መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ጌታ ሆይ እኛ ማን ነን ?

የትምህርቱ ርዕስ | ጌታ ሆይ እኛ ማን ነን ?

 ስማችንን እያወቅን ሥራችንን የማንመዝን ፣ ለምንባለው እንጂ ለምንሆነው የማይገደን ፣ እግዚአብሔርን በመንደራችን አስረን ለሌሎች የት አባታችሁ የምንል ፣ ጠዋት አመስግነን ማታ የምንራገም ፣ ዝም ስትለን እኛን አይነካንም የምንል ፣ ስትነካን የጻድቃን መከራቸው ብዙ ነው ለማለት የምንደፍር ፣ አውቀን ተመርቀን ገና ፊደል የምንቆጥር ፣ ሰማይ ጠቀስ ፎቅ ላይ እየኖርን ጭቃ የምናላቁጥ ፣ ስለ ጨረቃ እያወራን መቃብር የምንቆፍር ፣ ጽርሐ አርያምን እየናፈቅን እንጦሮጦስ የምንወርድ ፣ ወደ ላይ መሄድ ቢያቅተን ወደ ታች ማደግ ማንም አይከለክለንም የምንል ፣ ተማርን ብለን ያልተማረን በማንጫጫት የምንደሰት ፣ የማንበላውን እንጀራ ለድሀ ሰጥተን የምንኮፈስ እኛ ማን ነን ? የእህል ግፍ አለው እያልን ሰው ግን የምንጥል ፣ የውኃ ጡር አለው እያለን ደም የምናፈስስ ፣ ጭቃ ላይ ተቀምጠን እጠበኝ  ተቀያይመን ማረኝ የምንል ፣ የአንገት ንስሐ እንጂ የአንጀት ጸጸት የጎደለን ፣ እንደ ጦጣ ታስረን የምንዘፍን ፣ በምስኪኖች እንባ እንደ ተጠፈርን የረሳን እኛ ማን ነን ?

አምላክ ሆይ መታወቂያችንን የጣልን ፣ መልካችን በእሳት የተቃጠለብን ፣ ጾታችን እንጂ ማንነታችን የማይታወቅ ፣ እየተራብን የምናመነዝር ፣ እየቀጣኸን የምንቀጣጣ ፣ የመጣው ሳያንሰን ሌላ ጉድ የምናፈላ ፣ ዘመንን ማሽተት ፣ ጊዜን ማወቅ የራቀን ፣ በቅጽበት የምንረሳ ፣ አቤት አቤት ብለን በለው በለው የምንል ጸሎትና አድማ የተቀላቀለብን እኛ ማን ነን ? ጤነኛ ሁነን ውለን የትዳር ጓዳችን ሲመጣ አመመኝ የምንም ፣ የተሰጠንን መድኃኒት ንቀን ሌላ መድኃኒት የምንፈልግ ፣ በሞታችንም ተውኔት የምንሻ ፣ እየሰረቅን ዝክር የምናወጣ ፣ የጣር ኑሮ እየኖርን የባለጠጋ ጽዋ የምንጠጣ እኛ ማን ነን ? ሲረዱን በማንኪያ ሰጥተው ባካፋ ሊወስዱት ነው የምንል ፣ የማንኪያውን መልሰን የአካፋውን የማንጠቀም ፣ የሽባ ሩጫ የዕውር ግልምጫ ተብለን የተናቅን ፣ ከተነሣን ማንም አይችለንም እያልን ተቀምጠን የቀረን ፣ የመኖር ሳይሆን የመጋደል ሙያ ያዳበርን ፣ መልካችንን አፍርሰን የሰኞ ገዳይ የማክሰኞ እያልን በአዝማሪ የምንወደስ ፣ የክፉ ባለ አደራ ሁነን ሌላው ሲድን ክፋትን የምንከባከብ እኮ እኛ ማን ነን ? ጌታ ሆይ ንገረን ። አይሁድ ጥቂት ቢታገሡ የምንሰቅልህ እኛ ነበርን ። ቸኩለው ሰቅለውህ ስም ሆነባቸው ። እኛ ግን እንዳልሰቀለ ሆነን ሰቃዮችን የምንረግም ፣ ወንድምን መጥላት ፣ አማኝን ማውገዝ ጌታን መስቀል መሆኑን የረሳን እኛ ማን ነን ? ብትነግረንም አይገባንም ወልድ ሆይ እባክህ ንገረን ። ዓለም ከአንደኛና ከሁለተኛ ጦርነት ተማረ እንላለን ። እኛ ግን ከየትኛውም ጦርነት ፣ ከየትኛውም ስብከት የማንማር ፣ እግዜር እንኳ ያልቻለን ጎበዞች ነን ። እኮ እኛ ማን ነን ? አማኑኤል ሆይ ባንሰማህም ፣ ሰምተን ብንረሳውም እባክህ ንገረን ።
ስንያዝ ጭብጥ የማንሞላ ፣ ስንለቀቅ ዓለም የማይበቃን ፣ ስንታመም አባን ጥሩ የምንል ፣ ሊሻለን ሲል የለም በሉ የምንል ፣ የእግዚአብሔርን ካህናት በጥምጥም የምንደልል ፣ አገልጋዮችህ ሲራቡ ጽድቅ ነው እያልን የምናላግጥ ፣ ርስት የላቸውም እያልን መጠጊያ ግን የማንሰጥ ፣ ካህናትህ ጽድቅ ይልበሱ ሳይሆን አፈር ይልበሱ የምንል እኛ ማን ነን ? ሬሳችንን እንዲመሩ ቀሳውስትን አደራ የምንል ፣ የሞትኩ ቀን አሳምሩልኝ እያልን ለጣፋጭ ሽኝት የመረረ ኑሮ የምንኖር ፣ ለመቃብራችን እንጂ ለሕይወታችን የማንጨነቅ ፣ እሞታለሁ ብለን ዕድር እየገባን እሞታለሁ ብለን ንስሐ የማንገባ እኛ ማን ነን ? ሞትን ባንዴ አስበን ባንዴ የምንረሳ ፣ በየሳምንቱ ዕድር እየከፈልን በየሳምንቱ የማንቆርብ ፣ ቤተ ክርስቲያን ሲዘጋ መሄድ የሚያምረን ሲከፈት የምንጠፋ እኛ ማን ነን ? መለኪያ ጨብጠን በሃይማኖቴ ቀልድ የለም የምንል ፣ አብረውን የሚጠጡ የስም አገልጋዮች ከሃይማኖት ሕፀፅ የምግባር ሕፀፅ ይሻላል እያሉ ስካራቸውን ሕጋዊ የሚያደርጉብን ፣ አምነን ሳይሆን ተደልለን የተኛን ፣ ሆዳችን እያወቀ ዶሮ ማታ የተባልን ፣ በሌለ ዶሮ ኮሶ የጠጣን ፣ መተሬ የተጋትን እኮ እኛ ማን ነን ?  በተስፋ ዳቦ ቦርጭ ያወጣን ፣ በምኞት ጽዋ ጠጥተን የሰከርን ፣ እየተንገዳገድን ሰውን ማለፊያ ያሳጣን እኛ ማን ነን ? አብ ሆይ እባክህ ንገረን ። አባቶቻችን መሐረነ አብ አሉህ ፣ እኛ ደግሞ እግዜርን ተቀይመነዋል አልን ። አባቶቻችን ካንተ ምሕረት ፈለጉ እኛ ደግሞ ምሕረትን እንሰጥሃለን እያልንህ ነው ። ከተቀየምንህ ይቅርታ መጠየቅ አለብህ ። ልጆች ሳንሆን አባቶቻችን የምንል እኛ ማን ነን ? መሪዎቻችን በአደባባይ ከሁሉ ሃይማኖት ጋር ይጨባበጣሉ ፣ ሰፈር ስንመጣ እኛ እሳት አንጫጫርም ፣ ላዩ ልቡን እያሰፋ የሥሩ የሚጠብብን እኛ ማን ነን ? የምንፈልገውን የምንሰማ የማንፈልገን የማንሰማ እኛ ማን ነን ? ሬሳ የሚያቃጥሉ ሕዝቦችን የምንረግም ፣ በቁሙ ግን አቃጥለን የምንገድል ፣ ስንከስሰው የነበርነውን ቀብሩ ላይ ጥሩ ሰው ነበረ የምንም ፣ የሬሳ ክፉ የሌለብን የሰው ክፉ ግን የሞላብን እኛ ማን ነን ?
ጌታ ሆይ በበሽታችን አማረን ፣ በጤናችን የማናመሰግንህ ፣ የምስጋና ባሕል የተነጠቅን ያንተን የእኛ ፣ የእኛን የእኛ የምንል ሁሉን አዋቂውን ለማታለል የምንፈልግ ፣ ጨካኙን እየረገምን ደጉን የማንመርቅ እኛ ማን ነን ? ግብር እየከፈልን አሥራት የማናወጣ ፣ ምድራዊውን መንግሥት አክብረን ሰማያዊውን መንግሥት የናቅን ፣ የምንፈልገውን ባለማወቅ ማግኘት ያቃተን ፣ የማይማታ ባል ፣ የማትጨቃጨቅ ሚስት ፣ የማይገድል ንጉሥ ፣ የማይቆጣ መምህር እውነተኛ የማይመስለን ፣ ያንተን ጸጋ አምጣ የእኛን አሥራት እንቢ የምንል ፣ እኔ ከሞትሁ ማንም አይኑር ያልን ፣ መልካችን ጠፍቶን መስተዋት ላይ የምንውል ፣ ያየነውን መልክ ወዲያው ረስተን ደግመን የምናይ ፣ ከራሳችን ጋር እየኖርን ራሳችን የጠፋን ፣ ስለ ሰው እያወቅን ስለ እኛ የደነቆርን እኛ ማን ነን ? ጌታ ሆይ አንተ ንገረን ። ዋናው ጸሎት ነው እያልን ስናወራ የምንውል ፣ መስቀልህን እየሳምን አንተን የምንሰቅል ፣ ከምህላ በኋላ ምነው በተደባለቀ የምንል ፣ ልባችንን ቤት አስቀምጠን በእግራችን ቤትህ የምንመጣ ፣ አፈር ስሆን ብለን ያበላነውን ቀጥሎ አፈር የምናበላ ፣ በምን ሰዓት እንደምንለወጥ የማናውቅ ፣ አንዴ አፈር አንዴ ሰው ፣ አንዴ መናኝ አንዴ አስመናኝ የሆንን ፣ የማናውቀው ማንነት ድንገት የሚባርቅብን ፣ ጋብዘን የምናኮርፍ ፣ ጸልየን የምንበድል እኛ ማን ነን ? ያረፈደው ደስታ የማይውልልን ፣ ለመርገፍ የምንቸኩል እኛ ማን ነን ?
ጌታ ሆይ የዓለም መፍትሔ ከእኛ ነው እያልን ዓለምን እህል የምንለምን ፣ እኛን የነካ ይጠፋል እያልን እርስ በርስ የምንጠፋፋ ፣ እኛ ማለት ፍቅር ነን እያልን ለዓይን ለመተያየት የተጠላላን ፣ በደብተራ ቅኔ ፣ በአዝማሪ ውዳሴ ፣ በአሚና ማሽሞንሞን ውስጥ የተደበቅን ፣ ትንሽ ባለን ዘመን ሁሉን የምንሰጥ ፣ ብዙ ስናገኝ ምንም የማንሰጥ ፣ ዛሬ ከድቶን በትላንት የምንኮፈስ ፣ የምንለብሰው አጥተን መጋረጃ የምንጋርድ ፣ የታቹን አራቁተን የምንከናነብ ፣ ሽሮ በልተን ዶሮ የምናገሣ ፣ ትንሽ ሰጥተን ብዙ የምናወራ ፣ በቁሙ ሰውን አቃጥለን ሲሞት የማይበላውን በሬ የምንጥል ፣ አበሻ ክፉ ነው እያልን አበሻነቱንም ክፉነቱንም ለማን ሰጥተን እየተናገርን እንደሆነ የማናውቅ ፣ እኛው ገርፈን እኛው የምንጮህ ጅራፍ ፣ ወኔ ክርስትና ፣ ወንድነት እምነት የመሰለን ፣ በስምህ የምናፍር ፣ ራሳችንን በመልካችን በአምሳላችን ፣ በቅንዓት በምቀኝነት የሠራን ፣ አንተ የሠራኸውን መልክ ያፈረስን እኛ ማን ነን ?
ጌታ ሆይ ወይ ቃልህ ወይ ዘመኑ ያልገባን ፣ ከሰማዩም ከምድሩም ያልሆንን ፣ ምድርን ግዙ ተብለን ድሆችን የምገዛ ፣  አመላችንን ትተን ትዳራችንን የምናባርር ፣ በትክክለኛነት ስሜት የሰከርን ፣ የማንሳሳት መልአክ ፣ የማስቀደሻና የሱስ ልብስ ያለን ፣ ስንሰግድ መላእክትን ፣ ስናጫጭስ አጋንንትን የምንመስል ፣ በሙሉ ቀን ሳይሆን በግማሽ ቀን ሺህ ዓይነት ሰዎች የምንሆን ፣ ሰፈሩን አውከን ቤተ ክርስቲያን እንደ ጨዋ የምንቆም ፣ ተበደልሁ እንጂ በደልሁ የማንል እኮ እኛ ማን ነን ?
ጌታ ሆይ ራስን ከመሸንገል ፣ ፈጥኖ ከመርሳት ፣ ልብን አስቀምጦ በአፍ ከመጨዋወት አድነን ። በዚህ ቀን የመሻገር ጉልበት ሁነን ።
ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ክብርና ምስጋና ይሁን ዛሬም ዘወትርም ለዘላለሙ አሜን ።
የነግህ ምስጋና 22
ሚያዝያ 1 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም