መግቢያ » ስብከት » የእግዚአብሔር ባሪያ » የእግዚአብሔር ባሪያ

የትምህርቱ ርዕስ | የእግዚአብሔር ባሪያ

ወቅቱ ያልወለደች ማኅፀን ፣ ያላጠባች ጡት የተባረከች ናት የሚባልበት ፣ ወላድ በመውለዷ የተጸጸተችበት ዘመን ነበር ። ልጅን እንደ ወለዱት በክፉ ቀንም መልሰው ቢውጡት ጥሩ ነበር ። አንቺን አልፈልግም ብሎ ልጇን ለሞት የሚፈልግ ፣ እኔ ልለወጥ ብትል የእናትን ቤዛ መሆን የማይቀበል ቀን ከባድ ነው ። ቀን ሲከፋ ያሳደጉትም ውሻ ይነክሳል ። ያበሉት ጠላት ፣ ያኖሩት ገዳይ ይሆናል ። ማኅፀን የዘጠኝ ወር ቤት እንጂ  የሰባና የሰማንያ ዓመት መኖሪያ አይደለም ። እናት ምነው ባልወለድሁ የምትልበት ፣ ልጅም ምነው ባልተወለድሁ ብሎ የተወለደበትን ቀን የሚረግምበት ዘመን አለ ። ሲወለድ ያዩት የትላንቱ ሕፃን ሲሞት ማየት ከባድ ነው ። ኋላ የመጣው ማሙሽ ቀድሞ ሲሄድ ልብን የሚሰብር ነው ። ሰው የጨከነበት ፣ ወልዶ የበላበት ፣ አሳድጎ የቀጠፈበት ዘመን ነበር ። ከሽፍታ መንግሥት ያስጥላል ፣ መንግሥት ሽፍታ ሲሆን ግን ማን ያስጥላል  የምድር ነገሥታት በቅዱስ መጽሐፍ ላይ በአውሬ ተመስለዋል ። ለሥልጣን ልጃቸውን የሠዉ ፣ ሕዝብ የጨረሱ ፣ እናታቸውን የገደሉ ናቸውና ። ንጉሥ ተብሎ በግ የተባለ ክርስቶስ ብቻ ነው ። የገደለን ሳይሆን የሞተልን ነውና ። ወዳጅ ሲጠቁም ገዳይ የሚታዘብበት ፣ ጎረቤት ሲተኩስ ጥይት ራርቶ የሚስትበት ዘመን ነበር ፤ ያ ዘመን ።

በችሎት የቆመው አንድ ደግ አባወራ ዳኛው፡- “ወዳጅህን ይዘህ ና” ቢለው ውሻውን ይዞ መጣ ። “ጠላትህን ይዘህ ና” ሲለው ሚስቱን ይዞ መጣ ። ሚስቱ በሰላም ቀን ያወሩትን በክፉ ቀን አደባባይ ዘርታዋለችና ። ያ ዘመን እንኳን ባልንጀራ ልብ የማይታመንበት ዘመን ነበር ። እንደ ገለባ የሚያቀልል ዘመን አለ ።

ወዳጅና ጠላት ፣ ዘመድና ባላጋራ ፣ ሟችና ገዳይ የሚቀላቀሉበት ዘመን አለ ። ጦርነቶች ሁሉ ለሰልፍ የደረሰውን ጎበዝ ለመቍረጥ ይቀሰቀሳሉ ። ይህኛው ጦርነት ግን የሚወለዱትን ሕፃናት የሚቀጭ ነበር ። ሕፃናት ዘጠኝ ወር ካምስት ቀን ተረግዘው አንድ ሰዓት በዚህች ዓለም ላይ እንዲኖሩ አይፈቀድላቸውም ነበር ። ቀጣይ ጉዞ ያለው መንገደኛ በአየር ማረፊያው አንድ ቀን ያድራል ፣ ወይም አንድ ሰዓት ቆይቶ ይበርራል ። ከማኅፀን ዓለም በቀጥታ ወደ ሰማያዊ ዓለም መሄዳቸው እነዚያ ሕፃናት ያሳዝናሉ  ። ማርና ወተትን ሳይለዩ ፣ የተዘጋጀውን የጡቱን እፍታ ሳይቀምሱ ፣ የሚፈውሰውን እንገር ሳይጠጡ ይታነቁ ነበር ። ለሚሞት ሰው መድኃኒት ምኑ ነው  እናትም ምጡን እንጂ ልጁን ማየት አልታደለችም ነበር  ። ልጁን እያሰቡ ማማጥ ደስታ ነበረ ። ሞትን እያሰቡ ማማጥ ከሌሊት በኋላ የመጣ ሌሊት ያሰኛል ። ከእግዜር የመጣ ቍጣ ሳይሆን ሰው ለሰው የደገሰው ክፉ መርዝ ነበር ። ያ ዘመን ወንድ ልጅን የጠላ ዘመን ነበር ። የወንድን ቍጥር ለመቀነስ የተነሣ ዘመን ነበር ። በሰልፍ ሳይሆን በልደት ብዙ ወንዶች ይሞቱ ነበር ።

የወንድ ልጅ እናት ታጠቂ በገመድ ፣
ልጅሽን አሞራ እንጂ አይቀብረውም ዘመድ ፤

ቢባል ወግ ነበረ ። እነዚያ ሕፃናት አንድ ቀን ሳይኖሩ እስከ ወዲያኛው ይሞታሉ ። ኖሩ ሳይባል ሞቱ መባል ከባድ ነው ። አንድ ቀን ንጹሕ አየር ሳይተነፍሱ በተውሶ ተንፍሰው መሞታቸው ያሳዝናል ። አዋላጆች ገዳዮች የሆኑበት ጊዜ ፣ ነገሥታት ከእርጥብ ጨቅላዎች ጋር የተጣሉበት ዘመን ነበር ። ነገሥታት ጠብ ካልናቁ ከጽንስም ይጣላሉ ። ወዳጅነታቸው ወረት ያለበት ነውና ጥንቃቄ ይፈልጋል ። ፍቅራቸው ያሳብዳል ፣ ጠባቸው ይቀብራል ። ተጣላኝ ብቻ ሳይሆን የተወለደው የዛሬ ሃያ ዓመት አድጎ ሊጣላኝ ይችላል ብለው ያንቃሉ ። ለአዋላጅነት የተማሩት የገዳይነት ሥልጠና ሳይወስዱ ገዳይ ሆኑ ። ከትምህርት ባሻገር መቆም ፣ የባከነ እውቀት ነው ። ማዳን እንጂ መግደል ሙያ አይጠይቅም ። ሕፃናት በማኅፀን በራፍ ላይ ሞት እንደሚጠብቃቸው ቢያውቁ ኑሮ አልወለድም ብለው ይጮኹ ነበር ።

እንኳን ሕፃናቱ አራዊትና ከብቱ ፣ ሣሩና ቅጠሉ የእነርሱ ሳለ መኳንንትና ነገሥታት ሕፃናትን ለማነቅ ተነሡ ። ሳይኖሩ መሞት ፣ የአንድ ቀንን ፀሐይ ሳይሞቁ ማለፍ በእውነት ልብ ይነካል ። ልጁ ለራሱ ለማዘን ፣ ገዳይን ለመማጸን እውቀትም አቅምም የለውም ። ማርና ወተትን ፣ ሞትና ሕይወትን ሳይለይ ይሞታል ። የወለደች እናት ፣ ያማጠች ሴት ግን ታዝናለች ።

ልጇን ቀለመ ወርቅን ቅኔ ቢማር ብላ ዋሸራ የሰደደች የጎጃም እናት በትምህርት ቤቱ እሳት ተነሥቶ ልጇ እንደ ሞተና አመድ እንደሆነ ሰማች ። ኀዘን የቅኔ መገኛ ነውና እንዲህ ብላ በአለቀሰች፡-

ይማርልኝ ብዬ ዋሸራ ሰድጄ ፣
ቀለም ገባው አሉ እሳት ሆነ ልጄ ።

በአገራችን ዐፄ እንደ ማለት የግብጽ ነገሥታት የሚጠሩበት የክብር ስም ፣ ስመ መንግሥት “ፈርዖን” የሚል ነበረ ። ፈርዖኖች በጭካኔ የታወቁ ናቸው ። ታላቁ ቤተ መንግሥታቸውን በዓባይ ዳር የመሠረቱ ፣ የዝናብ ጥገኛ ስላልሆኑ ዓለም ሲራብ የሚተርፉ ናቸው ። ዓባይና ሊቃውንት ሲያልፉ ዝም ብላ የምታይ ፣ ካለፉ በኋላ የምትዘፍን ኢትዮጵያን ጥሎላቸው በሰላም ይኖራሉ ። ቋንቋቸው ቅብጥ የሚባል የቀበጦች ቋንቋ ነው ። እስልምና መካከለኛውን ምሥራቅ አልፎ ወደ ግብጽ ሲመጣ ቋንቋዋን ከቅብጥ ወደ ዐረብኛ ለወጠባት ። የነገሥታቱም ስም ከፈርዖን ወደ ከሊፋ ተለወጠ ። በታላቁ እስክንድር ስም የተሰየመችው እስክንድሪያም ዋና ከተማነቷ አብቅቶ በአሥረኛው ክፍለ ዘመን ካይሮ ዋና ከተማ ሆነች ። ግብጽ አፈርና ውኃን ከኢትዮጵያ ምድር የምታገኝ ብትሆንም ፣ በአፈሩ ዘርታ ፣ በውኃው አብቅላ አንድ ቀን እንኳ ኢትዮጵያን እሸት ቅመሺ ብላ አታውቅም ። በኢትዮጵያ የረሀብ ዘመን እንኳ ከማላገጥ በቀር አንድ ኩንታል እህል አልረዳችም ። እንደ ስምዋ ቅብጥ ፣ ቀበጥ ናትና አድርጉልኝ ብቻ የምትል ፣ ተቀብላ የማታመሰግን ፣ እኔን ብቻ ይድላኝ የምትል ናት ። የኮፕት ቤተ ክርስቲያን ጳጳሳትም ኢትዮጵያውያን ከገዛ መምህራኖቻቸው ጳጳሳት መሾም አይችሉም ብለው ለ1600 ዓመታት ያህል በመንፈሳዊ ባርነት ሥር አውለውናል ። ጳጳሳቱም በአብዛኛው የዓባይ የበላይ ጠባቂ እንጂ የሕዝቡ መንፈሳዊ እረኛ አልነበሩም ። በግብጽ ያሉ ክርስቲያኖች በከሊፋዎች እንዳይጠቁ በኢትዮጵያ ያሉ እስላሞችን የሚንከባከቡ ነበሩ ። ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንንም እያወገዙ ፣ መሃይሙንና ወረኛውን ምሥጢር መጋቢ እያሉ የሚጠሩ ነበሩ ። ይህም መንፈሳዊ ባርነት የተሰበረው አቡነ ባስልዮስ የመጀመሪያው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ በሆኑ በ1951 ዓ. ም. ነው ።

ከአባ ፍሬምናጦስ ጀምሮ 111 የግብጽ ጳጳሳት የኢትዮጵያን ቤተ ክርስቲያንን አስተዳድረዋል ። ጳጳሳቱም ይመጡ የነበረው በወርቅ እጅ መንሻ ነበረ ። አፈሩና ውኃው ሳያንስ ወርቁ ይጋዝ ነበር ። ወርቁም ካይሮ ሲደርስ እኩል ለቀዳሽ ፣ እኩል ለነጋሽ ብለው የኮፕት ቤተ ክርስቲያን መሪዎች ከከሊፋዎች ጋር ይካፈሉት ነበር ። ኢትዮጵያ ለተወለደባት ኮሶ ፣ ለባዕድ እንጀራ የምታቀርብ ፤ የባዕድ እናት ፣ የልጆችዋ እንጀራ እናት ናትና የራሷን ሊቅ እያወገዘች መሃይም የሆኑትን የደጅ ሰዎች ስታከብር የምትኖር ናት ። ይህ እዩኝና ውደዱኝ ማለት ዛሬም ስላልለቀቃት ፣  ኢትዮጵያ የአፈ ቀላጤዎችና የባዕዳን እንጀራ ናት ።

ይቀጥላል

የእግዚአብሔር ባሪያ/1

ሰኔ 1 ቀን 2012 ዓ.ም.

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም