መግቢያ » መጽሐፍ ቅዱስ » አዲስ ኪዳን » ኤፌሶን ትርጓሜ » የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ ጳውሎስ

የትምህርቱ ርዕስ | የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ ጳውሎስ

እግዚአብሔር የለም በሚባልበት ዘመን አንድ አገልጋይ የሆኑ ሰው ዘመን ወዳመጣው ክህደት ተሳቡ ። በአደባባይም “እስካሁን በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ስንል ኖረናል ፤ ከዚህ በኋላ ግን በስመ ሌኒን ወማርክስ ወኢንግልስ አሐዱ ሶሻሊስት እንላለን” አሉ ። እኒህ ሰው ዘመኑን ለመምሰል ብለው የጀመሩት ከመጨረሻው ኃጢአት ነው ። ሰይጣን እንኳ ሀልወተ እግዚአብሔርን አይክድም ። ሰው ግን ደፋር ነው ። የማይሞተውን አምላክ በሚሞቱ አብዮተኞች መተካት ያሳዝናል ። እግዚአብሔር የለም ብለው ዓለምን ያስካዱ አገሮች ካሉ የመጀመሪያዋ ሩስያ ናት ። ትርፏም እልቂትና ውድቀት ነበር ። ዛሬ በሩስያ ሁሉም አማኝ ነው ። የሀገሪቱ መሪም አስቀዳሽ ናቸው ። “ዓርብ ረቡዕን ገደፍን በሥጋ ባዋዜ ፣ እንዲህ ለሚያልፈው ለማይቆየው ጊዜ” ተብሏል ። ግጥሙ ዓርብ ረቡዕ ሥጋ መብላት የተራማጅነት ምልክት ተደርጎ የተወሰደበትን ዘመን ያስታውሰናል ። አንዳንድ ዘመን ከባድ ነው ። ካህንን ከሀዲ ፣ ሰባኪን ፖለቲከኛ ያደርጋል ። እኒህ ከላይ የጠቀስናቸው ሰው የአብዮቱ አጋር ፣ የእግዚአብሔር የለሽ ሥርዓት መልእክተኛ ለመሆን ብለው ይህን አደረጉ ። ዘመን ከሚያልፍብኝ ዘላለም ይክዳኝ አሉ ። ለሚያልፍ መንግሥት የማያልፈውን መንግሥተ ሥላሴ ለማጣት ወሰኑ ። ሒሳብ እንኳ አያውቁም ነበር ። የሚገርምው የእኒህ ሰው ደመወዝ ከቤተ ክርስቲያን ነበር ። ከእግዚአብሔር ቤት እየጎረሱ ወደ ዓለም የሚውጡ ጥንትም ዛሬም አሉ ። እርሳቸው ደመወዝ የሚበሉት እግዚአብሔር አለ ብለው የሚያምኑ ምእመናን በሰጡት አሥራት በኵራት ነው ። የእግዚአብሔር መኖር ለእርሳቸው እንጀራ እንኳ አስፈላጊ ነው ። በእምነት በተሰበሰበ አሥራት ከሀዲዎችን ማገልገል ግን ይገርማል ። መድኃኔ ዓለም እየጠሉትም እንጀራ ነው ።

ብዙ የነገረ መለኮት ተቋማት ሰዎች በእምነት ገብተው በእውቀት የሚወጡበት ፣ አንዳንዶችም እምነታቸውንና ሞራላቸውን የሚከስሩበት ነው ። መንፈሳዊ ትምህርት በመንፈሳዊነት ካልተሰጠ ፣ ነገረ መለኮት ከአምልኮተ እግዚአብሔር ጋር ካልቀረበ አደጋው ትልቅ ነው ። ቢሆንም የነገረ መለኮት ተቋማት አማንያን በሚያወጡት አሥራት በኵራት የተቋቋሙ ናቸው ፣ ስለዚህ ከሀድያን እንዳይወጡባቸው ጥንቃቄ ማድረግ ይገባል ።

የዘመን ሐዋርያ የሆኑ ሰዎች ራሳቸውን የለውጥ ሐዋርያ ብለው ይሰይማሉ ። በእግዚአብሔር ቤትም የፖለቲካ ወኪል ይሆናሉ ። ከእግዚአብሔር ካህንነት የመንግሥት ካድሬነት ፣ ከመላእክት ጥበቃ የደኅንነቶች ስልክ ቍጥር ፣ ከሰማይ ቤት የቁጠባ ቤትን ይመርጣሉ ። ዋጋቸውን አሳንሰው ፣ በሰማይ ጀምረው በምድር የሚጨርሱ ናቸው ። ይቅርታን የሰበከ ቂምን ሲዘራ ፣ አንድነትን የተረከ መለያየትን ሲያውጅ ፣ አማኒው ስሜታዊ ሲሆን የዘመን ሐዋርያ ሁኗል ማለት ነው ። ቢሆንም ለሚያልፍ ቀን የማያልፍ ንግግር መናገር ተገቢ አይደለም ። ቅዱስ ጳውሎስ ግን የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ ነበር ።

ሐዋርያነት ከማዕረግ ይልቅ ሥራን የሚያሳይ ነው ። ራሳቸውን ሐዋርያት ቢሉ ኖሮ ቢጽ ሐሳውያን/ሐሰተኛ ወንድሞች እንላቸው ነበር ። ክርስቶስ ግን ሐዋርያት ስላላቸው ሐዋርያ ተብለው ይኖራሉ ። ሐዋርያ ማለት ጥሬ ትርጉሙ ሒያጅ ፣ ገስጋጅ ማለት ነው ። የክርስቶስን ስምና መልእክት ተሸክሞ የሚፈጥን ማለት ነው ። መልእክቱን የሚያደርሰው ደግሞ ለሰው ነው ፤ ሰው ደግሞ ሞት የሚባል አባራሪ ያለበት ነው ። ከሞት ይልቅ ካልፈጠነ ሰውን ማትረፍ አይችልም ። ስለዚህ ይገሰግሳል ። ገስጋሽ ነውና ኑ ብሎ የሚጠራ ፣ ካልመጡ ብሎ የሚቀር አይደለም ። ዓለምን ድንበር ፣ ጽንፍን ዳርቻው አድርጎ ይገሰግሳል ። ሐዋርያነት ወንበር ላይ የሚገላበጡበት ሹመት አይደለም ። የበላይ ሁነው ሁሉን ታች የሚያዩበት አለቃነትም አይደለም ። በገጠር በከተማው ፣ በቆላ በደጋው ሰውን ለማትረፍ መገስገስ ነው ። ሐዋርያ ሲያልፍ ፣ ሲገሰግስ ይታያል እንጂ ቆሞ ሲሳደብ ፣ የሰው ስም ሲያነሣ ፣ ድንጋይ ሲወረውር አይታይም ። ጊዜ የለውም ። ሰውን ከዘላለም ሞት ለማዳን ይሮጣል ። ሕፃን ልጅ ከመደቡ ወርዶ በእሳቱ ቅላት ተማርኮ ወደ ፍሙ ሊገባ ሲል ወላጅ በታላቅ ፍጥነት እንደሚገሰግስ ፤ በዓለም አታላይነት ተይዘው የጠፉትን ፣ ይግባኝ ወደማይጠየቅበት ፍርድ እየወረዱ ያሉትን መታደግ ሐዋርያነት ነው ። እነዚህ ሰዎች ጥንትም ነበሩ ፣ ዛሬም አሉ ። እስከ ዓለም ፍጻም እንደ ቃሉ ይኖራሉ ። ሐዋርያት መካን አይደሉምና ። ማቴ. 28፡20 ።

ሐዋርያት ቋሚ አድራሻ አልነበራቸውም ። እንደ ሰው አነጋገር ብንናገር ኑሮአቸውም ሞታቸውም ያማረ አይደለም ። “አሟሟቴን አሳምርልኝ” እንደሚባለው ፣ ያማረ አሟሟት በዘመድ ተከቦ መሞት ሳይሆን ለእውነት ዘመድ አጥቶ መሞት ነው ። ሐዋርያት ግን አኗኗራቸውን በቆራጥነት አሳመሩት ፣ አሟሟታቸውን ደግሞ ገዳዮቻቸው አሳመሩት ። እነርሱ ባይገድሏቸው ሰማዕት አይባሉምና ። ጠላቶቻችን ማዕረግ ይጨምሩልናል ። ሐዋርያት ለክርስቶስ ስለ ኖሩ ሞትን እንደ ሙሽርነት ቀን ናፈቁት ። በትክክል የኖረ ሞቱ አያስፈራውም ። ሲኖሩ ከዕቁብ መገለልን ፣ ሲሞቱ ዕድር ማጣትን አላሰቡም ። ስለ ክርስቶስ እንደ ጨው ዘር ተበተኑ ። መልእክታቸውም ቃል ሳይሆን ሕይወታቸው ሆነ ። እግዚአብሔር ይወዳችኋል ከማለት በክርስቶስ ፍቅር ሰዎችን ወደዱ ። የጨው ዘር ናቸውና ከቤተ መንግሥት እስከ ደሀዋ ቤት ተገኙ ። በዚህም የብዙዎችን ሕይወት አጣፈጡ ። አዎ ቅዱስ ጳውሎስ የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ ነበረ ። እኛስ የማን ሐዋርያ ነን ?

ኤፌሶን ትርጓሜ/2

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ጥር 19 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም