የትምህርቱ ርዕስ | የታወቀ አምላክ

“የማይታየው ባሕርይ እርሱም የዘላለም ኃይሉ ደግሞም አምላክነቱ ከዓለም ፍጥረት ጀምሮ ከተሠሩት ታውቆ ግልጥ ሆኖ ይታያልና፤” ሮሜ. 1፡20 ።

የእግዚአብሔር አሳብ ይህን ፍጥረት አቀደ ፣ መለኮታዊ ቃሉ አበጀው ፣ ቅዱስ መንፈሱ አቆመው ። የመጽሐፍ ቅዱስ የመጀመሪያው ክፍልና ምዕራፍ እንዲሁም ቍጥር የሚናገረው ይህ ዓለም አስገኚ እንዳለው ነው ። “በመጀመሪያ እግዚአብሔር ሰማይንና ምድርን ፈጠረ” በማለት ነው ። ዘፍ. 1፡1። ሰማይ ሲል የማይታየውን ዓለመ መላእክትን ፣ ምድር ሲል የሚታየውን ዓለመ ሰብእ ማለቱ ነው ። በጸሎተ ሃይማኖትም፡- “ሁሉን በያዘ ሰማይና ምድርን የሚታይና የማይታየውን በፈጠረ በአንድ አምላክ በእግዚአብሔር አብ እናምናለን” በማለት እናውጃለን ። ይህ ጸሎትም ፣ ምስክርነትም ነው ። የሚታየውን የፈጠረ ንዑስ አምላክ ፣ የማይታየውን የፈጠረ ልዑል አምላክ አለ ብለው የሚያምኑ አሉና የሚታየውንና የማይታየውን በፈጠረ በአንድ አምላክ አምናለሁ እንላለን ።

ፍጥረት ስለ እግዚአብሔር የሚያሳውቅ ነውና ከመምህራን በፊት የነበረ መምህር ነው ። ፍጥረት ስለ ቅዱሱ ፈጣሪ ይናገራልና ቅዱስ ጽሕፈት ነው ። ሁሉም ሰው የሚያነበው ፊደል ፣ የቋንቋ ገደብ የሌለበት ጽሕፈት ፣ የተማረና ያልተማረ የሚያነበው መጽሐፍ ፍጥረት ነው ። መጽሐፍ ይታጠፋል ፣ ፍጥረት ግን ሁልጊዜ ተዘርግቶ ያለ መጽሐፍ ነው ። መጽሐፍ ዓይንን ያደክማል ፣ ለማየት የማይታክት መጽሐፍ ግን ፍጥረት ነው ። በፍጥረት መጽሐፍነት የምናነበው “እግዚአብሔር ፍቅር ነው” የሚለውን ጽሕፈት ነው ። በፍጥረት ላይ ችሎታው ፣ ምልአቱ ፣ ርቀቱ ፣ ረድኤቱ ፣ ጥበቡ ፣ ውበቱ የተገለጠ ቢሆንም ይህ ሁሉ የፍቅር ጠባዩን የሚገልጥ ነው ። የተፈጠረ ብቻ ሳይሆን ያልተተወ ፣ መለኮታዊ ጥበቃ ያለው ፍጥረት መሆኑን እናያለን ። የሚጠፋው ዓለም ገና ተመርምሮ ካልታወቀ የማይጠፋው ዓለም እንዴት ሊመረመር ይችላል ብለን እንጠይቃለን ። ስለተፈጠረው ፍጥረት ገና ግምት እንጂ እርግጥና ድምድም አሳብ አላገኘንም ፣ ስለ ፈጣሪው ጌታ ባናውቅና ባንገነዘብ የሚደንቅ አይደለም ።

ሰዎች መምህር አጥተው አላመኑም ፣ ሀልወተ እግዚአብሔርን አልተረዱም እንዳንል ከመጽሐፍ በፊት መጽሐፍ ፣ ከመምህራን በፊት መምህር ሁኖ ፍጥረት ቁሟል ። ፍጥረት በአንድ ድምፅ እግዚአብሔር አለ ብሎ ይናገራል ። በፍጥረት ላይም የእግዚአብሔር ባሕርይ ጎልቶ ይታያል ። የሚታየውና የማይታየው ኅብረት ስምምነቱ የእግዚአብሔርን አንድነት ይገልጣል ። ውበትና መናበቡ የእግዚአብሔርን ፍቅርና መሪነት ያጎላል ። ኃያልነቱና ግዝፈቱ የእግዚአብሔርን የማይመከት ክንድ ይተርካል ። ሰዎች ስለ ፍጥረት ብቻ ቢያጠኑ ፈላስፋ ሊቃውንት ይባላሉ ። በተፈጠረው ፍጥረት ፈጣሪውን ሲያስቡ ግን አማኝ ይባላሉ ። የዚህ ዓለም አዋቂዎች የተፈጠረው ፍጥረት ላይ ሲቀሩ ቅዱሳን አባቶች ግን ፈጣሪውን ያመልካሉ ። ቤተ ክርስቲያን የተፈጠረውን ፍጥረት ብቻ ሳይሆን የፈጠረውን እግዚአብሔር ተመልከቱ ትላለች ። ፍጥረታት ያለማቋረጥ ስለ እግዚአብሔር ይመሰክራሉ ። ከሰዎች ጋር ስለ ፍጥረት ብናወራ ሐሜት ይቀላቀላል ። ፍጥረት ግን ስለ ሌላ ሳይቀላቅል ስለ እግዚአብሔር ብቻ ይናገራል ። “የተፈጥሮ ጸጋ ፣ ተፈጥሮ ለግሶን” እያሉ ሰዎች ይናገራሉ ፣ ፈጣሪ ጌታ እንጂ በራሱ የሚለግስ ተፈጥሮ የለም ።

በግዙፍ መነጽሮች የረቀቁ ነገሮችን እናያለን ። በፍጥረትም እግዚአብሔርን እናስተውላለን ። መሃይም የሚያነበው ፊደል ተፈጥሮ ነው ። ተፈጥሮ ስለ እግዚአብሔር ይናገራልና ቅዱስ ጽሑፍ ነው ። ስለ እግዚአብሔር የሚናገሩ ሁሉ ቅዱሳን ናቸው ። መጽሐፍ ስናነብ የደራሲውን ልብ እናያለን ። በፍጥረት መጽሐፍነትም እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን የፍቅር አሳብ እንረዳለን ። ቋንቋ በጆሮ የሚሰማ ነው ፣ የፍጥረት ቋንቋነት ግን በዓይን የሚስተዋል ነው ። ለተፈጠረው ፍጥረት መገኘትን ብቻ ሳይሆን ቀጣይነትን ፣ ቀጣይነትን ብቻ ሳይሆን ግብን የሰጠ አንድ አምላክ አለ ። በሥጋችን ነፍሳችንን የተሸከምን ፣ በነፍሳችን ሥጋችንን የተረዳን የሰው ልጆች ፣ ረቂቅነትን ከግዙፍነት አሳማምተን ይዘናል ። ሕይወትና ሞትን አስማምተን በየዕለቱ እንራመዳለንና አስደናቂ ፍጡራን ነን ፣ ደግሞም ጌታ ያገዘን ብርቱዎች ነን ። እግዚአብሔር ለማወቅ ለሚሹ ግልጥ ነው ። እግዚአብሔር ለፍጥረቱ በፍጥረቱ ይታወቃል ። እግዚአብሔርን በፍጥረቱ አውቆ አለማምለክ ያስቀጣል ። ክብር ምስጋና ለፈጣሪነቱ ይሁን ። አሜን ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ተጻፈ ግንቦት 11 ቀን 2015 ዓ.ም

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም