መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የነቢያት ጉባዔ » የነቢያት ጉባዔ ክፍል 2

የትምህርቱ ርዕስ | የነቢያት ጉባዔ ክፍል 2

የከበረው ነቢይ ሙሴ ወደ መናገሪያው አትሮኖንስ ተጠጋ ። ከአቤል ጀምሮ ያሉት ቅዱሳንን ለማወቅ ስማቸውን ያስተዋወቀኝ አልነበረም ። በዓለመ ነፍስ እውቀት ሙሉ ይሆናል ። ሙሴና ሚልክያስ ለመተዋወቅ በመካከል የሚያገናኝ ሰው አላስፈለጋቸውም ። ቅዱሳን በሰማይ አለማወቅን ድል ይነሣሉ ። ከሥጋ ግርዶሽ ፣ ኃጢአትን ካመጣው ጨለማ ነጻ ወጥተው በሰማይ ያደሩ ጻድቃን እውቀታቸው ሙሉ ይሆናል ። እንኳን በሰማይ ያሉትን የአምልኮ አጋሮቻቸውን ይቅርና በምድር ላይ እየተከናወነ ያለውን ያውቃሉ /ራእ. 6፡9-11/። “ትንሽ ሥጋ ከመርፌ ትወጋ” እንዲሉ የአካላቸው ክፋይ ቤተ ክርስቲያን በምድር አለችና ስለ እርስዋ ይጸልያሉ ። ቤተ ክርስቲያንን በሰማይና በምድር ያለች አንዲት አካል የሚያሰኛት ራስዋ አንድ ክርስቶስ መሆኑ ፣ እርስ በርስዋም የምትተሳሰብ መሆንዋ ነው ። እንኳን የቅዱሳን ይቅርና የኃጥአን ነፍስም እውቀትዋ በምድር ከነበረው የበለጠ ነው ። ነዌ የተባለው ባለጠጋ በሞተ ጊዜ ከሺህ ዓመት በፊት የነበረውን አብርሃምን ያለ ነጋሪ አውቆታል ። በምድር ላይ ስላሉ ወንድሞቹም ሁኔታ ተረድቷል ። ሉቃ. 16፡ 24-27። እኔም ለቅጽበት በዓለመ ነፍስ ራሴን ሳገኘው አለማወቅን አሸንፌው ነበር ። አለማወቅ ወዳጅን ያሳንሳል ። ስናውቅ በሰማይም በምድርም ብዙ ወዳጅ እንዳለን ያስረግጥልናል ።

ሙሴ ለመናገር ድምፁን ይሞርዳል ብዬ ስጠብቅ እግዚአብሔርን ሲያመሰግን የነበረ ጉሮሮ ነውና ጽዳት አላሻውም ። በዓለመ ነፍስ ከቍጥርና ከዘመን እንዲሁም ከታሪክ ውጭ የሆነችው ነፍስ በዘላለም አሁን ውስጥ ተጠቅልላለች ። ከሺህ ዓመት በፊት የነበረውን ለማስታወስ አትመሰጥም ፣ ወደፊት የሚሆነውን ለመረዳት አታሰላስልም ። ነፍስ በሰማይ በማያረጅ አዲስነት ትኖራለች ። ነቢዩ ሙሴ ተናገረ፡-

“አንድ ጊዜ ተፈትነው ባለፉት ዳግመኛ በማይፈተኑት በዓለመ መላእክት ፣ ዘመናችሁን በሙሉ ተፈትናችሁ በዕረፍት ዓለም ያላችሁት ፣ ጸሎትና ምስጋና ተጋድሎ ሳይሆን እስትንፋስ ነውና ፣ ከጸሎትና ከምስጋና ያላረፋችሁ ፣ ምስጋናውን አዝመራ ፣ ውዳሴን መኸር አድርጋችሁ የምትኖሩ ፣ በሰማይ ያደራችሁ ፣ በአብርሃም እቅፍ ፣ በዘላለም መውደድ የተጠቀለላችሁ ቅዱሳን ፣ በምድር ጠርቶን በሰማይ በተቀበለን በእግዚአብሔር ስም ሰላም እላችኋለሁ ! ከምድር እስከ ሰማይ የሚታመን ፣ በሥጋም በነፍስም ዋጋ የሚከፍል እግዚአብሔር ብቻ ነውና አሜን ብላችሁ አመስግኑ!”

ታላቅ ምስጋናና እልልታ ተሰማ ። ከሞተው አቤል እስካረገው ነቢዩ ኤልያስ ድረስ የሆታ ምስጋና አስተጋባ ። በሰማይ ለማመስገን ምክንያት አያስፈልግም ። እሴት መኖር የለበትም ። ፍጹምነት የማይጎድል ምስጋና ባለቤት ያደርጋል ። ሞላ ጎደለ የቍማር ኑሮ ጨዋታ ነውና ምስጋናና ምሬት ሲያፈራርቅ ይኖራል ። ነቢዩ ሙሴ መናገር ጀመረ፡-

“እኔ ከግብጽ ምድር እየመራኋቸው የወጡት ሚሊየን ሕዝቦች ዛሬ ከእኔ ጋር መውረስ አልቻሉም ። ለከነዓንም ለሰማይም ሳይሆኑ ባክነው ቀርተዋል ። አንድና ሁለት ልጅ የሞተበት አባት ሲያዝን ሁሉ አብሮት ያለቅሳል ፣ ሚሊየን ሕዝብ የሞተበት ሰባኪ ግን ብቻውን ልቅሶን ይገፋል ። የሰባኪው ደግነት ሳይሆን የሰውዬው ምርጫ ለድኅነት ያበቃል ። በምድር ላይ መንፈሳዊውን ጉዞ ያልጀመሩ ኢአማንያን ፣ የጀመሩ ወጣንያን ፣ የጨረሱ ፍጹማን አሉ ። ከነዓንን እያሰቡ ምድረ በዳ መቅረት ፣ ያልተገራ የገዛ ምኞት ራስን አሰቃይቶ መግደሉ ያሳዝናል ። በቤተሰብነት ኃጢአተኝነት የለም ። አቤል አዳም አባቱን ትቶ ለአምልኮተ እግዚአብሔር ቆመ ። መንታ ሁነው ቢወለዱ በብዙ ነገር ይመሳሰሉ ይሆናል ፣ ክርስቶስን መምሰል ግን ምርጫ ነውና አንዱ አምኖ አንደኛው ይቃወማል ፣ አቤልና ቃየን በምድራዊ አባት አንድ ሁነው በሰማያዊ አባት ተለያዩ ። እምነት የሚጫንብን ዕዳ ሳይሆን የምንመርጠውና ራሳችንን የምንሰጥለት ነው ። በምድር እምነታችንን እናከብራለን ፣ እምነታችንም በሰማይ ያከብረናል ። ሁሉም በቤቱ ያስተናግዳል ።”

ሙሴ ይህን ከተናገረ በኋላ በአሳብ የተጓዘ እስኪመስል ዝም አለ ። እኔም እልኸኛ ሕዝብ መሪውን በምድረ በዳ የማስቀረት አቅም አለው ብዬ ማሰብ ጀመርሁ ። በአገልጋዮች የተሰናከሉ ምእመናን ብዙ ናቸው ፣ ሙሴን ስናይ ደግሞ በሕዝቡ ምክንያት ተሰናክሎ በምድረ በዳ የቀረ ፣ የአርባ ዓመት አገልግሎቱን ፍጻሜ ያላየ ነው ። ይህ ሁሉ ለትምህርታችን ተጻፈልን ። አገልጋዮች ሕዝብን ስታስተምሩ ካህንም ፣ ዲያቆንም ፣ ሰባኪም ሰው መሆኑን አስተምሩ ።

ይቀጥላል

የነቢያት ጉባዔ/2

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

መጋቢት 27 ቀን 2015 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም