የትምህርቱ ርዕስ | የክብር አባት

“ስለዚህ እኔ ደግሞ በእናንተ ዘንድ ስለሚሆን በጌታ በኢየሱስ ስለ ማመንና ለቅዱሳን ሁሉ ስለሚሆን መውደድ ሰምቼ ፥ ስለ እናንተ እያመሰገንሁ ስጸልይ ስለ እናንተ ማሳሰብን አልተውም ፤ የክብር አባት የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክ እርሱን በማወቅ የጥበብንና የመገለጥን መንፈስ እንዲሰጣችሁ እለምናለሁ ።” ኤፌ. 1፡15-17 ።

ሐዋርያው ስለ ኤፌሶን ክርስቲያኖች በርቀት ይሰማው የነበረው እግዚአብሔርን ስለ ማመንና ወንድሞችን ስለ መውደድ ነው ። የኤፌሶን ክርስቲያኖች እንዲህ ነበሩ ። ይህም ሕይወታቸውን የተሟላ ያደርገዋል ። ኦሪትም ሐዲስም ፍቅረ እግዚአብሔርና ፍቅረ ቢጽን የሚሰብኩ ናቸው ። እግዚአብሔርን የወደደ ወንድሙን ሳይወድ አይቀርም ፣ ወንድሙን የሚወድም እግዚአብሔርን ለመውደዱ ምስክር ነው ። ከወንድም ፍቅር ግን የእግዚአብሔር ፍቅር ይቀድማልና ሰው አስቀድሞ እግዚአብሔርን መውደድ ይገባዋል ። እግዚአብሔርን አምኖ ወንድሙን መውደድ የቸገረው ፣ ወንድሙን ወድዶ እግዚአብሔርን ማመን የተሳነው ካለ ኑሮው ከባድ ነው ። እግዚአብሔርን እወዳለሁ ብሎ ወንድሙን የሚጠላ የዓይን ቅርጽ ያለው ነገር ግን የማያይ ነው ። ወንድሙን ወድዶ እግዚአብሔርን አላምንም የሚል መሠረት የሌለው ረጅም ካብ የሚክብ ነው ። እምነት ያፋቅራል ፣ ፍቅርም ያምናል ። በሚወድድ እምነት ፣ በሚያምን ፍቅር መኖር ጸጋ ነው ።

ሰዎችን በግላዊ ጥንካሬአቸው ፣ በሰዎች ዘንድ ባላቸው ተጽእኖ ፈጣሪነት ፣ አያስነኩኝም ተብለው በታመኑት ልክ ፣ ኃይላቸው የሚጥል በመሆኑ ፣ ጊዜ ያከበራቸው የቀን ጎበዞች በመሆናቸው ፣ በግል ጽድቃቸው ፣ በአገልግሎት ትጋታቸው ሊታመኑ ይችላሉ ። የሚያስመሰግንና የማያሳፍር እምነት ግን በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ማመን ነው ።

ክርስቲያኖች እርስ በርስ መዋደዳቸው ምስክርነት ነው ። ክርስቲያኖች ክርስቲያን በመሆናቸው ብቻ ከማኅበረሰቡና ከምድራዊ ጥቅም መገለል ፣ መነጠልና መሰደድ ይገጥማቸዋል ። የቀስት መለማመጃ ሁነው ፣ ስድብ ለማጅ እንኳ ስሜት እንዳላቸው ረስቶ በእነርሱ ላይ ያሟሻል ። የክርስቲያኖች ሕይወት የተኩስ ወረዳ ነው ። በክርስቲያኖች ላይ ዱዳ የሚናገርበት ፣ ፈሪው ደፋር ሁኖ ካላጠፋኋችሁ የሚልበት ነው ። መስቀል በክርስትና ምርጫ ሳይሆን ግዴታ ነው ። የሥጋ ዘመዶቻቸው ሳይቀር አሳልፈው ሲሰጡአቸው ትልቅ ትምክሕት ይሰማቸዋል ። የክርስቲያኖችን አንገት መቅላት ለሃይማኖታቸው ቸብቸቦ እንደ ማቅረብ የሚቆጥሩት አያሌ ናቸው ። አንዳንዶችም ወደ አምላካቸው መንግሥት የሚገቡት በክርስቲያኖች እልቂት መሆኑን ያምናሉ ። የፈጠረውን ግደሉልኝ የሚል ፈጣሪ መኖሩ ግራ ያጋባል ። በዚህ ሁሉ ምክንያት ይህን መራራ ዓለም ለማሸነፍ ክርስቲያኖች እርስ በርስ መዋደድ አለባቸው ።

በዓለም ላይ እኛ ትንሾች ነን ፣ የተጠላን ነን ። ሁሉ ሊያጠፋን ይፈልጋል ብለው የሚያስቡ ወገኖች ይፋቀራሉ ። የክርስቲያኖች ፍቅር ግን የመጥፋት ስሜት የወለደው ሳይሆን በክርስቶስ የመዳን ፍሬ ነው ። በፍቅር የተገለጠ ፣ ራሱንም ፍቅር ብሎ የጠራ እግዚአብሔር ብቻ ነው ። የባዕድ አምልኮ ጉዳይ አስፈጻሚዎች ድምፃቸው ጎርናና ፣ ቃላቸው ጭንቁር ነው ። የሚመለኩበትም ስልት ማስፈራራት ብቻ ነው ። እግዚአብሔር ግን ተወድዶ የሚመለክ አምላክ ነው ። ሐዋርያው በርቀት ሁኖ የሰማው የኤፌሶን ክርስቲያኖችን እምነትና ፍቅር ነው ። እምነት ለማይታየው እግዚአብሔር የሚቀርብ መባ ነው ፣ ፍቅር ለሚታየው ባልንጀራ የሚቀርብ እንጀራ ነው ። ክርስቶስን በማመን መጽናት ፣ ወንድሞችን በመውደድ መታወቅ ትልቅ ዕድል ነው ። እግዚአብሔር በህልውናው እንደማይጠረጠር አማንያንም ሌላውን በማፍቀር መጠርጠር የለባቸውም ።

ዛሬ በርቀት ያሉ መንገድ የመሩን አስተማሪዎቻችን ፣ ስለ እኛ ሕይወት የተጨነቁ የሃይማኖት አባቶቻችን ምን እየሰሙብን ይሆን  ብለን ራሳችንን መጠየቅ አለብን ። የዘረኝነት ቀስቃሽ ሁነን ሲያዩን ምን ብለውን ይሆን  ሌላውን እየማገድን ለመኖር ስንጨክን ደጉን ክርስቶስ አልተማሩም ነበር ወይ  ብለው ተጠራጥረውን ይሆን  በሌብነት ዓይን ስናወጣ ድሀ ሁነን የወደደንን አምላክ በመካዳችን አዝነው ይሆን  የኤፌሶን ክርስቲያኖች የሚሰማ ቃል ሳይሆን የሚሰማ ሕይወት ነበራቸው ። እርሱም እምነትና ፍቅር ነው ።

የማይታየው እምነት በሚታየው ወንድምን መውደድ ይገለጣል ። ሰውን መውደድ እግዚአብሔር በሰው ላይ ያለው ዓላማ ማፍቀር ነው ። የክርስቶስ ስም እንዳይሰደብ ክርስቲያን ሀነው በችግር ውስጥ እያለፉ ያሉትን ዛሬ መጎብኘት ያስፈልገናል ። ይህ በቀራንዮ የተሰቀለውን የክርስቶስን ዕርቃን መሸፈን ነው ።

ሐዋርያው በሰማው ነገር ተደስቶ ሦስት ነገሮችን አደረገ ። ማመስገን ፣ መጸለይ ፣ ማሳሰብ ። ማመስገን ስላለፈው ኑሮአቸው ፣ መጸለይ ስለ ዛሬው ሕይወታቸው ፣ ማሳሰብ ያለማቋረጥ ጸጋን መመኘት ነው ። በመልካም መንገድ ላይ ስላሉ ሰዎች እግዚአብሔርን ማመስገን እንጀምር ። ያን ጊዜ ደስታ በልባችን ይሞላል ። ሰዎቹም ጸጋ ይበዛላቸዋል ። ሕይወታቸው ርእስ ሁኖ እግዚአብሔር ተመስግኖበታልና ። ደግሞም እንዲጸኑ መጸለይ ይገባል ። ታይቶ ጠፊ ፣ ጀምሮ ቀሪ ፣ ወጥቶ ዱር አዳሪ እንዳይሆኑ መጸለይ ግድ ይላል ። ተጠርተው ያልተመረጡ ፣ ራሳቸውን ከሕይወት መዝገብ የሰረዙ አሉና ። ማሳሰብም ወሳኝ ነው ። ቤተ ክርስቲያን ስላሉት ብቻ ሳይሆን ስለ ሞቱትም ማሳሰብን አትተውም ። ይህን ስፋትና እምነት መያዝ መታደል ነው ።

የክብር አባት የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክ እርሱን በማወቅ የጥበብንና የመገለጥን መንፈስ እንዲሰጣችሁ እለምናለሁ” ይላል ። ሥላሴን ያነሣል ። የክብር አባት ብሎ አብን ፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብሎ ወልድን ፣ የጥበብና የመገለጥ መንፈስ ብሎ መንፈስ ቅዱስን ያነሣል ። ደግሞም ምሥጢረ ሥጋዌን ያትታል ። የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክ ይላልና ። ጌታችን ለለበሰው ሥጋ አብም እርሱም ፈጣሪ ናቸውና ። ለለበሰው ሥጋ አብ አምላኩ ነው ። ያንን ሥጋ በመቃብር ጥሎት እንዳልሄደ ፣ ያ ሥጋ ባለ መለወጥ ፣ ባለ መጥፋትና ባለ መለየት አሁን በየማነ አብ እንዳለ እያስረዳን ነው ። መንፈስ ቅዱስ የመገለጥና የጥበብ መንፈስ ነው ። መገለጥ የዋሆችን ብልህ የሚያደርግ የመለኮት መብራት ነው ። ጥበብም ክርስቶስን ምርጫ ማድረግ ነው ። የክብር አባት ይላል ። ክብር ሰጪ ሳይሆን ራሱ ክብር ነውና ። ጌታችን ይለዋል ። ኢየሱስ ማለት ችግር የለውም ። እንደ ሐዋርያው ግን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ማለት ተገቢ ነው ። ኢየሱስ የሚሉት የታሪክ ተመራማሪዎች አሉ ። ነቢይ የሚያደርጉትም አይጠፉም ። እርሱን ጌታ ማለት ግን ከሁሉ በላይ ነው ፣ የክርስትናም መለያ ነው ። “እለምናለሁ” ይላል ። ተለማኝ አምላክ ነውና ። ስለ ሌሎች ስንለምነው የሚወድድ ፣ ለእኛም በእጥፍ የሚሰጥ ነው ።

አሜን።

የኤፌሶን መልእክት ትርጓሜ /25

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መጋቢት 22 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም