጥ ግንኙነት መፍጠር ነው ። ሳይበላ ራበኝ የሚል ሞኝ ነው ። ቃለ እግዚአብሔር ሳያገኝም ሰላም አጣሁ ብሎ የሚደነቅ ጥበብ ያጣ ነው ። ጥበብ የሌላው ሁከት የእኔ ሰላም ነው አትልም ፣ የሌላው ሰላም የእኔ ሰላም ነው ብላ ታምናለች ፣ ለዚያም ትሠራለች ። ቸር ክርስቶስ ሆይ ጥበብ አብዛልን ፣ በአንተ ድነናልና !

የኤፌሶን መልእክት ትርጓሜ /16

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የካቲት 29 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም