የትምህርቱ ርዕስ | የጸሎት ግብ

“ሰዎች ሁሉ ሊድኑና እውነቱን ወደ ማወቅ ሊደርሱ በሚወድ በእግዚአብሔር በመድኃኒታችን ፊት መልካምና ደስ የሚያሰኝ ይህ ነው።” 1ጢሞ. 2፡3-4 ።
ሐዋርያው ስለ ሰው ሁሉ ጸልዩ ብሎ ነበር ። ጸሎትን ክቡርና ሥሙር የሚያደርገው ስለ ሌሎች መማለድ ካለበት ነው ። ምልጃ የእግዚአብሔር ፍቅር ሲነካን የምናደርገው ልመና ነው ። ስለ ሌሎች ለመጸለይ ፍቅር ያስፈልጋል ። ምልጃ የእግዚአብሔርን ክብር መጋፋት አይደለም ። ምልጃ በሰው ልጆች መካከል መተሳሰብን ፣ በሰማይና በምድር ባሉት ዘንድ መተሳሰርን የሚያሳይ ልዩ መንገድ ነው ። የቤተ ክርስቲያንን አንድነት የሚያጸናም የሚያጎላም ምልጃ ነው ። ሐዋርያው ስለ ሰው ሁሉ እንዲጸለይ ይመክራል ። በዚህም ሦስት ነገሮች እንረዳለን፡-
1-  ሰው ሁሉ በችግር ውስጥ እንደሚያልፍ ፣
2-  የማንጸልይለት ሰው እንደሚያውከን ፣
3-  በጸሎት አድልኦ እንደሌለ እንገነዘባለን ።

ስለ ነገሥታትና ስለሚያስተዳድሩ ሰዎች አብዝቶ መጸለይ ይገባል ። ስለ ቤተ ክርስቲያን አባቶችም ጸሎት መደረግ ግድ ያስፈልጋል ። ስለ ሌሎች ስንጸልይ አብዝተን እየተቀበልን ነው ። ስለ ሌሎች መጸለይ መክሰር ሳይሆን በእጥፍ ማትረፍ ነው ። ስለ ሌሎች ስንጸልይ ልባችን በፍቅር ይሞላል ። ደግሞም ከመፍረድ ይድናል ። ሐዋርያው ይህን መልእክት በሚጽፍበት ጊዜ አብዛኛውን የዓለም ክፍል ይገዛ የነበረው ኔሮ ቴሣር ነው ። ኔሮ ቄሣር ከ54-64 ዓ.ም. ለአሥር ዓመታት ያህል በክርስቲያኖች ላይ ጥላቻ አልነበረውም ።ቤተ ክርስቲያን ትፈተን የነበረው በአረማውያንና በአይሁድ ነበረ ። የጢሞቴዎስ መልእክት ከተጻፈ ቢያንስ ከሁለት ዓመት በኋላ ኔሮ ታላቅ መከራ በክርስቲያኖች ላይ አመጣ ። የሮምን ከተማ የሚበዛውን ክፍል በእሳት አጋይቶ ይህን ያደረጉ ክርስቲያኖች ናቸውና ማንም ሰው ነጻ እርምጃ ሊወስድባቸው ይችላል አለ ። በኔሮ ቄሣር የጀመረው የመከራ ዘመን በ313 ዓ.ም. ታላቁ ቆስጠንጢኖስ ተነሥቶ የእምነት ነጻነት እስኪያውጅ ዕረፍት አልነበረውም ። ይህም ከ64-313 ዓ.ም. ማለት ነው ። ቤተ ክርስቲያን ለሦስት መቶ ዓመታት በሮማ ቄሣሮች ታላላቅ መከራዎችን ተቀብላለች ። ኑሮዋንም በዋሻና በምእመናን ቤት ውስጥ አድርጋለች ። ሐዋርያው ከሁሉ በፊት ስለ ነገሥታትና ስለ መኳንንት ጸልዩ ሲል ይህ ታይቶት ሳይሆን አይቀርም ።
ሐዋርያው ያዕቆብ፡- አትለምኑምና ለእናንተ አይሆንም” ይላል ። /ያዕ. 4፡2።/ አንዳንድ መከራዎች ያለ መጸለይ ውጤት ናቸው ። ጸሎት ቅጥር ነውና ሊጠብቅ ይገባዋል ። ቅጥሩ ከላላ ሕይወታችን ሊደፈር ይችላል ። ዛሬም ስለሚያስተዳድሩት ሰዎች ስለማንጸልይ በዚያ ፈንታ ስድብና እርግማን ስለምናወርድ ሳንግባባ እንኖራለን ። የበላዩ ለበታች እንዲያዝን ፣ የበታች ለበላይ እንዲገዛ ጸሎት በጣም ያስፈልጋል ።
ስለ ሰው ሁሉ ይልቁንም ስለ ነገሥታትና መኳንንት መጸለይ ያስፈለገበት ምክንያትና ግቡ ምንድነው ? ብለን መጠየቃችን አይቀርም ። ሐዋርያው፡- “ሰዎች ሁሉ ሊድኑና እውነቱን ወደ ማወቅ ሊደርሱ በሚወድ በእግዚአብሔር በመድኃኒታችን ፊት መልካምና ደስ የሚያሰኝ ይህ ነው ።” ይላል ። 1ጢሞ. 2፡3-4 ።
የምንጸልይበት ምክንያቱም በእግዚአብሔር ፊት መልካምና ደስ የሚያሰኝ ስለሆነ ነው ። ግቡ ደግሞ ሰው ሁሉ እንዲድንና እውነትን ወደ ማወቅ እንዲደርስ ነው ። ስለ ሰዎች ልንጸልይ እንችላለን ። የምንጸልየው ግን ስለ ምድራዊ ጉድለታቸው ብቻ ነው ። በዋናነት እንዲድኑ መጸለይ ይገባል ። የዚህ ዓለም ማግኘቱም ማጣቱም ፣ መታመሙም ፈውሱም ያልፋል ። የማያልፈው የዘላለም ሕይወት ነው ። ልብ አድርጉ እንዲድኑ እንጸልያለን ፣ እውነቱን እንዲያውቁ እናስተምራለን ። ይህ ብቻ አይደለም እውነቱን እንዲያውቁ ከማስተማራችን በፊት ልንጸልይላቸው ይገባል ። ምክንያቱም ልባቸውን የሚያዘጋጅ የእግዚአብሔር መንፈስ ነው ። ገበሬ መሬቱን አለስልሶ እንዲዘራ ጸሎትም የሰውን ልብ ማለስለሻ ነው ። ቃሉ ደግሞ ዘር ነው ። በጠፍ መሬት ላይ እየዘራን አልበቀለም ብለን እናዝናለን ።
ሰዎች ሁሉ እንዲድኑ እግዚአብሔር ይፈልጋል ። ክርስቶስ የመጣው አንዱን አዳምን ፍለጋ ነው ። ስለዚህ የአዳም ልጅ ያልሆነ የለምና ሁሉን አድራሻ አድርጎ መጥቷል ። ክርስቶስ የሞተው ለዓለም ሁሉ ነው ። በሙሉነት ለእነ እገሌ በከፊል ለእነ እገሌ ሞተ የሚል የለም ። ይህ ከሆነ ሁለት ነገሮችን መገንዘብ ያስፈልገናል ።
1-  ክርስቶስ ለሞተለት ወገን እኛ ለመጸለይ ልንደክም አይገባም ።
2-  ሰው ሁሉ እንዲድንና እውነቱን እንዲያውቅ እግዚአብሔር ይወዳልና የተመረጡና ያልተመረጡ አሉ ብለን መናገር ተገቢ አይደለም ።
ነገሥታትን የረሳናቸው በጸሎት ብቻ አይደለም ፤ በምስክርነትም ረስተናቸዋል ። በዚህ ምክንያት የሚበዙት የዓለም መሪዎች ከሀዲዎች ናቸው ። የሃይማኖት አባቶችም ቤተ መንግሥት ተጠርተው ፣ መድረክ ተሰጥቷቸው የሚናገሩት ዘላለማዊውን ነገር አይደለም ። ሰይፍ ሳይመጣ እንዲህ ዝም ካልን የመጣ ቀን ምን ልንሆን ነው ?
እውነትን ማወቅ የሰው ልጅ ሥነ ልቡናዊና መንፈሳዊ መብቱ ነው ። ጋዜጠኞች ራሳቸውን የሕዝብ ዓይንና ጆሮ አድርገው ይቆጥራሉ ። ሕዝብ መረጃ የማግኘት መብት አለው ይላሉ ። ድምፅ አልባ ለሆኑትም ድምፅ እንሆናለን በማለት ለፍትሕ ይጮኻሉ ። እግዚአብሔርም ሰዎች እውነቱን እንዲያውቁ ይፈልጋል ። እውነት በትምህርት ቤት ፣ እውነት በፍርድ ቤት ስትፈለግ ትውላለች ። እግዚአብሔር እንድናውቀው የወደደው እውነት ግን የዘላለም ሕይወት የሚገኝበትን እውነት ነው ። እርሱም ራሱ እግዚአብሔር ነው ። እውነት ብርሃን ነው ፣ እግዚአብሔርም ብርሃን ነው ። እውነት ነጻ ያወጣል ፣ እግዚአብሔርም ነጻነትን ይሰጣል ። እውነት ያሳርፋል ፣ እግዚአብሔርም ዕረፍት ይሰጣል ።
በእግዚአብሔር ፊት መልካምና ደስ የሚያሰኙ ነገሮች አሉ ። እነርሱም፡-

1-  ሌሎች እንዲድኑ መጸለይ ፣
2-  እውነቱን እንዲያውቁ ማስተማር ናቸው ።
እግዚአብሔር እንደ ቃሉ የሆነ ትጋት ይስጠን !!
1ጢሞቴዎስ /24/
ታኅሣሥ 16 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲ.አ.መ.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም