መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » ይሉኝታ ወይስ እውነታ

የትምህርቱ ርዕስ | ይሉኝታ ወይስ እውነታ

“አምልኮት በእውነትና በመንፈስ መሆን አለበት (ዮሐ. 4፡24) ።
የአዲስ ኪዳን የአምልኮ መስፈርቱም ይህ ነው ።”


አምልኮ እግዚአብሔርን እያዩ በእውነተኛ ልብ መደረግ ይሻል ።

በምድራዊቷ ቤተ ክርስቲያን በአካል ፣ በመንፈስ ደግሞ በሰማያዊቷ ቤተ
ክርስቲያን ተገኝቶ መቅረብ አለበት ። መንፈሳችን በጸሎት ሰዓት ከብዙ
ቅዱሳን ጋር በሰማይ ትገኛለች ። አጠገባችን ከምሥራቅ አገር ፣ ወይም
ከደቡብ የዓለማችን ክፍል የመጣች መንፈስ ቆማለች ።

እኛ ባናይም ብቻችንን ጸሎት አቅርበን አናውቅም ። እግዚአብሔር ጸሎትን
የሚሰማው በእውነተኛ ልብ ፣ ዋጋ ከፋይነቱን በማመን ፣ በኅብረት ሲቀርብ
ነው ። ጸሎትን በሚመለከት አፋዊ ማነብነብ የሆነበት፣ ልባችን ግን
የሌለበት ልመና አለ ።

ሁለተኛው ከሰው የውዳሴ ከንቱ ዋጋ ለመቀበል ፣ ጸሎተኛ ነው ለመባል
የሚደርስ አለ ። ሦስተኛው ሰዎችን በመፍራት የሚደረግ የይሉኝታ ጾምና
ጾሎት አለ ። በአገራችን አንዱ የአንዱ የጾም ፖሊስ ስለሆነ ምን ይሉኛል
ብሎ የሚጾም ብዙ ሰው አለ ።

የጾም ዋጋ ከፋይ ግን እግዚአብሔር ነው ። አምልኮ ከፈሪሀ እግዚአብሔር ወደ
ሰው መፍራት ከወረደ ከንቱ ልፋት ይሆናል ። ይሉኝታ አምልኮን የመበጥበጥ
አቅሙ ከፍተኛ ነው ። ሰማይን እያየን ምድር እንድንቀር የሚያደርገን
በመጠባበቅ ላይ የተመሠረተ አምልኮ ነው ።

በዛሬ ዘመን ሰዎችን ለማብሸቅ የሚደረሱ መዝሙራት አሉ ። ለውድድር ፣ የእኔ
ይበልጣል ለማለትም በእግዚአብሔር ስም የሚቀርቡ አምልኮዎች አሉ ።
ደመወዛቸውን ታሳቢ አድርገው የሚቀድሱና የሚያስቀድሱ ፣ መቅደሱን እንደ
ቢሮ የሚቆጥሩም አሉ ።

አድናቂዎቻቸውን ለማስደሰት መቅደስ ውስጥ በማኅበራዊ ሚዲያ እያስተላለፉ
የሚቀድሱ ፣ ኔትወርኩ ሲቋረጥ ሰው አላየኝም ብለው የሚረበሹ ካህናት
እያፈራን ነው ። ትላንት ድምፅ ማጉያው የነጠቀንን ተመስጦ አሁን ደግሞ
የማኅበራዊ ሚዲያው ሱስ ጨምሮ ወስዶብናል ።

እግዚአብሔርን እያየ የሚዘምር የሚያመልክ እየጠፋ ነው ። ድካሙ አለ ፣
የሥላሴ በረከት ግን የለም ። እግዚአብሔርን ብንፈልገው ይገኝልን ነበረ ፣
የምንፈልገው ሰውን ስለሆነ የሰማይ በረከት አልተገኘም ።

ቤተ ክርስቲያንና በዓላት ፎቶ መነሻ ከሆኑ ሰንብተዋል ። በዓላቱ በዩኔስኮ
መመዝገቡ የሚደንቀው መንፈሳዊ አባት እያተረፍን ነው ። ለቱሪስት መስሕብ
ተብሎ የሚደረግ ምንም ዓይነት መንፈሳዊ በዓል የለንም ።

በዓል ማለት እግዚአብሔርን በቤታችንና በአገራችን ላይ መጋበዝ ማለት ነው ።
የበዓሉ እንግዳ እግዚአብሔር ነው ። በበዓላት ቀን የሚጎበኙን ሳይሆን
አምነው የሚጠመቁ ካፈራን ለእንግዳው እግዚአብሔር ልጆችን እናበዛለት ነበር ።
አምልኮቱና በዓላቱ ይሉኝታ ላይ ስለ ታሰሩ ፣ የልብስ ውድድር ፣ የግሪክ
ቆብ ፣ የኢየሩሳሌም ካባ የምንባባልበት ስለሆነ እግዚአብሔር አልተቀበለውም ።

ይሉኝታ ግዛቱን እያሰፋ ሲመጣ ባለጠጋ የሆነች አገር ሳይሆን የምትመስል አገር
እየፈጠርን እንመጣለን ። በአገራችን በብዙ አካባቢዎች ግጭቶች አሉ ። አንድ
የውጭ ዜጋ ቢሄድ የሚነካው ማንም የለም ። ኢትዮጵያዊ ግን በገዛ መልኩ
በገዛ ወንድሙ ሊጎዳ ይችላል ።

ግብዝነታችን ባዕድን የሚያከብር ፣ ራሱን የሚንቅ አድርጎናል ። እንግዳ ተቀባይ
ነን ፣ ራሳችንን ግን ገና አልተቀበልንም ። እንግዶቻችንን በብዙ ዋጋ
እንቀበላለን ፣ ድሆቻችን እንዳይታዩብን እንሰውራለን ። ውጤቱን ስናየው
ከሚሰጡን የምንሰጣቸው ይበዛል ።

“የስሙኒ ዶሮ የብር ካምሳ ገመድ ይዛ ጠፋች” ይባላል ። ይሉኝታዎቻችን በጣም
ስጉ አድርገውናል ። ዝግጅቶቻችን ከመጠን ያለፉና ራሳችንን
የምናስጨንቅባቸው ናቸው ። ይሉኝታ አባወራውን ትቶ እንግዳውን ወደ ማክበር ፣
የቤቱን ሰው ጥሎ የውጭውን ለማጥገብ ይሰደናል ።

እዚህ ያለው ሙስሊም ስለ ፍልስጤም ፣ እዚህ ያለው ክርስቲያን ስለ እስራኤል
አለሁ ይላል ። ፍልስጤምና እስራኤል ጠባቸው የመሬት እንጂ የሃይማኖት
አለመሆኑን የሚገነዘብ ጥቂት ነው ። የራሳችን ስንት ችግር እያለብን
ተንጠራርተን እናጨበጭባለን ።

ቅድሚያ ለራሳችን አገርና ወገን መስጠት አለብን ። በዓለም ላይ ስመ ጥር የሆኑ
አገራት ለዜጎቻቸው ቅድሚያና ክብር የሰጡ ናቸው ። ራሳችንን ከናቅን
የሚያከብረን የለም ። ሃይማኖት ለዋጮችን ሥራቸውን እንጠየፋለን ።
በሃይማኖቱ የማይጸና ሰው በምድር ላይ የረከሰ ሰው ነው ።

ይህ ትውልድ ምግብ ቤት እንደ መቀያየር ሃይማኖቱን ሲለውጥ ቅር የሚለው
አይደለም ። ታዲያ አንድ ወጣት ሲነግረኝ የሄደባቸው ሃይማኖቶችና
አስተማሪዎች ቅር እንዳይላቸው እስካሁን ሦስት ጊዜ ተጠምቄአለሁ ብሎኛል ።
በጣም ያስፈራል ።

ሦስት ጊዜ የሚያስጠምቅ ይሉኝታ ፣ የሄደባቸው ስለ ጎተጎቱት ነው ። ይሉኝታ
ሃይማኖትን እንድናፈርስ እያደረገን ነው ። አልኮል መጠጥ መጠጣት ውድቀታችን
እንጂ የእኛ መገለጫም አይደለም ። ሌላ ይሉኛል ብሎ የሚጠጣ ሰው አለ ።

ኦርቶዶክሳዊነት በነቢያትና በሐዋርያት መንገድ መሄድ ነው ። መገለጫውም ቃለ
እግዚአብሔርን በኑሮአችን ተዳሳሽ ማድረግ ነው ። ጾምን በኃጢአት የሚቀበል ፣
ጾሙንም በዓመፃ የሚፈስክ በእግዚአብሔር ስም የሚበድል ነውና ለራሱና ለአገር
ትልቅ መከራ ያመጣል ።

እግዚአብሔር ከይሉኝታ ሊፈታን ፣ ለእውነታ ሊያኖረን ይቻለዋል ።
“እግዚአብሔር የታሰሩትን ይፈታል ።” (መዝ. 145 ፡ 7) ።

ይቀጥላል…

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የካቲት 18 ቀን 2017 ዓ.ም

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም