መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » የአዳም ተስፋ

የትምህርቱ ርዕስ | የአዳም ተስፋ

የበደለ አዳም ቀና ብሎ ይሄድ ዘንድ ዳግማዊ አዳም ሁኖ መጣ ፣ የስህተት በር የሆነችዋን ሔዋንን ያጽናና ዘንድ ክርስቶስ ከሴት ዘር ተወለደ ። ገነትን ላጣው አዳም ራሱ ክርስቶስ ገነት ሆኖለት መጣ ። ስጦታውን ቢያጣ ሰጪው ዘመዱ ሆነ ። ስጦታው የተፈጠረ ነው ፣ ሰጪው ግን ያልተፈጠረ ነው ። አዳም ሰማይና ምድር የእርሱ ቢሆኑ ያለ ጌታ ኀዘን እንጂ ደስታ አይሆኑትም ነበር ። የሰማይና የምድር ጌታ ለመሆን አስቦ ከሰይጣን ጋር መከረ ፣ እንኳን ሰማይን ሊያተርፍ ግዛቱ የሆነችውን ምድር አጣ ። ክርስቶስ ግን በመወለዱ የሚታየውን ብቻ ሳይሆን የማይታየውን ዓለመ መንፈስ ፣ ሰይጣንንና ደዌያትን ይገዛ ዘንድ ባለሥልጣን ሆነ ። ተጠቃን የሚሉ ወንድ ልጅ ሲወልዱ ስሙን ደምመላሽ ይሉታል ። ክርስቶስም ርስትን ይመልስልን ዘንድ ፣ ጠላትንም ይበቀል ዘንድ ወንድ ልጅ ሆኖ ተወለደ ። ክርስቶስ በወንድ አምሳል ስለ መጣ ወንድ ልጅ ክቡር ነው ። ክርስቶስ ከሴት ዘር በመወለዱ ከድንግል ማርያም የተነሣ ሴት ሁሉ ክብርት ናት ። የሄደችውን ገነት አዳም በእንባ ፣ አበው በምግባር ፣ ካህናት በመሥዋዕት ፣ ነቢያት በናፍቆት ሊያስመልሷት አልቻሉም ። ክርስቶስ ግን በመወለዱ የሰማይ በር ተከፈተ ። አዳም በወደቀ ቀን አጋንንት ዘፍነዋል ፣ ክርስቶስ በተወለደ ቀን መላእክት ዘመሩ ። ዛሬም በክርስቶስ ልደት የሚዘፍኑ ፣ የሚሰክሩ በአዳም የውድቀት ቀን ከተደሰቱ አጋንንት ጋር ይተባበራሉ ። አዳም ሳይወልድ በመበደሉ አንድ ራሴን ነኝ ብሎ ተመክቶ ነበር ። ነገር ግን የአባት ዕዳ ለልጅ ይተርፋልና ልጆቹ በደለኛ ሆኑ ። በአንዱ አዳም የተኰነኑ ፣ በአንዱ ክርስቶስ ጻድቃን እንዲሆኑ ፣ ሚዛንም እንዲተካከል ይህ ሆነ ።

አዳም በገደል ላይ በመጫወቱ ከጥልቁ ወደቀ ። ነገሥታትና ጠቢባን ከገደል ሊያወጡት አልተቻላቸውም ። ምድራዊ ሥልጣን ማዕሠረ ኃጢአትን ሊበጥስ ፣ ምድራዊ ጥበብም መቃብርን ሊበዘብዝ አልቻለም ። ክርስቶስ ግን ጠቢብ ድሀ ሆኖ መጣ ። ጌትነትን ተመኝቶ የሞተው አዳምን ፣ ክርስቶስ ክብርን ንቆ ሊታደገው መጣ ። የከፍታው ምሥጢር ዝቅታ መሆኑን ሊያስተምረው ክርስቶስ በበረት ተወለደ ። ሔዋን ደመኛው ሆና ብትታየው ፣ በእርስዋ ላይ ቢነሣሣባት የመዳኛውን ዘር ያጣው ነበረ ። አዳም ይቅርታ በማድረጉ ክርስቶስን አገኘ ። ከክርስቶስ የለዩን አንድ ዘመን ላይ ወደ ክርስቶስ ያቀርቡናል ። እግዚአብሔር ታሪክን ሲለውጥ ከበደሉን በላይ ይክሱናል ። ከቆሸሸው በላይ የሚያጸዳ ባለሙያ አለ ። ትልቁ ባለሙያ እግዚአብሔር ምድራዊት ገነትን ላጣው አዳም ሰማያዊ ርስትን ሰጠ ። በልጅነት ላይ ክህነትን ደረበለት ። መበቀል የፍጡር ጠባይ ነው ። እግዚአብሔር ግን ኃይሉን በይቅርታ ገለጠ ። ይቅር የሚሉ የሁልጊዜ ብርቱዎች ናቸው ። መግደል ብዙዎች ችለዋል ፣ ይቅር ማለት ግን አልቻሉም ። ይቅርታ የልዕልና መገለጫ ነው ። አባቶችን ከተቀየምን መጀመሪያ የምንቀየመው አዳምን ነው ። አዳም የወደቀባትን ቦታ ሳይሆን የተነሣባትን ጎልጎታ እናስታውሳለን ።

አዳም ገነትን በራሱ አጣ ፣ በክርስቶስ እንደሚያገኛት ተስፋ አደረገ ። ሰው ተስፋ ሰጥቶ ይጸጸታል ። እግዚአብሐር ግን ተስፋን እንደ ክብሩ እንጂ እንደ ዕዳ አያየውም ። አዳም መውደቅ በቻለበት አቅም መነሣት አልቻለም ። ያለ መካሪ የበደሉ ሰዎች በመካሪ ኃይል ሊነሡ ይቸገራሉ ። ሰውን ከኃጢአት የሚያላቅቀው ነጻ ፈቃዱ ከኃይለ መንፈስ ቅዱስ ጋር ሲዛመድ ነው ። አዳም በሰማይና በምድር ብቸኛ ሆነ ። ጥቂት ዘመን በደስታ ኖሮ 5500 ዘመን በስቃይ አሳለፈ ። አዳም አባት እናት አልነበረውም ፣ አባትና እናቱ እግዚአብሔር ነበረ ። አዳም ሙሉ ስሙ ሲጠራ “አዳም ወልደ እግዚአብሔር በጸጋ” ይባል ነበረ ። አባትና እናትህን አክብር የሚለውን ትእዛዝ አዳም ሻረ ። አዳም በገነት ውስጥ አነጋጋሪው ፣ የብቸኝነቱ መድኃኒት እግዚአብሔር ነበረ ። አሁን ግን ወዳጁን አጣ ። እግዚአብሔርም በወዳጁ ቤት ቆሰለ ። ክርስቶስ ሰው የሆነው ለአዳም ያለውን ፍቅር ለመግለጥ ፣ የወጣ እንደ ወጣ ይቅር የማይል አምላክ መሆኑን ለማስታወቅ ነው ።

አዳም የሠላሳ ዓመት ጎልማሳ ሁኖ ተፈጠረ ። ክርስቶስ ግን ሊያድነው የዕለት ሕፃን ሆኖ በበረት ተጣለ ። አዳም በገነት ብቻውን ነበረ እንጂ ብቸኛ አልነበረም ። ምክንያቱም እግዚአብሔር ያለው ብቸኛ አይባልምና ። አሁን ሔዋን አጠገቡ ሳለች ብቸኝነት ተሰማው ። ብቸኝነት ያለ ሰው ሳይሆን ያለ እግዚአብሔር መሆን ነው ። አዳም ተስፋው የክርስቶስ መወለድ ነበረ ። ይኸው ተወለደ ። እርሱ አሻግሮ መወለዱን አየ ፣ እኛ መለስ ብለን መወለዱን አስተዋልን ። ዕለት ዕለት ክርስቶስ መወለዱን የሚያምኑ ጥሙቃን /ተጠማቂዎች በቤተ ክርስቲያን ይገኛሉ ። የእኛ አምላክ አብ የሚወልድ ፣ የእኛ ጌታ ክርስቶስ የሚወለድ ነው ። ሰው በመሆኑ አምላክነቱን አልከሰረም ። ጌታቸው ባለበት መላእክቱ ተገኝተው ምስጋናውን አቀረቡለት ። የዘላለም አባት ፣ በሕፃን መልክ ሲገኝ በመደመም ዝም አሉ ። ቅዱስ ገብርኤል ምን ቢያበስር ይህን የልደት ምሥጢር መልመድ አልቻለም ። እኔ ድሀው ከመላእክት አእምሮ በላይ ለሆነው ልደትህ ክርስቶስ ሆይ ሰላም እላለሁ !

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ታኅሣሥ 24 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም