ወዳጄ ሆይ !
ምክር መልካም የምትሆነው ለሚተገብራት ነው ። ምክርና ፍቅር ያለ ቦታቸው ርካሽ ናቸው ። በነጻ በምክር ካልተማርህ በበትር በዋጋ ትማራለህ ። መልካም ምክር ለጊዜው መራራ ፣ ቆይቶ ጣፋጭ ናት ። ክፉ ምክር ደግሞ ለጊዜው ጣፋጭ ፣ ቆይቶ ግን መራራ ናት ። የመልካም ምክር ምሬት ለጊዜው ፣ ጥፍጥናው ግን ለሕይወት ዘመን ነው ። የክፉ ምክር ጣፋጭነትም ለአሁን ፣ ምሬቱ ግን ለዘላለም ነው ። መላእክትን አጋንንት ፣ አዳምንም አሮጌ ሰው ያደረገው ክፉ ምክር ናት ። የሰውን ነጻ ፈቃድ የምታከብር ምክር ናት ፤ ካልተቀበልሃት ትሄዳለች ። መልካም ምክር መድኃኒት እንጂ ማር አይደለችምና አትጣፍጥም ። መድኃኒት እየመረረ ያድናል ፣ መልካም ምክርም ለጆሮ እያሳከከ ይፈውሳል ። ምክር አራት ነገሮች አሏት፡- እነርሱም መካሪ ፣ ተመካሪ ፣ ምክሩና ውጤቱ ናቸው ። የሁሉንም ሰው ምክር የምትሰማ ከሆነ ብቻህን ትቀራለህ ። መልካም ምክርን የናቀ የሞተው ዛሬ ነውና አልቅስለት ። የአንዳንድ ሰዎች ሞታቸው ይቀድምና ቀብራቸው ይዘገያል ። ቀና ምክር ንጹሕ ልብ ካለውና መንፈስ ቅዱስ ከሞላበት ሰው ይገኛል ። ምክር ሞልቶ መፍሰስ ነውና መካሪዎች የእውቀት ፣ የዕድሜ ፣ የልምድ ፣ የመንፈሳዊ ተጋድሎ ሙላት በውስጣቸው አለ ።
ወዳጄ ሆይ !
በትምህርት የምታውቀውን በኑሮ ስታውቀው ሌላ ነው ። ምክር የኑሮ ጭማቂ ናት ። አንደኛው ታምሞ ሌላው እንዳይታመም የሚጥርባት የደግነት መድረክ ናት ። አምጠው የሚመክሩ ጀማሪዎች ናቸውና ያስከፍላሉ ፣ ሰምተው የሚመክሩ ጎበዞች ናቸውና ይደነቃሉ ፣ ሞልተው የሚፈስሱ ግን ምክራቸውን ለተቀበለው ደመወዝ ይሰጣሉ ። መጥምቁ ዮሐንስ ጭው ባለ በረሃ ላይ የእግዚአብሔር ድምፅ እንደ ነበረ ፣ መካሪዎችም በዚህ ዓለሙና ሰዉ በረሃ በሆነበት ዘመን የመጽናናት ድምፅ ናቸው ።
ምክር ሁሉ ዋጋ ይከፍላል ። ለሰሙት ደስታን ሲከፍል ፣ ያልሰሙትን ፀፀት ይከፍላል ። ስላልሄድክበት መንገድ ከሄዱት ሰዎች ጋር አትከራከር ። ምክር አለመስማት የሚመጣው አፍ ተከፍቶ ጆሮ ሲደፈን ነውና ። ከአዋቂች ፊት መቅደም ፣ ከአባቶች ፊት አስተማሪ መሆን ፣ በማመን በቀደሙን ፊት ስለ መንፈሳዊ ተጋድሎ ማውራት አለመመከርን ይወልዳል ። “ስጡ ይሰጣችኋል” ለገንዘብ ብቻ የተነገረ ሳይሆን ለእውቀትና ለምክርም ነውና መካሪ ስትሆን እውቀትህና ምክርህ ስስት አይኑረው ። ስትሰጥ ይሰጥሃልና ።
ወዳጄ ሆይ !
መልካም መካሪዎች በዓለም ላይ ውድ ናቸው ። ከተገኙ ግን እግዚአብሔር በመልካም አስቦሃል ማለት ነው ። ምግብን አስደሳች የሚያደርገው ማቅረቢያው ንጹሕህና ያማረ ሲሆን ነው ። የጠራ ቋንቋና የከበረ የቃላት አጠቃቀም ለምክር እጅግ ወሳኝ ነው ። የንግግር ችሎታም በራሱ እውቀት ነውና አታናንቀው ። ሰው ምንም ቢማር መግለጫ ቋንቋና ርቱዕ አንደበት ከሌለው እውቀቱ የጋን ውስጥ መብራት ነው ። ብዙ መንገዶች ቢኖሩም የምትሄደው በሚያደርስህ መንገድ ነው ፣ ብዙ ምክሮች ቢኖሩም እውነት የሆነው ምክር ሊገዛህ ይገባል ። መልካም ምክርን በእውነትነቱ እንጂ በስሜትህ አታጣጥመው ። ከሰው ላለመለየት ብለህ የምታደርገው ተግባር ፣ የምትፈጽመው ግዳጅ ራስን የማጥፋት ሂደት ነው ። ምክር በነጻ ቢገኝም ውጤቱ ግን ውድ ነው ። ወደ ገደል የሚገባን ሰው ለማዳን ብትጮህ ክብሬን አጣሁ እንደማትል እየጠፋ ያለ ወገንን ለማትረፍ መቆጣትህ ራስህን ማዋረድ አይደለም ። ያንተ ቍጣ ብቻውን ሊለውጠው አይችልምና ጸጋ መንፈስ ቅዱስ እንዲረዳው ጸልይለት ።
ወዳጄ ሆይ !
የአባት ምክር ማረሻ ነው ፣ መንገድ ይከፍታል ። የእናት ምክር ቀንበር ነው ፣ ስለ ሌሎች መኖርን ያስተምራል ። የመንፈሳውያን አባቶች ምክር ስንቅ ነው ፣ በረሃውን ያሻግራል ። የሸንጋዮች ምክር ዘበት ነው ፣ መሳቂያ ያደርጋል ። የአድር ባዮች ምክር እንብላ እንብላ ነው ፣ ለውርደት ይዳርጋል ። የጨካኞች ምክር የቃየን ወንድም ነው ፣ እጅን በደም ይነክራል ። የፈሪ ምክር ሽብር ነው ፣ ከድል ያስቀራል ። የክፉ ሴት ምክር ረግረግ ነው ፣ ወጣሁ ሲሉ ይይዛል ። ያልሰማኸው የአባትህ ምክር ስኬት ባጣህ ቀን ፣ የናቅኸው የእናትህ ምክር ሁሉም በር በተዘጋብህ ጊዜ ይታወስሃል ። የመንፈሳውያን አባቶች ምክር ዓለም በከፋብህ ጊዜ ከፊትህ ድቅን ይላል ። መከራ የተመከርከውን ያስታውሳል ።
የሰማይ አምላክ ቀኑን ይቀድስልህ !!!
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥቅምት 16 ቀን 2013 ዓ.ም.