የትምህርቱ ርዕስ | የትውልድ መጠጊያ

“አቤቱ ፥ አንተ ለትውልድ ሁሉ መጠጊያ ሆንህልን።”
መዝ. 89 ፡ 1 ።

ከግብጽ ሕዝቡን እየመሩ የወጡት ሙሴና አሮን ናቸው ። በምድረ በዳ የተወለደው ትውልድ ስለ ግብጽም ስለ ከነዓንም አያውቅም ። በግብጽ የነበረውን መከራ በከነዓን ያለውን ደስታ ከመስማት ውጭ አልኖረውም ፣ ለመስማትም ትዕግሥት ያለው አይመስልም ። ከሚሊየን በላይ የሚሆነው ሕዝብ በሲና በረሃ ረግፎ ቀርቷል ። ወደ ከነዓን የሚገቡት ሁለት ሰዎች ኢያሱና ካሌብ ብቻ ናቸው ። በበረሃ የተወለደው ያ ትውልድ የመጨረሻ ትልቁ ዕድሜ 39 ዓመት የሞላው ፣ ከአርባ ዓመት በታች ነው ። በበረሃ የተወለደው ትውልድ በግብጽ የነበረውን ጡብን በደም ማቡካት አያውቀውም ። ለአንዲት ቁራሽ እንጀራ ቀኑን በሙሉ በጽኑ ሥራ መሰቃየትን ሲሰማውም ሊያምነውም አልቻለም ። በምድረ በዳ የተወለደው ያ ትውልድ በተአምራት በልቶ የሚያድር ነበር ። እንኳን ሊያርስ የእርሻ ቦታን አይቶ አያውቅም ነበር ። ያለፋበትንና ያልደከመበትን መና ከቤቱ ደጃፍ ላይ ያገኝ ነበር ። ታማኙ እግዚአብሔር ያለ እርሻና ጎተራ ፣ ያለ ኩሽና ይመግበው ነበር ። በመግቦቱ የማይታማው አምላክ ይመግባቸዋል ፣ የእነርሱ ሥራ እግዚአብሔርን ማምለክ ነበር ።

አገር የሌለው አገር ለማግኘት የሚጓዘው ፣ ያልጎደለበት ነገር ግን የሚወርሰውን ማርና ወተት የምታፈሰውን ምድር የሚሰማ ነበር ። በመከራ ያለፉት ወላጆቹ ነበሩ ። የእያንዳንዱን ቀን ቁርስ ለመብላት የዓመት ልፋት በየዕለቱ የሚለፉት ፣ በነጻነት ወጥቶ መግባት የተነፈጉት ፣ ልጆችን ወልደው ማሳደግ የተከለከሉት አባትና እናቱ ነበሩ ። ያ መካከል ላይ ነዋሪ ፣ በግብጽና በከነዓን መሐል የተገኘው ወጣት ግን በተአምራት የሚኖር ነበር ። ስላለፈው መከራ ለመስማት አይፈልግም ነበር ። አላየውም ፣ ደግሞም ጎድሎበት አያውቅምና የረሀብን ምንነት ለማወቅ መዝገበ ቃላት ያገላብጥ ነበር ። ከነዓን አይናፍቀውም ። ከከነዓን በተሻለ ቁጭ ብሎ ይበላልና ።

እንዲህ ያለ ትውልድ ብዙ አገራት ገጥሟቸዋል ። በቻይና ፣ በሕንድ ፣ በደቡብ ኮሪያ ፣ በጃፓን ፣ በራሽያ ፣ በአውሮፓ ፣ ከፊል በኢትዮጵያ ይህ ትውልድ እየመጣ ነው ። የምድረ በዳው ትውልድ ፣ በተአምራት የሚኖረው ትውልድ የብዙ አገራት ሥጋት እየሆነ ነው ። ስላለፈው መከራ ሲወራ እርሱን ለማሳቀቅ ተብሎ የተፈጠረ አስፈራሪ ፊልም አድርጎ ይመለከተዋል ። ደግሞም “የእኔ ችግር አይደለም ፣ ለምን ይነግሩኛል?” ብሎ በልቡ ይታዘባል ። የወላጆቹ መከራ ካለፈ ምናልባት የሠላሳ ዓመት ዕድሜ ያለው ሊሆን ይችላል ። እርሱ ግን “ሊያሳድጉኝ ካልቻሉ ለምን ወለዱኝ” ብሎ ራሱን ያዋድዳል ። ስላለፈው መከራ መስማት የማይፈልግ ፣ ስለ ነገ ተስፋም መፈንደቅ የማይችል ትውልድ የምድረ በዳው ትውልድ ነው ። ለአገሩ ቁጭት ፣ ለወገኑ ክብር ያጣ ፣ ጥቅሙን ጣዖት አድርጎ የሚያመልክ ፣ “ምን እሰጣለሁ ?” ሳይሆን “ምን አገኛለሁ?” በሚል ስሌት የሚጓዝ ፣ ትንሽ እንቅፋት ከገጠመው አማራጩ መሞት የሆነ ምስኪን ትውልድ እየፈላ ነው ።

ሙሴ የእግዚአብሔር ሰው ፣ የሕዝብ አባት ፣ መልካም መሪ ነበር ። ያለ አገር ሕገ መንገሥት የተቀበለ ፣ ያለ እርሻ ሕዝብ ሲበላ ያየ ፣ ያለ ኢኮኖሚ አርባ ዓመታት ያስተዳደረ ቅን ሰው ነው ። ይህ ሙሴ ሚሊየን ሲወለድ ሚሊየን ሲሞት አይቷል ። የታሪኩን ሰፊነት ለማወቅ ከዘጸአት እስከ ዘዳግም ያለው የአርባ ዓመት የሙሴ የአመራር ዘመን ነው ። አራት መጻሕፍት አርባ ዓመታትን ሲዘግቡ ሰፊ ነገር እንዳለ እንረዳለን ። የዘፍጥረት መጽሐፍ አንድ ቢሆንም የሚተርከው የአራት ሺህ ዓመታትን ታሪክ ነው ። ሙሴ የእኛ ሰው ቢሆንና ልጅ ቢወልድ “ብዙ አየሁ” ብሎ ይሰይመው ነበር ። ይህ ሙሴ፡- “አቤቱ ፥ አንተ ለትውልድ ሁሉ መጠጊያ ሆንህልን” ብሎ ዘመረ። አገር ያልነበረው ያ ትውልድ አገሩ እግዚአብሔር ነበረ ። የጦር ሠራዊት ወይም መከላከያ ያልነበረው ያ ትውልድ መጠጊያው እግዚአብሔር ነበረ። ከመሠረታዊ ፍላጎት አንዱ መጠጊያ ነው ። ሰውም እንስሳም መጠጊያ ይፈልጋል ። አንዳንድ መጠጊያዎች ከፍራሽ ስፍራ ፣ ከባዶ ሜዳ ያልተሻሉ ናቸው ። ትምህርት ቤቶች የብልግና ተቋም ሲሆኑ የፈረሱ መጠጊያ ናቸው ማለት ነው ።

ትውልድ የዘመን በረዶ አለበትና መጠጊያ ይፈልጋል ። ትውልድ ፋሽን ፣ ሱስ ፣ አምባገነን መሪዎች የአካልና የሥነ ልቡና እስረኛ ሊያደርጉትን ይፈልጉታልና መጠጊያ ይሻል ። ትውልድ ከመነሻ እየራቀ ጦርነት ይበዛበታልና ፣ የበጋው ሐሩር የክረምቱ ቍር ያስጨንቀዋልና መጠጊያ ይፈልጋል ። ሥጋ ፣ ዓለምና ሰይጣን ያሳድዱታልና መጠጊያ ይፈልጋል ።

እግዚአብሔር የትውልድ መጠጊያ ሲሆን ትውልድ በነጻ ሕይወትን ይማራል ። ስለ ነገ ተስፋ ይኖረዋል ። ነገን በማበላሸት ዛሬን መኖር አይሻም ። “ሁሉም ነገር ወደ ጦር ግንባር” እንደሚባለው “ሁሉም ነገር ወደ መዝናናት ግንባር” ወደሚል ቀውስ ውስጥ አይገባም ። የጉርምስና ዘመናቸውን ሳያውቁት ያለፈላቸው ወጣቶች ካሉ እነርሱ እግዚአብሔር ቤት የተጠጉ ናቸው ። እስከ ማታ በሰላም የዋሉ ከተገኙ በጠዋቱ እግዚአብሔርን የተተገኑ ናቸው ። እግዚአብሔር የትውልድ መጠጊያ ነው ። አንዳንድ ትውልድ ምቾትን መቋቋም አቅቶት ፣ መና ሰልችቶት ራሱን ለማጥፋት ይፈልጋል ። በጣም ደስ ሲለውም ሲከፋውም የኃጢአት አምሮቱን ይወጣል ። በሰበብ ከማምለክ በሰበብ መበደል ይቀናዋል ። ትውልድ መጠጊያ ያስፈልገዋል ። የምድር ጠቢባንን ከተጠጋ ከሀዲ ይሆናል ። አክተሮቹን ከተጠጋ አስመሳይ ሰው ይሆናል ። ፖለቲከኞቹን ከተጠጋ ጥይት ማብረጃ ይሆናል ። መተተኞችን ከተጠጋ በአጋንንት እርዳታ የሚያምን ይሆናል ። የወላጆቹን የኑሮ ዘይቤ ከተጠጋ ዘረኛና ትዕቢተኛ ይሆናል ። የትውልድ መልካም ጥጉ እግዚአብሔር ብቻ ነው ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መስከረም 29 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም