መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የአሳብ ውጊያ » የአሳብ ውጊያ /4

የትምህርቱ ርዕስ | የአሳብ ውጊያ /4

1- የክስ ስሜት

ይህ ዓለም በጥፋታቸው ይቅርታ የማይጠይቁ ደንዳና ሰዎች ያሉበትን ያህል ያለ ጥፋታቸው ደግሞ በሰይጣን ክስ የሚሰቃዩ ደንባራ ሰዎች የሞሉበትም ነው ። ዓለምን ፍትሐዊነት የሚያሳጣት ይህ ይመስላል ። የክስ መነሻው ብዙ ነው ። ማንኛውም ውስጣዊ ክስ ግን ከሰይጣን ነው ። መንፈስ ቅዱስ ይወቅሳል ፤ ሰይጣን ደግሞ ይከስሳል ። ወቀሳ መነሻው ፍቅር ፣ መድረሻው የኃጢአተኛው መዳን ነው ። የክስ መነሻው ጥላቻ ፣ መድረሻው በደለኛውን ተስፋ ማስቆረጥ ነው ። የሕሊና ክስ ፣ የሰዎች ክስ ፣ ሰይጣን ክስ ያለበት ዓለም ነው ። እነዚህ ሦስት ከሳሾች በተጨበጠና ባልተጨበጠ ክስ ሊያሳድዱን ይችላሉ ። ሕሊናም ፣ ሰዎችም ሆኑ ሰይጣን ሊከስሱ ቢችሉም ይቅርታ መስጠት ግን አይችሉም ። የእግዚአብሔር ይቅርታ ከሕሊና ፣ ከሰዎችና ከሰይጣን ክስ በላይ ነውና እርሱ ይቅር ያለውን ማንም ሊከስሰው አይችልም /ሮሜ. 8 ፡ 33/። ያለፈው ስህተታችን ፣ የዛሬው ውድቀታችን ፣ የሚመጣው ስጋታችን ክርስትናችንን ልበ ሙሉ ሁነን እንዳንኖረው ያደርገናል ። ሰውን ሰው የሚያሰኘው እግዚአብሔርን በንስሐ ፣ የበደላቸውን ሰዎች ደግሞ በይቅርታ ክሶ የቀደመ ፋይሉን መዝጋት የቻለ ነው ። ያለ መበደልን ያህል በበደል መጸጸት ትልቅ ዋጋ አለው ። የንስሐ መንፈስ እምነትም ምግባርም ነው ። ንስሐ አያስፈልገኝም የሚል ደግሞ እምነትም ምግባርም የሌለው ከሀዲና ዓመፀኛ ነው ።

የጥፋተኝነት ስሜት ከባድ የሆነ ስቃይ ያለው ነው ። ጠላቶች ደጋግመው በሚሰጡን ክፉ ስም እውነት ያጠፋን የሚመስለን ጊዜ አለ ። ሰይጣን አንድን ነገር ደጋግሞ በማስወራት ያ ስሜት እንዲሰማን የማድረግ የውጊያ ስልት አለው ። ሌላ ጊዜም በምናደርገው መልካም ነገር ፍቅርን ለመግዛት ስንፈልግ የትዳር ጓደኛችንን ፣ ልጆቻችንን ያስቀየምን እየመሰለን የጥፋተኝነት ስሜት ውስጥ እንገባለን ። ኃይለኛና ሞገደኛ የሆኑ ሰዎች ጋር ስንኖርም የሁልጊዜ ቍጣቸው ራሳችንን እንደ በደለኛ እየቈጠርን እንድንኖር ያደርገናል ። አንዳንድ ጊዜ የትዳር ጓደኛችንና ልጆቻችን ይህን ደካማ ስሜታችንን ካወቁ ለማንበርከክና የፈለጉትን ለመቀበል ድራማ ይሠሩብናል ። ያኮርፉናል ፣ በር ዘግተው ይቀመጡብናል ፣ ስልክ አያነሡልንም ። በዚህ ጊዜ ያልበደልነውን መናዘዝ እንጀምራለን ። እየተለማመጥን በመኖር ከሰውነት ልክ ወርደን በውሻ ደረጃ እንገኛለን ። የሚገርመው ይህን ያህል መገዛት ለእግዚአብሔር አድርገን አናውቅም ። የሚያኖረን እግዚአብሔር መሆኑን ረስተን መኖራችን በሰው ላይ የተመሠረተ ከመሰለን ይህ እምነትን መጣል ነው ።

የሰው ታዛዥና ሎሌ የሆነው በክርስትና ትምህርት ተገርተን ከሆነ መልካም ነው ። ነገር ግን ሰዎችን ፈርተን ከሆነ ራሳችን ላይ ወጥመድ ይዘን እንዞራለን ። እነዚያን ሰዎች ካጣን ሕይወታችን የሚያከትም መስሎ እየተሰማን የሰው ጣዖት አቁመን እንሰግዳለን ። ይህ ፍርሃትና አለመረጋጋት ያመጣብናል ። እምነታችንን ወስዶ ዕራቈታችንን ያስቀረናል ። መኖር ግን በእግዚአብሔር ነው ። ሊሄድ የወደደውን በደስታ መሸኘት እንጂ እየሰገዱ መኖር ያንንም ሰው ማባለግ ነው ።

በክስ ስሜት ወይም በጥፋተኝነት ሕመም የሚሰቃዩ ሰዎች የአሳብ ውጊያ አለባቸው ። በትክክል አጥፍተው ከሆነ እግዚአብሔርን በንስሐ ፣ ሰዎችን በይቅርታ መቅረብ አለባቸው ። ሰው ሁኖ የማይበድል ፣ እንጨት ሁኖ የማይጤስ የለምና ። ቤተ ክርስቲያንም የተነሣሕያን ማኅበር እንጂ የፍጹማን ኅብረት አይደለችም ። በቤተ ክርስቲያን ያለው አገልግሎት በሙሉ ከስርየት ጋር የተያያዘ ነው ። ጸሎት ፣ ጥምቀት ፣ ቍርባን … የንስሐ አገልግሎት ነው ። ቤተ ክርስቲያን በደለኞች ባይኖሩባት ኖሮ የንስሐ ጸሎት በየሰዓቱ አታደርስም ነበር ። እነዚህ በጥፋተኝነት ስሜት የሚሰቃዩ ሰዎች አላጠፉ እንደሆነ ይቅርታ መጠየቅ አይገባቸውም ። ያለ ጥፋት ይቅርታ መጠየቅ ጥፋተኛ ሰውን ማባለግ ነው ። ለእውነት ዋጋ እየከፈልን እንጂ እውነትን እየሠዋን የምንመሠርተው ፍቅር ዕድሜ የለውም ።
በጥፋተኝነት ስሜት የሚመጣው የአሳብ ውጊያ ዋነኛ መሪው ሰይጣን ነው ። ሰይጣን ተከሳሹ ከሳሽ ነውና ልንፈራው አይገባንም ። በደላችን የእኛና የእግዚአብሔር ጉዳይ እንጂ የማንም አይደለም ። የእግዚአብሔር ፖሊስ ነን ብለው የሚያስቡ ሰዎችንም መፍራት አይገባንም ። መፍራት አንድ አምላክን ብቻ ነው ። በጥፋተኝነት ስሜት የሚመጣብን የአሳብ ውጊያ አለ ። መፍራት ፣ ሁሉም ሰው ጻድቅ ሁኖ እኛ ብቻ የረከስን መስሎ እንዲሰማን ያደርገናል ። ቤተ ክርስቲያን ብንሄድ ሰይጣን እንዳለበት ሰው የምንጮህ ፣ የእግዚአብሔር ሰዎችን ስንቀርብ ቀሚሳቸው የሚያቃጥለን መስሎ ይሰማናል ። መፍትሔው ስህተቱ ካለ ንስሐ ገብቶ መርሳት ነው ። ምክንያቱም እግዚአብሔር የረሳውን ማስታወስ ነውር ነውና ። ስህተቱ በሌለበት ያለ የአሳብ ውጊያ ግን ከሰይጣን ነውና በስመ እግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ ከእኔ ራቅ ማለት ይገባናል ። ትላንትን ቢያስብ ሐዋርያው ጴጥሮስ ከሀዲ ነበር ። ሐዋርያው ጳውሎስ እስጢፋኖስን ያስገደለ ነው ። የትላንቱን ካልረሳን ወደፊት መዘርጋት አይቻልም ፊልጵ. 3 ፡ 13 ።

አቤቱ ልቡናችንን ግዛው!

ይቀጥላል

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም