የትምህርቱ ርዕስ | የአዞ እንባ


በተለምዶ “የአዞ እንባ” ሲባል እንሰማለን ። አዞ ጥቅጥቅ ባለው ቆዳው አማካይነት ላብ ስለማይወጣው በዓይኑ አማካይነት ላቡ እንባ መስሎ ይፈስሳል ። ከ62 እስከ 66 በሚጠጉት ጥርሶቹ ሥጋ የሚቆርጠው አዞ ተንቀሳቃሽ ምላስ የሌለው መዋጥ እንጂ ማኘክና ማላመጥ የማያውቅ ነው ይላሉ ስለ እርሱ ያጠኑ አዋቂዎች ። በዚህ ሰዓት ላይ ብዙ ሥጋ ቆርጦ ከዋጠ ጉሮሮው ስለሚጨናነቅ ላብ ያልበዋል ፣ ላቡም በዓይኑ በኩል ይፈስሳል ። የአዞ እንባ ላቡ ነው ። በብዛትም የሚታየው ሲበላ ነው ። አዞ እየበላ የሚያለቅሰው ላቡን ለማውጣት እንጂ አድኖ በመብላቱ ተጸጽቶ አይደለም ። እየበላ ያለቅሳል ፣ እያለቀሰ ይበላል ። አዞ ያስለቅሳል እንጂ አያለቅስም ። የዋሃን እንባውን አይተው ያለቅሳሉ ፣ እርሱ ግን ላቡን ያወጣል ። የአዞ እንባ ፈሳሽ እንጂ ስሜት የለበትም ። እንባው ደስታንም ኀዘንንም የሚገልጥ ሳይሆን ዓይኑ የላብ ቦይ በመሆኑ የመጣ ነው ። አስመሳይ ሰዎች ፣ እንባ ናልኝ እያሉ ሲጠሩት የሚመጣላቸው ፣ ቆየኝ ሲሉት የሚቆምላቸው ፣ በአጭር ቃል እንባ ሎሌ የሆነላቸው ፣ የውሸት አልቅሰው የእውነት የሚያስለቅሱ ሰዎች የአዞ እንባ የሚል ስያሜ ተሰጥቷቸዋል ።

ጠንካራ ማንነት ያላቸው ፣ ጥቅጥቅ ልብ የያዙ ፣ ለፍቅር ክፍተት የሌላቸው ፣ አድፍጠው መኖር ፣ የማያዩአቸውን እያዩ መሳቅ የሚፈልጉ ሥጋ በል የሆኑ ፣ ሰውን ካልጠለፉ ደስታ ፣ ካላጠፉ እንቅልፍ የሌላቸው ሰዎች በምድር ላይ አሉ ። አዞ መሰሏን ለመውለድ ብዙ ጥንቃቄ ታደርጋለች ። ፈሪሳውያን እንደ እነርሱ የከፉ ሰዎችን ለማምረት ቆላ ደጋ ይማስኑ ነበር ። ልፋት ሁሉ ልፋት አይደለም ። ዲያብሎስም ከወደቀ ጊዜ አንሥቶ ያለ ደመወዝ ይለፋል ። ውጤቱ ግን ለገሀነመ እሳት የሚያበቃ ነው ። ጌታችን፡- “እናንተ ግብዞች ጻፎችና ፈሪሳውያን ፥ አንድ ሰው ልታሳምኑ በባሕርና በደረቅ ስለምትዞሩ ፥ በሆነም ጊዜ ከእናንተ ይልቅ ሁለት እጥፍ የባሰ የገሃነም ልጅ ስለምታደርጉት ፥ ወዮላችሁ” በማለት ገሥጾአል ። ማቴ. 23 ፡ 15 ። አዞ የተፈለፈሉ ልጆችዋን ባሕር ውስጥ ከመክተትዋ በፊት ትንንሽ ነፍሳትን እንዲበሉ ሣር ላይ ትተዋቸዋለች ። መሰላቸውን ከልጅነት ጀምሮ ክፋትን የሚያለማምዱ ፣ የክፋትን የዕድገት ሕግ የሚያከብሩ ፣ ለመኖር ሌላውን መግደል አለብህ በማለት ትውልድን የሚያሰለጥኑ ፣ እነርሱ ትልልቅ ገዳይ ሳሉ ልጆቻቸውን ትንንሽ ገዳይ አድርገው ፣ በልጆቻቸው ልክ የገሃነም ቀሚስን የሚሰፉ አያሌ ናቸው ። ስግብግብነት ሁሉም የእኔ ይሁን ባይነት እንደ ሰዎች ተፈጥረን እንደ አራዊት የምንኖርበት ጠባይ ነው ። እግዚአብሔር የመረጠልን ሰውነት ከጠዋቱ ሕጻንነትና መልአክነት የነበረው ነው ። ከእግዚአብሔር የተቀበልነው ገራም ተፈጥሮ ነው ። ያዳበርነውና የመረጥነው ግን አራዊታዊ ጠባይ ነው ።

አዞ በባሕር ፣ በየብስና በዛፍ ላይ መቆየት ይችላል ። ሁሉም ቦታ ላይ ግን የእኔ ነው ብሎ ሊተናኮል ይችላል ። ልካቸውን የማያውቁ ፣ ድምበርተኛ አልፈልግም ብለው ሁሉንም መጠቅለል የሚሹ ፣ የራሳቸውን የግላቸው ፣ የሌሎችን የእኔ ብለው የሚያስቡ ሰዎች በምድር ላይ መኖራቸው እርግጥ ነው ። አዞ ረሀቡን በቅጠል የማስታገሥ የማይችል ፣ ካልገደለ የማይበላ ነው ። ባልተገራ ፍላጎትም ለአንድ ሆዳቸው ሺህ ገዳይ የሆኑ ጨካኞች በምድር ላይ ከተከሰቱ ብዙ ዘመን ሁኗቸዋል ። ቃየንም መሪያቸው ሁኖ ይኖራል ።

ሕይወትን ለማጣጣም ፣ በልኩ እየኖሩ የቀኑን ሲሳይ ተቀብለው ለማመስገን የማይፈልጉ በመዋጥ ብዙ ተጨንቀው የሚያስጨንቁ በዚህች ዓለም ላይ ተከስተዋል ። የእኔ አሳብ ብቻ ይደመጥ የሚሉ ፣ የሌሎችን እምነትና ባህል ደፍጥጠው በማለፍ የሚረኩ አያሌ አሉ ። መደመጥ የሚፈልግ ሰው ማድመጥ አለበት ። ማድመጥ መቻል የሰውን የልብ ሰላም ማሳያ ነው ። ሰው ሲታወክ ማውራት ብቻ ይፈልጋል ። ራሱ ጣኦት ሲሆንበትም እኔ ካልኩት ውጭ አዲስ አሳብ የሚያመጣ ጠላቴ ነው ይላል ። ብዙ ሰብስበው ለመዋጥ ጉሮሮአቸው የተጨናነቀባቸው በዚህ ምክንያት የሚሰቃዩ አሌ የማይባሉ ናቸው ። መሰብሰብ ይቻላል ። መብላት ግን እግዚአብሔር ሲፈቅድ ነው ። አውሬ እንኳ ከጠገበ አይተናኮልም ፣ የሚያድነው በቂም ሳይሆን በረሀቡ ምክንያት ነው ። ሰው ግን ጠገብኩ የማይል ሁልጊዜ የሚስገበገብ መሆኑ አሳዛኝ ነው ። ይህ ዘመን የሚያስተምረን ነገር ቢኖር ንብረት ከንቱ መሆኑን ነው ። እግዚአብሔር የገንዘብን ትምክሕት ሊሰብር ቆርጦ ወጥቷል ። “በኪሱ ሳንቲም የሌለው ከሽፍቶች መንደር ሲደርስ ያቅራራል” ይባላል ። በዚህ ዘመንም ተረጋግቶ እየኖረ ያለው ምንም የሌለው ድሀው ነው ። ሲሰበስብ የታወከው ባለጠጋ ሊበላ ሲልም ሁከት ይገጥመዋል ። ብቻ ትምክሕት እንደዚህ ዘመን ቶሎ ቶሎ ሲፈርስ አልታየም ።

እንባ አንድ ትርጉም ብቻ ያለው ከመሰለን ሞኝነት ነው ። እንባ እንደ አዞ ጠባይ ከሆነ ላብ ማስወጣት ነው ። እንባ ፊልም የሚሠሩበት ፣ በሚያስለቅስ ቅባት የሚያለቅሱበትም ነው ። እንባ ደስታን መግለጫ ፣ ኀዘንንም ማውጫ ነው ። እንባ የሰዎችን ስሜት ወክሎ የሚታይ መልእክተኛ ነው ። እኔ ቀብር መውጣት አልቻልኩም አንተ ሂድልኝና ታይልኝ ብሎ ስሜት የሚልከው እንባን ነው ። ራሳቸው በድለው ራሳቸው የሚያለቅሱ ፣ በሁልጊዜ ትክክለኛነት ስሜት የሚኖሩ ፣ ዓለሙ ሁሉ በድሎ እኔ ብቻ ቀረሁ የሚሉ ፣ ጌታዬ ብለው የሚጠሩትን ባልም ይሁን አለቃ በእንባ ላሳምን የሚሉ ደካማ ሰዎች አሉ ። ሙሉ አካል እያላቸው ሠርተው መብላት ሲችሉ ነገር ምሰው ፣ ሰው አፋጅተው ይኖራሉ ። ሰው ያወቀባቸው ሲመስላቸው ዕድሌ ነው ብለው ያለቅሳሉ ። መኝታቸው ላይ ሆነው ለፍጅት የሚያነሣሡ ለራሳቸው ግን አካላቸውንና ጥቅማቸውን ጠብቀው የሚኖሩ፣ የአስመሳይነት እንባቸውን ግን ጊዜ ባመጣው መሣሪያ ቀርጸው የሚልኩ ዘመናዊ ነጋዴዎችን እናያለን ። አገራቸውን በዘፈን ብቻ የሚወዱ ፣ ወገናቸውን በከንፈር ፉጨት ብቻ እናዝንልሃለን የሚሉ የአዞ ዘመዶች አሉ ። አልቃሽ ራስዋ አታለቅስም ። ኩሏን ተቀብታ ልቅሶ ትወጣለች ኩሉ ሳይበላሽ ትመለሳለች ። ዓይንዋ ድንጋይ ከሆነ ሰንብቷል ። ደረቷን አትመታም ። የሰው ደረት ሲፈርስ ግን ደስ ይላታል ። አዞ እንባ ቢወጣውም እያለቀሰ አይደለም ። ቢያስለቅሰም አያለቅስም ። እየበላ በማንባቱ የሚያዝን የሚመስል ፣ እያለቀሰ በመብላቱ የምበላህ ላንተ ብዬ ነው የሚል አስመሳይ ነው ።

አስመሳይነት ፣ ዋሽቶ አዳሪነት የአዞ እንባን ይወልዳል ። እውነትን ዋስ መጥራት የማይችሉ እንባን “ቶሎ ናልኝ ፣ ልጠቃ ነው ፤ ድረስልኝ” በማለት የየዋሃንን ልብ የሚጠመዝዙ ፣ ደጉን ሰው ከሚወዳቸው ጋር እንዲጣላ ፣ ከልጅ ከሚስቱ እንዲለያይ የሚያደርጉ ሰብቀኞች የአዞ እንባ ተብለው ይገለጣሉ ። ቲያትራቸውን ሲጨርሱ የደስታ ሻማ የሚያበሩ ፣ እናትና ልጅ በማጣላት ግን የተጉ ብዙ ናቸው ። እውነተኛነትና “መኖር በእግዚአብሔር ነው” ብሎ ማመን ከአዞ እንባ ያድናል ። ጥገኝነት የአዞ እንባን ይወልዳል ፣ ጨካኝነትም የአዞን እንባ ያመጣል ፣ በልክ አለመብላትም የአዞን እንባ ይከስታል ።

አንድ አባባል አለ፡- “የውሸት ብንኖርም የምንሞተው ግን የእውነት ነው ።” የእውነት እንሞታለንና የውሸት አንኑር።

እግዚአብሔር በሰላሙ ይባርካችሁ ። አሜን ።

የብርሃን ጠብታ 22

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ኅዳር 15 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም