መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » የክርስቶስ ልደት !!!

የትምህርቱ ርዕስ | የክርስቶስ ልደት !!!

በዚህ ዓለም ላይ በመወለዱ የዓለም ደስታ የሆነ ሕፃን ከክርስቶስ በቀር ማንም የለም ። አምላክ በትሕትና ዝቅ ያለበት ፣ ሰው በታላቅ ክብር ከፍ ያለበት ልደት ነው ። በልደቱ ሰማይና ምድር ፣ ሰውና መላእክት ፣ ሕዝብና አሕዛብ ታርቀዋል ። አስታራቂ ልደት ከክርስቶስ በቀር የትም አይገኝም ። ተዋሕዶውም ድልድይ ሁኖ የተራራቁትን አገናኝቷል ። የተወለደው ሕፃን ብቻ ሳይሆን ፍቅር ፣ ሰላም ፣ ኅብረት ተወልዷል ። ሰው መሆን ለአምላክ ውርደት ነው ፣ አምላክ መሆን ግን ለሰው ክብረት ነው ። “ክርስቶስ ዛሬ ተወለደ” እየተባለ ሲዘመር ልደቱ ታሪክ ሳይሆን ሕያው እንደሆነ እየመሰከርን ነው ። እኛ የእግዚአብሔር ልጆች እንድንባል እርሱ የሰው ልጅ ተባለ ። ዳግም ሊወልደን ሁለተኛ ልደትን ከድንግል ገንዘብ አደረገ ። በምድር አባት የለኝም ለሚሉት መጽናናት እንዲሆን እርሱ ያለ አባት ተወለደ ። በምድር ላይ በአባት የተከዱ እንጂ ያለ አባት የተወለዱ የሉም ። ክርስቶስ ግን ያለ አባት ከድንግል ብቻ ተወለደ !

በዚህም ችሎታውን ፣ ደግሞም የሔዋንን ክብር መለሰ ፣ ሐፍረት ገሠጸ ። በሰማይ እናት የሌለው ክርስቶስ በቤተ ልሔም ያለ አባት ተወለደ ። በሰማይ እናታችን እርሱ ነውና የእናት እንክብካቤ አያስፈልገንም ። በምድር ላይም የእናት እንክብካቤ እስከ አካለ መጠን ድረስ ነው ። የዘላለም እናት ግን በሰማይ ያለው ፣ በዘላለማዊ ልደቱ ያለ እናት የተወለደው ነው ። እኛ ከውኃና ከመንፈስ እንወለድ ዘንድ ክርስቶስ በግብረ መንፈስ ቅዱስ ተወለደ ። የልደቱን ምሥጢር ሰው ቢረዳውና ቢያስተውለው ይገርም ነበር ። የልደቱ ምሥጢር ግን ከአእምሮ በላይ ነውና ዝማሬ ያሻዋል ። እኛን ወደ ራሱ ያቀርበን ዘንድ ፣ እርሱ የእኛ ዘመድ ሆነ ። ሊለየን ስላልፈለገ ተዋሕዶውን ዘላለማዊ አደረገ ።

በዕፀ በለስ ፣ በስርቆት ያላገኘነውን አምላክነት በተዋሕዶ አገኘነው ። ከንጉሥ ምነው ብዛመድ ፣ ንጉሥ ከወጣበት ጎሣ ምነው ብወለድ ብለን እንዳንቀና አምላክ ዘመድ ሆነን ። ባሕርያችንን ተዋሕዶ አከበረው ። በሦስትነቱ ላይ አራትነት ሳይጨመርበት በመንበረ ሥላሴ የእኛ ሥጋ ተቀመጠ ። አዳምን ከአፈርነት በመንፈስ ቅዱስ እፍታ ያነሣ ፣ አፈር ሥጋችንን በመንፈሱ ተዋሐደ ። መንፈስ ቅዱስም የሥጋዌው አበጋዝ ሆነ ። አብ ለልጁ ማደሪያ የወደዳት ድንግል እንደምን ታደለች ! በእርስዋ መክበር የእኛን ክብር አየን ። ጸጋ የበዛላቸውን አገልጋዮች እንወዳለን ፣ ባለጸጋውን ክርስቶስን የወለደችውን ድንግል እጅግ እንወዳታለን ። እርስዋ ምድራዊት ኪሩብ ናት ። ኪሩቤል ሊያዩት የማይቻላቸውን በቡሩካት ዓይኖችዋ አየችው ። የዓለምን መጋቢ በድንግልናዊ ጡቶችዋ አሳደገችው ። ክርስቶስ በቤተ ልሔም ሲወለድ እኛ ከሰማይ ተወለድን ። የክርስቶስ በሥጋ መወለድ የእኛ መንፈሳዊ ልደት ነው ። በቤተ ልሔም ለሆነችው የተባረከች ልደቱ ምስጋና ይገባል !

“ዛሬ” የማይሰኝ ፣ ዘመኑ የማይቆጠር ፣ ዘላለማዊ ልደትን ከአብ የተወለደው ፤ በታወቀ ቀንና ሰዓት ከድንግል ተወለደ ። እርሱ ሁሉ በሁሉ ነው ። ዘመን የማይቆጠርለት ፣ ዘመን የሚቆጠርለትም ሆነ ። በሚቆጠር ዘመን በሥጋ እንወለዳለን ፣ ዘላለማዊ ልደትን በመንፈስ እንወለዳለን ። ለችሎታው መመርመር የሌለበት ከድንግል ተወለደ ። በዕለተ ሠሉስ ዘርን ያለ ዘር ያበቀለ ፣ ያለ ወንድ ፈቃድ ተወለደ ። ያለ ወገን ፣ ያለ ብቃታችን ሊረዳን እንደሚችል በዚህ ተገለጠ ። ከእኔ ከድሀው ለተባረከች ልደትህ ምስጋና ይገባል ። አዳም ከድንግል መሬት ያለ ወንድ ዘር ተፈጠረ ፣ ክርስቶስም ዳግማዊ አዳም ይባል ዘንድ ከድንግል ማርያም እንበለ ዘርዐ ብእሲ ተወለደ። ኦ አንክሮ ፣ መደነቅ ፣ በተመሥጦ መጥፋት ይገባል !

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ታኅሣሥ 23 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም