መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የነቢያት ጉባዔ » የነቢያት ጉባዔ ክፍል 6

የትምህርቱ ርዕስ | የነቢያት ጉባዔ ክፍል 6

ነቢዩ ሙሴ ወደ አሮንና ወደ ኢያሱ እያየ መናገሩን ቀጠለ፡-

“እኔ በጉልበቴ እስራኤልን ነጻ ላወጣ ተነሣሁ ። ነገር ግን ራሴን ለስደት ዳረግሁ ። “ጨው ውኃ ልትቀዳ ወደ ወንዝ ወረደች ፣ እንኳን ልትቀዳ እርስዋ ራስዋ ውኃ ሁና ቀረች” የተባለው ደረሰብኝ። በመጨረሻ ግን የራሴን መቃብር ቆፍሬ ተቀበርሁ ። ከአንድ ሚሊየን የሚልቅ ሕዝብን መርቼ አንድ ቀባሪ አልነበረኝም ። የእግዚአብሔር ሰው ቀብሩ ሳይሆን ኑሮው ፣ ሞቱ ሳይሆን ምርጫው ፣ መልኩ ሳይሆን እግሩ የሚያምር ነው /ሮሜ. 10፡15/ ። እናንተ አገልጋዮች ዓለም በዝና መቃብር ሳትቀብራችሁ ፣ የወርቅ ጉድጓድ ውስጥ ሳትጥላችሁ ፣ የአልማዝ ሸለቆ ውስጥ ሳታስራችሁ መቃብራችሁን ቆፍሩ ። ለዓለም ያልሞተ ለእግዚአብሔር መኖር አይችልም ። ለሚታየው ዓለም ያልሞተ ለማይታየው ዓለም መኖር አይችልም ። ሊቁ ልጃችን ቅዱስ አትናቴዎስ፡- “ዓለም ሁሉ ጠላህ” ቢሉት “እኔ አስቀድሜ ዓለሙን ጠልቼዋለሁ” አለ ይባላል ። ዓለምን ቀድሞ ያልናቀ ዓለም ስትንቀው ይደነቃል ። እንዳይሰድቡት ብሎ ይዋሻል ፣ እንጀራ እንዳይነሡት ብሎ ኅብስተ ሕይወት ክርስቶስን ይክዳል ። ዓለም ድንጋዩን ወርቅ አድርጋ ታሳያለች ። “ወድቀህ ካልሰገድህ አልሰጥህም” ትላለች ። ወድቀው ሲሰግዱ በድንጋዩ መትታ ትገድላለች ። በሽታ ከገደለው ምኞቱ የገደለው ይበዛል ።”

“እናንተ የልዑል ነቢያት አገልጋዮች ! ለእኔነታችሁ መሞት አለባችሁ ። እስራኤል ቀይ ባሕር ውስጥ ባይቀበሩ መና አይበሉም ነበር ። ከክርስቶስ ጋር ያልሞተም ለእግዚአብሔር ክብር መነሣት አይችልም ። ዓለም ተስፋ እስክትቆርጥባችሁ ፣ እናንተም በዓለም ተስፋ እስክትቆርጡ በሞት ሕግ መለያየት አለባችሁ ። ቤተ መንግሥቱ ያወራውን እናንተ መስማታችሁን የሚያረጋግጥ ፣ እናንተም የተናገራችሁት ነገሥታቱን ያላስከፋ መሆኑን ማዳመጥ ከማን የወረሳችሁት ባሕል ነው ?? ከምድራውያን ጋር ያላችሁን ርኵስ ጋብቻ ፣ የሰዎችን ፊት እያያችሁ ያላመናችሁበትን መናገር ፣ ሁለገብ ለመባል ጽድቁንም ኃጢአቱንም መባረክ ፣ አዋቂ እንዲሏችሁ መጽሐፋችሁንና ፍልስፍናን ማዛመድ ፤ ከደረጃችሁ መውረድ ፣ ራሳችሁን በራሳችሁ ማጥፋት ነው ። ለምእመን እየራራችሁ ለወደቀ አገልጋይ ግን የምትጨክኑ ፣ የምትሰብኩትን ምሕረት ለግላችሁ ብቻ እየተጠቀማችሁ ፣ ራሳችሁን በጸጋው ሌላውን በሕግ የምትዳኙ ፣ ከሥራ ይልቅ ሴራን የመረጣችሁ ፣ ለአንድ እንጀራ በእግዚአብሔር ስም መዋሸትን የደፈራችሁ ፣ በእናንተ ስብከት ሌላው እያመነ እናንተ የካዳችሁ እንዳትሆኑ እባካችሁ ተጠንቀቁ !! እኛ እዚህ በሰማይ ያለነው የእግዚአብሔርን ደግነት ፣ በመንግሥቱ ያለውን ሰማያዊ ግብዣ ባየን ጊዜ ወደ ምድር ሄደን ለማገልገል ተመኝተናል ፤ ግን አይቻልም ። ማገልገል ዕድል ነውና ተጠቀሙበት ።”

ሙሴ ይህን ሲናገር “ምነው አገልጋዩ ሁሉ ይህን በሰማ” አልኩኝ ። አንደኛው ልቤም፡- “እግዚአብሔር የሚናገረው ለመጣው እንጂ ላልመጡት አይደለምና ወደ ራስህ ተመልከት” አለኝ ።

ይቀጥላል

የነቢያት ጉባዔ/6

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ሚያዝያ 12 ቀን 2015 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም