የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

የጠፉ እሳቶች

“የጌታችንም ጸጋ በክርስቶስ ኢየሱስ ካሉ ከእምነትና ከፍቅር ጋር አብልጦ በዛ።” 1ጢሞ. 1፡14 ።
ሐዋርያው እስካሁን እየተናገረ ያለው እርሱን ክርስቲያንና አገልጋይ ስላደረገው ጸጋ ነው ። ኦሪታዊውን ወንጌላዊ ፣ ነፍሰ ገዳዩን ስምዐ ጽድቅ/የእውነት ምስክር/ ፣ ቤተ ክርስቲያን አፍራሹን ምእመናን ጠባቂ ስላደረገው ጸጋ በመገረም እየተናገረ ነው ። የሕግ አስተማሪዎች ሊሆኑ የሚወዱ ከጳውሎስ ይልቅ የሕግ አስተማሪ አይሆኑም ። ሐዋርያው ሕጋዊ መሆኑ ክርስቶስን እንዲገፋ ፣ ምእመናንን እንዲያሳድድ ፣ ቅዱስ እስጢፋኖስን እንዲገድል አደረገው ። በሕጋዊነት ውስጥ ጨዋነት ቢኖርም ፍቅር ግን የለም ፤ ቅንዓት ቢኖርም ሰላም ግን የለም ፤ እልህ ቢኖርም ማዳመጥ ግን የለም ፤ ሥርዓት ቢኖርም የልብ መማረክ የለም ። ሕጉማ መልካም ነው ። ለሚጠብቀው ሁሉ በረከትን ያመጣል ። ሰው ግን ሕጉን መጠበቅ ትቶ የሕግ አስተማሪ ሊሆን ሲወድ የእግዚአብሔርን ስጦታ ከማሰብ ለእግዚአብሔር የሚሰጠውን ማሰብ ይጀምራል ። “እነሆኝ የጌታ ባሪያ” ብሎ እንደ እመቤታችን ከመነሣት እንደ እገሌ ቀራጭና ኃጢአተኛ ስላልሆንሁ አመሰግንሃለሁ ይላል ። /ሉቃ. 1፡38 ፤ 18፡11/ ። የእግዚአብሔርን ጸጋ አሳንሶ ለእግዚአብሔር የሰጠውን አስበልጦ ያያል ። ሐዋርያው ግን ጠፍቶ ስለተገኘበት ፣ ሙቶ ሳለ ስለዳነበት ጸጋ ይናገራል ። ጸጋ እግዚአብሔርን የምናይበት መስተዋት ሲሆን ሕግ ግን ራሳችንን የምናይበት መጽሔት ነው ።ሐዋርያው ይህንን የመጀመሪያይቱን የጢሞቴዎስ መልእክት ሲጽፍ ወደ ክርስትና ከመጣ 22 ዓመት ገደማ ሁኖታል ። እንደ አሁን የሚያስበው ግን የመጠራቱን ነገር ነው ። እኛ እግዚአብሔርን ብንሆን ኑሮ ይህንን ማንነት አንጠራውም ነበር ።

ሐዋርያው በእግዚአብሔር ቤት የሚኖርበትን ምሥጢር ያልረሳ ሰው ነው ። የተጠራበት ፍቅር እንደሚያኖረው እየተናገረ ነው ። የሚዋደዱ ወዳጆች በመጀመሪያው ቀን ፍቅር ሁልጊዜ ካልተገኙ አብረው በደስታ ሊኖሩ አይችሉም ። የዛሬው ፍቅራቸውን የሚለኩበት የሙቀት መለኪያ የመጀመሪያው ቀን ፍቅር ነው ። ሐዋርያው የመጀመሪያው ጸጋ በሕይወቱ ሁሉ የሚመራበት ፍቅር መሆኑን ተረድቷል ። በቸርነቱ ጀምሮ በቸርነቱ ለመፈጸም ቆርጧል ። ሐዋርያው የሚያደንቀው ጸጋ እርሱን ክርስቲያን አድርጎ የተቀበለውን ቸርነት ነው ። የልብሱ ጨርቅ ሳይቀር ድዉይ እንዲፈውስ ያደረገውን የእግዚአብሔር ስጦታ ነው ። እርሱን እስከ መታሰርና መገረፍ ያጸናውን የእግዚአብሔር በረከት ነው ። ጸጋው ይጠራል ። ከጫካ ሕይወት አውጥቶ ከሰው ቊጥር ይደምራል ። ጸጋው አገልጋይ ያደርጋል ። ለራሱ ጠፍቶ የነበረው ወግ ደርሶት ሰው ፈላጊ ይሆናል ። ጸጋው በመከራ ውስጥ ትዕግሥትን ይሰጣል ። የተጠራበትን ጸጋ ስላልረሳ ለሌሎች የሚራራ ፣ ለሕይወቱን ሳይሳሳ የሚያገለግል ሆነ ። ለእግዚአብሔር ክብር መኖር ብቻ ሳይሆን መሞትም ፈለገ ። እንደ ፈቃዱ መኖር ብቻ ሳይሆን እንደ ፈቃዱ መሞትንም ተመኘ ። ይህን ሁሉ ፍቅር ፣ በረከትና ጥንካሬ የሰጠው ጸጋው ነው ።
ጸጋው ባለቤት አለው ። የጌታችን ጸጋ ይለዋል ። ጸጋው ለሰዎች ብቃት የተበረከተ ሳይሆን ጸጋው ኃጢአተኞችን በንስሐና በእምነት ያጸደቀ ነው ። ጸጋው የግል ገንዘብ ሳይሆን ጸጋው ባለ ጸጋ አለው ።
ጸጋው የእግዚአብሔር ሲሆን ከጳውሎስ የሚጠበቀው ግን እምነትና ፍቅር ነው ። ጸጋው ለኃጢአታችን የተከፈለው ዋጋ ነው ። እምነት ኃጢአትን አምኖ መናዘዝ መሢሑንም አምኖ መመስከር ነው ። ፍቅር ደግሞ ለእግዚአብሔር መኖር ነው ። ፍቅር ለሚወዱት መኖር ነው ። ጸጋው ሲነካው ለእግዚአብሔር ያለው እምነትና ፍቅር ጨመረ ። ሲያምን እግዚአብሔር እንደሚወደው አረጋገጠ ፤ ሲያፈቅር ደግሞ ለእገዚአብሔር ተቀደሰ ። ልብ አድርጉ የተቀደሰው ለሰው ሳይሆን ለእግዚአብሔር ነው ። የሚፈልጉትን እስኪያገኙ በሰው ፊት የሚቀደሱ ፣ ውጫዊ ማንነታቸውን የሚያጸዱ አሉ ።
ጸጋ የበዛላቸው አገልጋዮች አሉ ፣ ጸጋ የሚያስተላልፉ አባቶችም አሉ ። ጌታችን ግን ጸጋ የሚያሳተላልፍ ሳይሆን ራሱ ባለ ጸጋው ነው ። ፍጥረታት ዘንድ ያለ ጸጋ የተቀበሉት ሲሆን እርሱ ጋር ያለው ጸጋ ግን የባሕርዩ ነው ። በፍጥረታት ዘንድ ያለ ጸጋ ጉድለት ሲኖረው በእርሱ ዘንድ ያለው ጸጋ ግን ፍጹም ነው ። በፍጥረታት ዘንድ ያለው ጸጋ መጪና ሂያጅ ሲሆን የእርሱ ጸጋ ግን ከዘላለማዊ ህልውናው ፣ አካሉ ፣ ስሙና ባሕርዩ ጋር አብሮ የሚኖር ነው ። ጸጋው የሥላሴ መለኮታዊ ርስታቸው ነው ። የጌታችን ጸጋ ቢባልም የአብና የመንፈስ ቅዱስም ጸጋ ነው ። በአካላት ልዩ ቢሆኑም በሀብታት ግን አንድ ናቸው ። በስም ልዩ ቢሆኑም በመስጠት ግን አንድ ናቸው ።
ሰማይና ምድር በውስጣቸው ያሉ ሁሉ ሀብትነታቸው የሥላሴ ፣ ጸጋነታቸው ለእኛ ነው ። ከተሸከምነው አካል የእኔ ብለን የምንኮራበት ምንም ነገር የለምና እርሱም ጸጋ ነው ። ጸጋ እኛን የሚያሳቅቅ ሳይሆን እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን ፍቅር የምንረዳበት ነው ። እግዚአብሔር አምላክ በዚህ ዓለም ላይ ስንገኝ ራሳችንን የምንረዳበት ጸጋ ሰጥቶናል ። ይህንንም ክህሎት እያልን የምንጠራው ነው ። በተፈጥሮ አማካይነት የተቀበልነው ስጦታ ነው ። ሙያ ብለን የምንጠራቸው ነገሮች ሁሉ የእግዚአብሔር ስጦታ ናቸው ። እንጨት መጥረብም ፣ ወርቅ ማንጠርም የእግዚአብሔር ስጦታ ነው ። የእግዚአብሔር ስጦታ ነውና አክብረን ልንይዘው ፤ በሰዎች ላይ ስናየውም ልናከብርላቸው ይገባል ። ቃሉ እንዲህ ይላል፡- እይ ከይሁዳ ነገድ የሚሆን የሆር የልጅ ልጅ ፥ የኡሪ ልጅ ባስልኤልን በስሙ ጠርቼዋለሁ ። በሥራ ሁሉ ብልሃት በጥበብም በማስተዋልም በእውቀትም የእግዚአብሔርን መንፈስ ሞላሁበት የጥበብን ሥራ ያስተውል ዘንድ፥ በወርቅና በብር በናስም ይሠራ ዘንድ ፥ ለፈርጥ የሚሆነውን የዕንቍ ድንጋይ ይቀርጽ ዘንድ ፥ እንጨቱንም ይጠርብ ዘንድ፥ ሥራውንም ሁሉ ይሠራ ዘንድ ።” ዘጸ. 31፡2-5 ። ብዙ ጊዜ መንፈሳዊ ጸጋ ያላቸው የእጅ ጥበብ ያላቸውን አያከብሩም ፣ የእጅ ጥበብ ያላቸውም መንፈሳዊ ጸጋ ያላቸውን አያከብሩም ። የእጅ ጥበብ ምድርን ሲያበጅ ፣ የሰውን ልጅ ኑሮ ሲያቀል ፤ መንፈሳዊ ጸጋ ደግሞ ሕይወትን ያንጻል ። ለዘላለማዊ ሕይወት ያበቃል ። የሰው ልጅ ከመላእክትና ከሌሎች ፍጥረታት ልዩ የሚያደርገው የሁለት ዓለም ወራሽ መሆኑ ነው ። እንስሳት የዚህ ዓለም ብቻ ወራሾች ፣ መላእክት የሰማይ ዓለም ወራሾች ናቸው ። ሰው ግን የምድርና የሰማይ ወራሽ ነው ። ይህንን ዓለም ለመውረስ የእጅ ጥበብ ፣ ሰማይን ለመውረስ መንፈሳዊ ጸጋ ያስፈልገዋል ። እንጀራንና ቃሉን የሰጠ እግዚአብሔር ሥጋዊና መንፈሳዊ ጸጋንም ሰጥቷል ። ሥጋዊ ጥበብ በተፈጥሮ ስንቀበል ፣ መንፈሳዊ ጸጋ ግን ከእግዚአብሔር በመወለድ የምንቀበለው ነው ። እንጨት መጥረብም ፣ ወርቅ ማንጠርም ፣ የሚታዩ ውብ ነገሮችን መሥራትም የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ነው ብሎ ለማሰብ ሰው ቢቸገርም የእርሱ ስጦታ ናቸው ።

ጸጋው በክረስትና በሦስት መንገድ ይገለጣል፡-

1-  የሚያድን ጸጋ ፤ ይህ ክርስቲያን የተባልንበት ፣ ውሉደ እግዚአብሔር ተብለን ወራሽ የሆንበት ስጦታ ነው ። /ኤፌ. 2፡8/።
2-  የሚቀድስ ጸጋ ፤ ይህ ለእግዚአብሔር እንድንኖር የሚያደርገን ፣ ጻድቅ ግን በእምነት ይኖራል የተባለበት ፣ ዕለት ዕለት ሥጋና ዓለምን የምንክድበት የመንፈሱ ሙላት ነው ። /ሮሜ. 1፡17/ ።
3-  የሚረዳ ጸጋ ፤ በመከራና በፈተና ሰዓት በድል አድራጊነት ለመሻገር የሚያግዝ ፣ ተራራን የሚደለድል ኃይል ነው ። /ዕብ. 4፡16/።
ሐዋርያው ከጸጋው የተነሣ ወይም ከእግዚአብሔር ስጦታ የተነሣ ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ያለው እምነትና ፍቅር እየጨመረ መምጣቱን ይገልጻል ።እምነት በተባረደበት ፣ ፍቅር በቀዘቀዘበት ዘመን ሐዋርያውን ማሰብ ይገባናል ። እምነታችሁ ተዳክሞ ፣ ፍቅራችሁ ቀዝቅዞ ከሆነ አሁን ተስፋ አድርጉ፤ የተስፋ እሳት የጠፉትን ሁለቱን ሻማዎች ይለኩሳል ። እነርሱም እምነትና ፍቅር ናቸው ።
ጌታ ሆይ የእኛንም እምነትና ፍቅር እባክህን ጨምረው ።
1ጢሞቴዎስ /16/
ኅዳር 24 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲ.አ.መ.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ