መግቢያ » ትረካ » ደህና ነው » ደህና ነው /5

የትምህርቱ ርዕስ | ደህና ነው /5

ወረኞች ጥንትም ነበሩ ፣ ዛሬም አሉ ። ወረኞች ማለት የወሬ ጥማት ያላቸው ፣ ካላወሩ የሚሞቱ የሚስላቸው ፣ የሰሙትን ምሥጢር መቋቋም አቅቷቸው እንደ ወንፊት የሚያፈስሱ ፣ የጠባያቸው ቀላልነት የሰሙትን መሸከም አቅቷቸው ኧረ ልፈነዳ ነው ? የሚሉ ፣ እንደ ዝንብ በካይና በሽታ አምጪ ነገርን የሚያመላልሱ ፣ የሐሜት ፈረሶች ፣ የሰብቅ ሠረገላዎች ፣ የሰውን ንስሐ የማይቋጥሩ ፣ የሰሙትን ሽሽግ ነገር የሚያሰሙ ፣ እሺ – ይገርማል – ቀጥሎስ በሚሉ ቃላቶች ነዳጅ የሚሰጡ ፣ ነፋስ የሚያመርቱ ናቸው ። ወረኞች ብዙ ዓይነት ሲሆኑ ጥቂቶቹን ግን ማየት እንችላለን፡-

1- የስለላ ጓዶች፡-

የስለላ ሠራተኞች ያስወራሉ እንጂ አያወሩም ። እነዚህ ሰዎችም ሲመረጡ መጠጥና ዝሙት የማይወዱ መሆናቸው ተረጋግጦ ነው ። የስለላ ሠራተኞች አንድ አውርተው መቶ ይቀበላሉ   ። የሚመርጡት ሥራም ማንም ሰው ልብ የማይለውን ነው ። ሰው እንደ ቀላል የሚያያቸው ሰዎችና ቦታዎች ለስላላ ተመራጭ ናቸው ። እነዚህ ሰላዮች የሚከፈላቸው ወረኞች ናቸው ። አገራቸውንና መንግሥታቸውንም የሚጠብቁ ናቸው ። እነዚህ ወሬ ለቃሚዎች ፣ ነጭ ለባሾች ፣ ጆሮ ጠቢዎች የሚያዩትን ሰው ሁሉ አንድ መረጃ አያጣም ብለው ያስባሉ ። ወሬ በዚያ ዓለም መረጃ ይባላል ። የዳቦ ስም መሆኑ ነው ። ከየአቅጣጫው የሚቃረመው ወሬ የሚወቃበት ውድማ አለ ። እርሱም የደኅንነት ተቋም ነው ።

2- ሥራ ፈቶች፡-

ሥራ የሌላቸውና ሥራ ፈቶች ልዩነት አላቸው ። ሥራ የሌላቸው ዕድሉን ያላገኙ ፣ ሁሉም ስፍራ በዘመድ ተይዞ በር የተዘጋባቸው ምስኪኖች ናቸው ። “የሚበላና የሚወራ አይታጣም” እንዲሉ ለቀኑ የሚሆን አንድ ወሬ ካላገኙ የሚንቀዠቀዡ ፣ እገሌ ማለት እንጂ እኔ ማለት የማይችሉ ፣ የሐሜት ዕድር አቋቁመው ፣ እንደ እነርሱ የበታችነት ስሜት የሚያደቃቸውን ሰዎች ይዘው የሚሳደቡ ወረኞች ሥራ ፈቶች ናቸው ። እነዚህ ወረኞች በየትኛውም አገርና የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ናቸው ። ማሰብ የማይፈልጉት ነገር ያላቸውና ሥራ መሥራት የማይወዱ ናቸው ። ልጆችን በሥርዓት አለማሳደግ እገሌ ምን አለ ? እያሉ በልጅነታቸው ወሬ ለቃሚ ማድረግ ፤ አባትሽ ምን ሲሠራ ነበር ?  እናትሽ ምን ስታደርግ ነበር ? እያሉ በከረሜላ ጉቦ መጠየቅ የወሬ ሠራዊትን ማፍሪያ ነው ።

3- ሹመት ፈላጊዎች፡-

በአገራችን በሙያ ሳይሆን በፖለቲካ ተሳትፎ ሹመት ይቸረቸራል ። በዘር ተዋጽኦም መሾም የተለመደ ነው ። በድልድል ቀዶ ጥገና ላይ ሰው ባይመደብም ቀዶ ጥገና የሚሠራውን ሐኪም የሚያውኩ የፖለቲካ ሹመኞች ግን አሉ ። ባለሙያዎች ሙያ በሌላቸው ወረኞች እየታወኩ የሚኖሩባት ምድር ናት ። በአፍሪካ ሥልጣን ሕይወትና ሥራ ነው ። አንድን ሰው ሥልጣን ልቀቅ ማለት ሕይወትህን አስቀምጥ ፣ ሥራህን ተው እንደ ማለት ነው ። ስለዚህ ያለውን እሳት ሁሉ ያዘንባል ። ተናገር ብሎ ፈቅዶ ሲናገሩ ያኮላሻል ። ሥልጣን ቀናተኛ ባሎች በዝተውባት አንለቅሽም ፣ አብረን እንሞታለን ይሏታል ። በቤተ ክህነትም ምሥጢር መጋቢ እየተባሉ ወረኞች ይሾማሉ ። ባይማሩም ፣ ሙያ ባይኖራቸውም ከተማረውና ከባለሙያው በላይ የሚኖሩት ወረኞች ናቸው ። በዚህ ምክንያት አዛኝ መሳይ ፣ ያልቆሸሸ ቀሚስ የሚያራግፉ ፣ ለአንድ እንጀራ የሚልከሰከሱ ፣ ቀኑን በሙሉ እንደ ወፍ ወሬ ሲለቅሙ ውለው ለሚጠብቋቸው አባቶች የሚተነፍሱ አያሌ ናቸው ። እንዳይሳደቡ ተብለው ያለ ሥራ የሚከፈላቸው ፣ ተሳደቡልን ተብለውም የሚከፈላቸውን ሰዎች እያፈላን ነው ። የወረድንበት ዝቅጠት ከባድ ነው ።

4- የወሬ ተዋጊዎች፡-

ከቦታቸው ሳይነሡ ደረስን የሚሉ ፣ አንድ ጠመንጃ ይዘው ተዋጊ አውሮፕላን ይዘናል የሚሉ ፣ ከአደጋ ጣዮች በላይ ወሬ እየጣሉ አገር የሚያምሱ ብዙዎች ናቸው ።  ጦር ካስበረገገው ወሬ ያስበረገገው የሚባለው ለዚህ ነው ። “ከሺህ ጦረኛ አንድ ወረኛ” የሚባለውም በምክንያት ነው ። እነዚህ የፕሮፓጋንዳ ሠራዊት ሌላው ሲታወክ በሰላም የሚተኙ ናቸው ። ይህን ሙያ ብለው የሚሠሩ አሉ ። እንዲሁም ውስጣቸው እየጮኸባቸው የሚጮኹ ሰዎችም አሉ ። እነዚህ ወገኖች ሰው እንደ ጤነኛ ቆጥሯቸው ይሰማቸዋል ። ብዙ መታከም ያለባቸው ወረኞች አሉ ።

5- ተበቃይ ወረኞች፡-

ከበቀል መንገዶች አንዱ ወሬ ነው ። ያንን ሰው ከሰዎች ሕሊና እንዲወጣ ስለ እርሱ ክፉ መናገር አንዱ የበቀል መንገድ ነው ። ይህ መንገድ ግን የሚሰማው ሰው እንዲፈራንና እንዲሰጋን ያደርጋል ። ለእኔም እንዲህ ነው በማለት ሰው ሊሸሸን ይችላል ። “ውሻን በምን ይፈሩታል ቢሉ በአጥንት” ይባላል ።

6- ሱሰኛ ወረኞች፡-

እነዚህ ሰዎች የሚያነሡት ሰው ቢያጡ መድኃኔ ዓለምን እንቦጭቀው ሲሉ ይሰማሉ ። የሰውን ውስጥ ለማወቅ በጣም የሚጓጉ ፣ የማያውቁት ነገር ካለ የሚረበሹ ናቸው ። የሰው ቦርሳ ከፍቶ ማየት የሚወዱ ፣ ሰው ቤት ሂደው ድስት የሚከፍቱ በአስተዳደጋቸው ያልተገሩ ሰዎች አሉ ። ያለ ክፍያ የእገሌ ገቢ ስንት ነው ? ብለው ያጠናሉ ። ከፍለው ወሬን ያስሳሉ ። ስልኩና ዘመናዊ ዕቃው ሁሉ ሐሜት ማፍጠኛ ነው ። ድሮ አንድ ሐሜት ቢያንስ ሦስት ቀን ይፈጅበት ነበር ። አሁን በአንድ ደቂቃ ሐሜት ይሄዳል ።

7- አላውቅም ማለት የሚረብሻቸው፡-

አንድን ሰው ቶሎ ቀርበው ምሥጢሩን አውቀው ፣ ጉድለቱን ተረድተው ፣ ቶሎ የሚንቁት ፣ እንተዋወቃለን እኮ እያሉ የሚያስፈራሩ ፣ በአምስት ደቂቃ ውስጥ የአምስት ዓመት ምሥጢርን ፈልቅው የሚያወጡ ፣ የምስኪኖችን የዋህነት ተተግነው ወሬ የሚለቅሙ ሰዎች አሉ ። እነዚህ ሰዎች አንድ ነገር ሲፈጠር ስለ እገሌ እኔ አውቃለሁ ብለው የሚናገሩ እስከዚያው ግን የሚያደፍጡ ናቸው ። ወላጆች ምንም አያውቁም ወረኛ ልጆች ግን በደንብ ያውቃሉ ። መምህራን ስለዚያ ሰው የሚያውቁት ነገር ጥቂት ነው ። ደቀ መዛሙርቱ ግን ያ ሰውማ እንዲህ ነው በማለት ያጠኑትን ጥናት ያቀርባሉ ። ግያዝ ማለት እንዲህ ዓይነት ሰው ነበረ ።

ዛሬም የግያዝን አገልግሎት እንሰጣለን በማለት ነቢይና ፈዋሽ ነኝ ለሚሉ ምሥጢር ለቅመው ፣ የሰውን ጉድለት አጥንተው የሚያቀርቡ ፣ በደረሰው መረጃ መሠረትም እንዲህ የሆናችሁ እያለ የሚናገር ነቢይና ፈዋሽ ረዳት ሆነው የሚሠሩ አሉ ። 2ነገሥ . 4፡14ን ጠቅሰው ነቢዩ ኤልሳዕ የሱነም ሴት የጎደላትን ነገር አያውቅም ነበር ። ግያዝ ግን መረጃ ሰጠውና ሴቲቱ ወለደች ። እኛም የግያዝን አገልግሎት ማገልገል አለብን ብለው በድፍረት የሚናገሩ ፣ በኩራት የሚሠሩ እናውቃለን ።

ሰዎች ስለ እኛ ኑሮ ለማወቅ ቢጓጉም ፣ ትንሽ አይተው ብዙ ቢያወሩም ፣ ያላቸው መሣሪያ እርሱ ነውና የወሬ ጦር ቢወረውሩብንም ደህና ነው ። በሌላ ዓለም ርእስ ሁኖ የሚወራለትና የሚጻፍለት ትልቅ ሰው ነው ። ስለ እኛ ሲያወሩ የሚወሉ አክባሪዎቻችን ናቸውና ልንረበሽ አይገባንም ። ዋናው አለማማት ነው ፤ መታማት ግን ክብር ነው ። የሚያደርግ ሰው አያወራም ። ወረኞች ያላቸው አቅም ወሬ ብቻ ነው ፣ ያልተማረ ማኅበረሰብም የሰማውን ሁሉ ያምናል ። ቢሆንም መኖር በእግዚአብሔር ነውና ደህና ነው ። እርሱ በቃሉ መኖሪያህ የሰው ፍቅር ነው ሳይሆን የዘላለም አምላክ ነው ብሎናል ። ተሰባሪው ሰው መኖሪያችን አይደለም ። ክንዱ የማይዝለው እርሱ እግዚአብሔር መኖሪያችን ነውና ደህና ነው ።

ደህና ነው /5
ሰኔ 22 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም