መግቢያ » ትረካ » የጌርጌሴኖን ታማሚ » የጌርጌሴኖን ታማሚ/2

የትምህርቱ ርዕስ | የጌርጌሴኖን ታማሚ/2

 ማር. 5፡1-20
የመጀመሪያው በመቃብር ይኖር ነበር ። እያለ የሌለ ፣ እየኖረ ያልኖረ ፣ በቁም የሞተ ፣ የሚንቀሳቀስ ሬሳ ፣ ዕድር ያልተበላበት ሙት ፣ ዕቁብ የማይገባ መናጢ ፣ የማያጭ የማይታጭ ፣ የማይመርጥ የማይመረጥ ፣ ሕዝብ ሲቆጠር የማይቆጠር ፣ ጎረቤት የሌለው በረኸኛ ፣ ዱር ቤቱ የሆነ አመለኛ ፣ ባልተመለሰ የሚባል ፣ ከአራዊት ይልቅ የሚፈራ ፣ እሳት የማያስጭሩ የመቃብር ጎረቤቶች ያሉት ፣ ሲጮህ ቢውል የማይመልሱ ጓዶችን ያፈራ ፣ ከሰፈር የራቀ ፣ ከሕያዋን ማኅበር በግድ የተገለለ ፣ አለሁ የማይል ፣ አለ የማይሉት ፣ ስጡኝ የማይል ፣ ይሰጣል ተብሎ ተስፋ የማይደረግ ፣ የቤት ቊጥር የሌለው ፣ መቃብር አልጋው ፣ ሙታን ትራስ የሆኑለት የጨለማ ነዋሪ ነበር ። ክብር ይግባውና ጌታችን ፣ ሊያገኘው ባሕር አቋርጦ የመጣው ይህን ሰው ነበር ።

ዓለሙ ተስፋ የቆረጠባቸው እነርሱም በዓለሙ ተስፋ የቆረጡ ፣ እንደገና አብባለሁ ብለው የማያስቡ ፣ በቁም የደረቁ ፣ በቁም ያረሩ ብዙ ጎበዞች ዛሬም አሉ ። ሳይነጋ በሱስ የሚቃጠሉ ፣ ከጨዋ ሰው ርቀው መሰላቸው ጋር በደቦ የሚሞቱ ፣ ጠባ ለመጠጥ ፣ መሸ ለሱስ የሚንከለከሉ የመቃብር ነዋሪዎች ዛሬም አሉ ። በሰው የተገለሉ ፣ ብዙ የሆነው ማኅበረሰብ ጥቂትነታቸውን በፍቅር ያላሸነፈው ፣ ለራሳቸው የተተዉ ፣ ይመጣሉ ተብለው የማይጠበቁ ፣ በጎዳና የወደቁ ፣ ክረምት ብርድ ልብሳቸው ፣ ፀሐይ አንሶላቸው የሆኑ ፣ ከእንስሳ አንሰው ከመንደር የወጡ ፣ ትራፊም ለመለመን ነጻነት የሌላቸው ፣ እንደ ሰው ጀምረው እንደ ሰው መኖር ያቃታቸው ፣ ኑሮአቸው ሞት ስለሆነ ሞታቸው ኑሮ እንዲሆን የሚናፍቁ ብዙ ቀበዝባዞች አሉ ። እነዚህን የሚፈልግ ሰባኪ የለም ። በባለጠጋ የሚጣላ አገልጋይ እንጂ እነዚህን ሰው ለማድረግ የሚተጋ የእግዜር ሎሌ እየጠፋ ነው ። ጌታ ግን ሰውን ለማዳን የቤት ቊጥር አይፈልግም ። ያለ ቀብድ የሚወድና የሚያገለግል እርሱ ብቻ ነው ።
ሁለተኛ፡- ይህ ሰው በእጅ ሰንሰለት ፣ በእግረ ሙቅ የታሰረ ሰው ነበር ። ይህ ሰው የመቃብር ነዋሪ ብቻ ሳይሆን በታላቅ ብረት የተዘጋበት ሰው ነበር ። ሰንሰለቱንና ብረቱን ይበጣጥሰው ነበር ። ከቤተሰቡም ፣ ከመንደሩም ያራቀው ይህ ኃይለኝነቱ ነበር ። ከቤተሰብ በላይ ሲሆን መንግሥት ይይዛል ። ፍጹም አቅሉን የሳተውን ግን መቃብር ይቀበለዋል እንጂ ማንም ሊይዘው አይችልም ። ጥፋተኛ ተብሎ መወቀስ ፣ በሕግም ተከሶ ወኅኒ መጣል ተስፋ ለሚደረግ ሰው ነው ። ይህ ሰው ግን ጥፋቱ ፣ ጥፋት ተብሎ አይቆጠርም ነበር ። አእምሮውን ካጣ ሰንብቷል ።
በኅሊና ያለ ሰው የማያደርጋቸውን ነገሮች በማድረግ የታሰሩ ብዙ ወገኖች አሉ ። አብደዋል ተብለው ስህተታቸው የጸደቀላቸው ፣ በፍቅርም በሕግም ሊመለሱ ያልቻሉ አያሌ ናቸው ። እየበዙ ሲመጡ ስህተታቸው የጸደቀላቸው ፣ ኃጢአታቸው የሕግ ከለላ ያገኘላቸው ብዙዎች ናቸው ። ይህን ሰንሰለት ሊበጥስ ፣ ከዚህ የእግር ብረት ሊያድን የሚችል እግዚአብሔር ብቻ ነው ። ጌታችን ወደዚህ ሰው መጣ ። ሰው ያቃተውን እኔ ያቅተኛል የማይለው ሊፈልገው መጣ ። ከሰው አቅም በላይ የሆነ ሁሉ ከእርሱ አቅም በታች ነው ። የደረቀውን ተስፋ በማለምለም የታወቀ ነው ።
ሦስተኛው፡- በመቃብርና በተራራ ይጮኽ ነበር ። የሚጮኸው ሌሊትና ቀን ነው ። በቁሙ ሲዖልን ተሸክሞ የሚዞር ሰው ነበር ። ውስጡ ካልጮኸበት የሚጮህ ሰው የለም ። ጩኸት ለጩኸት የሚሰጥ መልስ ነው ። ትልልቅ የድምፅ ማጉያ ሥር ተቀምጠው የማይሰማቸው ፣ በደማቅ ዘፈኖችና ዳንኪራዎች ውስጥ ሌሊትና ቀን የሚጮኹ አሉ ። ከራስ ለማምለጥ ፣ ትላንትን ለመርሳት የሚደረግ ጥረት ነው ። ጌታችን ይህን ሰው ለመፈለግ መጣ ። ዛሬም በዚህ ውስጥ የሚያልፉትን እርሱ ይፈልጋቸዋል ። ደም በደም አይጠራም ፤ በደልም በበደል አይነጻም ።
አራተኛው፡- ሰውነቱን በድንጋይ ይቧጭር ነበር ። ሰውነቱን ራሱ እያፈረሰው ፣ የደሙን ጋን ራሱ እየሸነቆረው ነበር ። ራሱን ለማጥፋት በብርቱ ይታገል ነበር ። ለዚህች ቀን ስላሰበው ግን በሕይወት ቆየ ። ጌታ ይህን ምስኪን ፍለጋ መጣ ። ከኑሮ ይልቅ ሞት ቅርቤ ነው የሚሉ ፣ ሞቼ በተገላገልሁ የሚሉ አያሌ ናቸው ። ሞተው እንደሚያርፉት ግን ምን ያህል እርግጠኛ ናቸው ? ሞቶ የሚያርፈው አሳራፊውን አምላክ ያገኘ ብቻ ነው ። የኃጥአን ሞታቸው ኀሣር ፣ የጻድቃን ሞታቸው ሕይወት ነው ።
ያ ሰው የማያስቀርብ ሰው ፣ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን በሩቅ ሲያየው ሰገደለት ። አጋንንቱ እንዳትሣቅየኝ እለምንሃለሁ አለ ። ያደረበት ሌጌዎን የሚባል ጭፍራ ነበር ። ሌጌዎን ጭፍራ ማለት ነው ። አንድ ጭፍራ በሮማ ወታደር አደረጃጀት እስከ ስድስት ሺህ ሠራዊት ይይዛል ። ይህ ሰው የተሸከመው ጉድ ብዙ ነበር ። ያስጨነቀው የሚጨነቅበት ጊዜ ደረሰ ። በተራራ ላይ ያሉ የእርያ መንጋ ነበሩና አጋንንቱ በዚያ ለመግባት ለመኑት ። አጋንንት በእርያ ላይ እንኳ ሥልጣን የለውም ። ጌታ ፈቀደላቸው ፣ እርያዎቹም እየተጣደፉ ወደ ባሕር ሰጠሙ ። ይህ በሽተኛ ከእንቅልፍ ሲነቃ እንዴት ካለ ነገር እንደ ዳነ አያውቅም ነበር ። ስለዚህ ጌታችን የመዳኑን ታላቅነት እንዲገነዘብ አፋፍ ላይ ያሉ እርያዎች ሲሰጥሙ እንዲያይ አደረገው ። ደግሞም ከንብረት የሰው ዋጋ እንዲበልጥ ለማስተማር ይህን አደረገ ። የከተማው ሕዝብ ግን በሰውዬው መዳን ከመደሰት በእርያዎች ባሕር መስጠም አዝነው ከከተማችን ውጣልን ብለው ለመኑት ። ግባልን እንጂ ውጣልን ተብሎ መለመኑ የሚደንቅ ነው ። በሰው ዘንድ ንብረት ከፍ ያለ ዋጋ አለው ። የሰው ዋጋ ከፍ ያለው በክርስቶስ ዘንድ ነው ።
ዛሬም ለጌርጌሴኖን ታማሚዎች መድኅን አለ ። ከሰው ርቄ ብቻዬን ነኝ ለሚሉ ፣ በሰንሰለት ተይዘው ለሚጨነቁ ፣ በጩኸት ውስጥ ለተደበቁ ፣ ራሳቸውን ለጠሉ እርሱ አለሁ ይላል ። በቁም የደረቁ ዛፎችን ያለመልማል ። ምስጋና ለአዳኝነቱ ይሁን !!!
ተፈጸመ
ሰኔ 14 ቀን 2011 ዓ.ም.
ዲአመ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም