የትምህርቱ ርዕስ | የነቢያት ጉባዔ

ክፍል አንድ

ሊቀ ነቢያት ፣ ታላቁ መስፍን ፣ ሊቀ ካህናት አሮንን የቀባው ታላቁ ካህን ፣ እግዚአብሔር ባሪያዬ ያለው ፣ የእግዚአብሔርን መልክ ያያል የተባለለት ፣ የሰው ሳይሆን የእግዚአብሔር ሎሌ የሆነው ፣ እጅግ ከፍ ያለው ፣ ነገር ግን በምድር ካሉት ይልቅ ትሑት የሆነው ሙሴ ወደ መድረኩ መጣ ። በዙሪያው የእስራኤልን ነገድ የወከሉ ሰባ ሽማግሌዎች እንደ አጃቢ በዙሪያው ተሰበሰቡ ። ዐቃቤ ሕግ ሙሴ ፣ ብሉይ ኪዳን ሲሰጥ መካከለኛ የነበረው ፣ ከልዑልነት እረኝነትን ፣ ከቤተ መንግሥት ሐቅለ ሲናን የመረጠው ፣ የአርባ ዓመቱ ልዑል ፣ የአርባ ዓመቱ ስደተኛ ፣ የአርባ ዓመቱ መሪ ፣ የገዛ መቃብሩን የቆፈረው ፣ ድንቅ ሰባኪ ሊናገር ሲል ነቢያት ሁሉ ፀጥ አሉ ። የሰማዩ አደባባይ በዝማሬ ውስጥ ፀጥታ ፣ በፀጥታ ውስጥ ዝማሬ አለው ። ሰማይ ሰላም ነው ። ለእግዚአብሔር እንጂ ለራሱ የሚኖር ማንም የለምና ፣ የእኔና የእኛ የሚል ሙግት በአርያም ዓለም የለም ። ሁሉም የእግዚአብሔር ነውና ሽብር የለም ። ሰው የራሱ ሲሆን ሞትን ይፈራል ። ሰው የሰው ሲሆን ሞቶ ይኖራል ።

ሙሴ ወደማይዘጋውና ሥራ ወደማይፈታው ታላቁ የሰማይ አደባባይ ሲመጣ ከአቤል እስከ ሚልክያስ ያሉ ነቢያት ሁሉም በታላቅ አክብሮትና እልልታ ተቀበሉት ። የድል ነሺዎች ማኅበርም ከአቤል ጀምሮ ያሉ ሁነቱን በአትኩሮት ይከታተሉት ነበር ። ምድርን ሁሉ የእኔ ይላታል ፣ ቀና ብሎ ወደ ሰማይ በማየት ግን ሰማይን የእኔ ማለት አይቻልም ። ሰማይ የሁሉ ነው ። ሰማይ ቢፈካ ፣ ቢጨግግ ማንም መለወጥ አይችልም ። ሰማይ ጥያቄ የሌለበት ነው ። እኔም በዚህ የሰማይ ማኅበር ላይ ራሴን ሳገኘው የእኔ የሚል ነገር እስካጣ ሁሉም የእግዚአብሔር ፣ ሁሉም የእኔ ሁኖ ይሰማኝ ነበር ። እጅግ ድህነት እጅግ ባለጠግነት እንዲህ ተሰምቶኝ አያውቅም ነበር ። አቤል የመጀመሪያው ሰማዕት ነው ፣ የመጨረሻው ግን አልነበረም ። የመጨረሻ ከሆንን የመጀመሪያዎች አሉ ። የመጀመሪያ ከሆንም የሚቀጥሉት ይመጣሉ ። ኤልያስ ብቸኛ ነኝ አለ ። በምድርም በሰማይም ግን ብዙ አጋሮች ነበሩት ። ወገን የሌለው ብቸኛ ሃይማኖት የለም ። በሰማይም በምድርም ብዙ ወዳጆች አሉን። ኢዮብ ልጆቹ ቢሞቱም በሰማይ አሥር ልጆች ፣ በምድር አሥር ልጆች ሁነውለት የሃያዎች አባት ሆነ ። እግዚአብሔር አውቆት የሚባክን በሰማይ የተቀመጠ እንጂ የጠፋ አይደለም ። ባለመጥፋትና ባለመታጣት የሚመለክ እግዚአብሔር ነው ። እነዚህ ሁሉ አባቶች እንደ ደመና በዙሪያዬ አሉ ። ደመና ቢቆለልም አያስጨንቅም ። ደመና ባናት ላይ ቢሆንም ቀጥሎ ዝናብ የሚያፈስስ ነው ። የቅዱሳን ገድልም የእውነት ጠል ነው ።

ይቀጥላል

የነቢያት ጉባዔ/1

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

መጋቢት 24 ቀን 2015 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም