መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የነቢያት ጉባዔ » የነቢያት ጉባዔ ክፍል 3

የትምህርቱ ርዕስ | የነቢያት ጉባዔ ክፍል 3

ነቢዩ ሙሴ ሲናገር የቍጣ መልክ ያየሁበት መሰለኝ ። ቍጠኛ የሚመስሉ ሰዎች ብዙ ጊዜ የዋህ ናቸው ። የሚናገሩትም በልባቸው ምንም ላለማስቀረት ነው ። ስሜታቸውን በቀላሉ ማግኘት ይቻላል ። ውስጣቸው የዋህ ነው ፣ ፍቅር ብቻ ያሸንፋቸዋል ። ለወደዱት ሟች ናቸው ። በሽንገላም ማንንም አያታልሉም ፣ የሰው ዕድሜም አይበሉም ። ሰው ግን እየተቆጣ ከሚያቀናው ሰው ይልቅ እየሸነገለ ገደል የሚከተውን ይወዳል ። እየገሠጸ ከሚያበላው ሰው ይልቅ ማሬ ፣ ሆዴ እያለ ጦም የሚያሳድረውን ይፈቅዳል ። እውነተኞች ኮስታራ ይመስላሉ ፣ ቁምነገርን ግን እንደ ልብስ ለብሰውታል ። ደልለው አዳሪዎች ግን በለስላሳ ምላሳቸው ይዳስሳሉ ፣ ልባቸው ግን ከዓለት የጠነከረ ነው ። ለመቅረብ ይሞክራሉ ፣ ውስጣቸው ግን የመንፈቅ መንገድ ያህል ሩቅ ነው ። ፊታቸውን ብሩህ ያደርጋሉ ፣ ልባቸውን ግን ያጠቁራሉ ። ጥርሳቸውን አጽድተው ብልጭ ያደርጋሉ ፣ ውስጣቸው ግን ከሲኦል ጨለማ ይልቅ የጠቆረ ነው ። የማያደርጉትን “እሽ” ብለው ሰውን እንደ ዶሮ ያባርራሉ ፣ እሺታቸው ግን ከእንቢታ የጠነከረ ነው ። “በጊዜው የሆነ እንቢታ ፣ የእሺታ ያህል ነው” እንዲሉ ።

እግዚአብሔር ቀናተኞችን ፣ ትኩሶችን ፣ ተቆርቋሪዎችን ፣ ግልጾችን ይወዳል ። ከመንፈሰ ቀዝቃዞች ጋር ፣ ከተወዛዋዥ ሬሳዎች ጋር ኅብረት የለውም ። አንድም ቅዱስ ቸልተኛና ዳተኛ አይደለም ። ቅዱሳን ሁሉ ትኩስ ናቸው ። ሊቀ ነቢያት ሙሴ ለእግዚአብሔር አምልኮ ፣ ለወገን ነጻነት የሚቀና ነበር ። ቀናተኞች ቅንዓታቸው ደፋር ያደርጋቸዋል ፣ እነርሱ በሕይወት ሳሉ ፈሪዎች ይሞታሉ ። እውነተኛ ደፋሮች የሚነካቸው የለም ። ነቢዩ ኤልያስ ለእግዚአብሔር አምልኮ ቀንቶ ፣ እንዴት በገዛ በረከቱ ይካዳል ? ብሎ ሰማይን በሰማርያ ላይ የገዘተ ፣ ምድርን ፍሬ አትስጪ ብሎ ያዘዘ ነው ። እግዚአብሔር ስለ ስሙ ሲቀኑ ከአሳባቸው ጋር ይተባበራል ። ዮሐንስ መጥምቅ የሚገሥጽ መምህር ፣ መልክ አይቶ የማያደላ መምህር ወመገሥጽ ነበር ። ቅዱስ ጴጥሮስ ስሜቱ ቶሎ የሚነካ ፣ ዛሬ ካልሆነ ብሎ ለበጎ ነገር የሚሽቀዳደም ነው ። ቦአኔርጌስ የነጎድጓድ ልጆች ወልደ ነጎድጓድ የተባሉት ዮሐንስና ያዕቆብ ትኩስ ነበሩ ። /ዘጸ. 32፡19፤ 1ነገሥ. 17፡1፤ ማቴ. 3፡7 ፤ ማር. 3፡17 ፤ ገላ. 2፡11/

ዛሬ “በጌታ ፍቅር እወድሃለሁ” የሚሉ በዘመድ ፍቅር እንኳ መውደድ ያቃታቸው ፣ ልባቸውና አፋቸው የተለያየባቸው ፣ ነቢያትና ሐዋርያት ያልወለዱአቸው ፣ ዘመኑን እንጂ ክርስቶስ መምሰል የማይሹ ናቸው ።

ባለቤቱ ራሱ፡- “ያዕቆብንም ወደድሁ ፥ ዔሳውንም ጠላሁ” ብሏል ። ሚልክ. 1 ፡ 2 ። እግዚአብሔር ግልጽ ነው ። ሦስተኛ ነገር የለውም ። ሲወድዱና ሲያዝኑ ግልጽ ማድረግ የመንፈሳዊ ሰው ጠባይ ነው ። አማኝ እንደሚያምነው እግዚአብሔር ነው ። አሁንም ባለቤቱ እንዲህ ይላል፡- ሦስተኛ ማንነትን ይጠላል ። “በራድ ወይም ትኩስ እንዳይደለህ ሥራህን አውቃለሁ ። በራድ ወይም ትኩስ ብትሆንስ መልካም በሆነ ነበር ። እንዲሁ ለብ ስላልህ በራድም ወይም ትኩስ ስላልሆንህ ከአፌ ልተፋህ ነው።” ራእ. 3 ፡ 15-16 ። የሚተፋው ለበራድነቱ ወይም ለሙቅነቱ ሳይሆን ለለብታው ነው ። ለብታነት ሚና የለሽነት ፣ አዎ አይደለም የማይል የሚንቀዋለል ማንነት ነው ። ሦስተኛ ሰፈር በሕይወት ውስጥ ሊኖር አይችልም ። የለብታ መንደር የለም ። እግዚአብሔር ሲወድድ አያፍርም ፤ ሲያዝንም አያንቀራብጥም ። ልጆቹም እርሱን ይመስላሉ ። ሽንገላን መጸየፍ የዲያብሎስን ራስ መርገጥ ነው ።

በአሳብ ብዙ ሄድሁ ። ወደ መጣሁበት ምድር ተመልሼ ኑሮአችንን ቃኘሁ ። ራሴን መክሬ ወደ ነቢዩ ሙሴ መልእክት ጆሮዎቼን አነቃሁ ።
ይቀጥላል

የነቢያት ጉባዔ/3

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

መጋቢት 28 ቀን 2015 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም