መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ግብ የሌለው መንገድ ፣ ቅንነት የሌለው ብርታት

የትምህርቱ ርዕስ | ግብ የሌለው መንገድ ፣ ቅንነት የሌለው ብርታት

“አካሄዳቸው ክፉ ነው ፥ ብርታታቸውም ቅን አይደለም ።” ኤር. 23፡10።

ነቢዩ ኤርምያስ ገና በለጋነቱ ዕድሜ ለነቢይነት አገልግሎት ወጥቶ ከማይሰማ ሕዝብ ጋር ሲታገል የኖረ ነው ። ያ ሕዝብ ደግ ሳይኖር ደግ መስማት የሚፈልግ ፣ በሚደልሉ ነቢያት ማደንዘዣ ወስዶ የተኛ ስለነበር የኤርምያስ ተግሣጽ እየቀሰቀሰው ይበሳጭ ነበር ። ሰላም ፣ ሰላም በሉ ሰላም ይሆናል በሚል ምኞት የጠፋ ወገን ነበር ። ሕይወት ያልዘሩባትን የማታበቅል ማሳ መሆኗን አላወቀም አላስተዋለም ነበር ። ዝሙትን ዘርተው የተባረኩ ልጆችን ፣ ጣዖትን ወድደው ያረፈ ልብን ፣ መግደልን ፈቅደው ሰላምን ይሹ ነበር ። ያ ዘመን የሐሰት ነቢያት የፈሉበት ፣ ከኤርምያስ እውነት የነቢያቱ ውሸት ይግደለን የተባለበት ፤ ሰው በነፍሱ የጨከነበት ወራት ነበር  ። የነገሥታት ልጆች እየተነቀሉ ወደ ባቢሎን በተራ ሲወሰዱ ቀጥሎ እኔ ነኝ ለማለት አእምሮአቸው ተሰውሮባቸው ነበር ። መዓት ደጃቸውን ሲጸፋ ጎረቤቴን እንጂ እኔን አይደለም ብለው ተኝተው ነበር ። ይህ መረጋጋት ከንቱ መረጋጋት ነበር ። ይህ መኝታ ወደ ሞት የሚወስድ መንገድ ነበር ። ኤርያምስ ቀጣዩ ቀን ታይቶታል ፣ እንዳልታየው ለመኖር ግን አልቻለም ። ታይቶት እንዳልታየው ለመኖር መስከር ፣ ማበድ ፣ አብሾ መውሰድ ያስፈልጋል ። የእግዚአብሔር ቍጣ በድለላ ፣ መዓቱም በፉከራ አይርቅም ። የሚርቀው በንስሐና እርስ በርስ በመታረቅ ብቻ ነው ። ካህናት ፣ ነቢያትን ፣ ሹማምንት የጋራ ርእስ ፈጥረው ስለ ኢየሩሳሌም ልዕልና የሚያወሩበት ፣ የድንጋይ ብርድ ልብስ ለብሰው አንዱ ያንዱን ሞት የሚያደንቅበት ነበር ። ከተሜው በነውር ፣ ገጠሬው በጭካኔ የሚወዳደሩበት ዘመን ነበር ። የድሀ ልጅ ተገፋ ፣ ምስኪኑ ተቃባይ አጣ ። አገር ቅርጫ ሁኖ ጥቂቶች ተካፈሉት ። ዘመናዊ ባርነት በወገን ልጅ ሰፈነ ። ድሀውና ባለጠጋው የሚገናኙበት ድልድይ እስኪሰበር ደሀው በጣም ደኸየ ፣ ባለጠጋውም ልክ አጥቶ ፋነነ ። ይህ ሁሉ ከፍታ በምርኮ ፣ ብልጥግናውም በባቢሎናውያን እሳት እንደሚጠፋ ያስተዋለ አንድ ሰው ነበር ። እርሱም በዛሬ ያልተዋጠው ነገ የታየው ኤርምያስ ነበር ።

ልጆች ዛሬ ዛሬን ሲያዩ ፣ አላዋቆች ለአሁን መሻታቸው ሲገዙ ፣ ሞኞች ቀኑን ሲያመልኩ የእግዚአብሔር ሰዎች ግን በመንፈስ ቅዱስ መነጽር አሻግረው ያያሉ ። ቤተ ክህነትና ቤተ መንግሥት የሚሄዱበት ካርታ ጠፍቷቸው ፣ አንዱ ላንዱ ደረቅ ዜማ ያዜምለት ነበር ። ኤርምያስም ካህኑን ቢገስጽ ካህኑ እንደ መስፍን በእንጨት ጠርቆ የሚቀጣው ፣ ገዥው በጉድጓድ ከትቶ የሚያሰቃየው ፣ ዝም በል እያለ የሚያስጨንቀው ነበር ። የሚያዩ እንዳያዩ ፣ የሚሰሙ እንዳይሰሙ የሐሰት ነቢያት ዓይንን አሳውረው ፣ ጆሮን አደንቁረው ነበር ። ሰው የሚወደውን እንደ ምግብ ዝርዝር እያቀረቡ ፣ ሰውም መርጦ እየሰማ ራሱን የሚያታልልበት ዘመን ነበር ። ጠንቋይ ቤት እንዳይሄድ ዘመናዊነቱ እያሳቀቀው ያለ መጋረጃ የሚጠነቁሉ ፣ ራሳቸውን አዋቆችና ብእሴ እግዚአብሔር ፣ ፈዋሴ ዱያን እያሉ የሚጠሩትን ይከተል ነበር ። ጥፋት የተቀጠረባት ከተማ ነጋሪት ቢጎስሙባት አትሰማም እንዲሉ ሰሚ ጠፍቶ ፣ እውነተኛው የእግዚአብሔር ቃል ጆሮ ተነፍጎ ነበር ። ኤርምያስ ብቻውን የሚጮህ ፣ የእግዚአብሔርን ድምፅ የሚያስተጋባ ነበር ። ያንን ትውልድ ልትሸከም የከበዳት ምድር ብቻ ትሰማው ነበር ። ያች ምድር ሰባ ዓመት የተሸከመቻቸውን ተገላግላ ማረፍ ፈልጋ ነበር ።

ነቢዩ ኤርምያስ ብቻውን በመቅረቱ እኔ ነኝ ወይ የተሳሳትኩት? የሚል ግርታ ባይገጥመውም እግዚአብሔርን ግን ወደማይሰማ ሕዝብ ለምን ላክኸኝ? እያለ ይሞግት ነበር ። የእውነት ቃል አገልጋዮች መስቀላቸው እልከኛ ሕዝብን መቻል ነው ። ነቢዩ ኤርምያስ ሕዝቡን ከገሰጸበት ቃል አንዱ፡- “አካሄዳቸው ክፉ ነው ፥ ብርታታቸውም ቅን አይደለም” የሚል ነው ። ኤር. 23 ፡ 10 ።

ዓይናቸው በምሕረት የማታይ ፣ የወደቀን ለመርገጥ ፣ የሞተን ለመደብደብ የምታይ ክፉ ነበረች ። የድሆች ጩኸት የማይሰማቸው ፣ ምስኪኖችን እንደ ጎመን የሚቀረድዱ ነበሩ ። ጠላታቸውን ያልለዩ ፣ አይጎዱንም የሚሏቸውን ሕፃናትና ሴቶች የሚሰይፉ ነበሩ ። የሚናገሩት መርዝ የተቀላቀለ ፈሳሽ ነበር ። ሰው እንዲህ ያስባል ወይ ? እስኪባል ራሳቸውን ያከፉ ነበሩ ። አዎ አካሄዳቸው ክፉ ነበረ ። እጆቻቸው በንጥቂያና በገዳይነት ፣ እግራቸውም ወደ ጥፋት ሥፍራ በመሮጥ ተጠምደው ነበር ። አዎ ያ ሕዝብ በርትቶ ነበር ። በቀትር ዕረፍት ፣ በሌሊት እንቅልፍ አልነበረውም ። ያ ሕዝብ ከፊቱ ላለው ሩጫ ጊዜውን ሳይሆን ነፍሱን መድቦ ነበር ። ያ ወገን ተሰባስቦ በአንድነት አንድ ዓይነት ነገር ያዜም ነበር ። ትጋቱና ብርታቱ ግን ለቅን ነገር አልነበረም ። ለጥፋትና ለመፍረስ ነበር ። እርስ በርሱ ሲጋደል በደንብ የሚገድሉ ባቢሎናውያን መጡበት ፤ የሕዝቡ ርስት ኢየሩሳሌም ፣ የካህናት ርስት የሰሎሞን መቅደስ በፍጹም መደምሰስ ተደመሰሱ ። የወንድማማቾች መጠላለፍ የባዕድ አጥፊን ለመጥራት ነው ።

ካለፉት ዘመናት ይልቅ ዛሬ ሁለትና ሦስት ሥራ የሚሠራበት የሩጫ ዘመን ነው ። ሰዎች የተወሰነ የሥራ ሰዓት ሳይኖራቸው ሃያ አራት ሰዓት የሚሮጡበት ጊዜ ነው ። በአገር ፣ በአህጉር ፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ ሕብረት በዝቷል ። የጋራ ትብብር የሚባሉ ነገሮች ብዙ ነው ። ለአንድ ሰው አንድ ነገር ለመናገር ቀርፋፋ የነበረው ዘመን አልፎ ለሚሊየኖች በአንድ ጊዜ መናገር የሚቻልበት የመረጃ ፈረሰኛ ያለበት ዘመን ነው ። በዚህች ቅጽበት በማኅበራዊ መገናኛ ሺህ ጓደኞችን መመልመል ይቻላል ። ይህ ሁሉ ብርታት ግን ለቅን ነገር አይደለምና እግዚአብሔር ያዝናል ። የእግዚአብሔር ቃልን ዞር ብሎ የሚያየው የለም ፣ የዓመጽ ወሬን ግን ሰው ደጋግሞ ያነባል ። የሰላምን ቃል የሚደግፋት የለም ፣ በለው የሚለውን ግን የሚያስፋፋው እልፍ ነው ። ቀኑን በሙሉ የሚያጠፋ ቃልን ሲሰሙ የሚውሉ ለአሥር ደቂቃ ቃለ እግዚአብሔር ለመስማት አይሹም ። ብዙ መጻፍ የሚችሉ ስለ ሰማያዊ ነገር ለመጻፍ አይፈቅዱም ። እየሄድን ስለሆነ ጎበዝ አንባልም ። የት እንደምንሄድ መናገር ካልቻልን ከርታታ ነን ። ብርቱ ስለሆንን አንደነቅም ። “የበረታነው ለምንድነው ?” የሚለውን ጥያቄ መመለስ መቻል አለብን ።

የተቀመጠ ሰው የለም ፣ ሁሉም እየሄደ ነው ። ዝም ያለ ሰው የለም ፣ ሁሉም እየተናገረ ነው ። የታጠፈ እጅ የለም ፣ ሁሉም እየሰነዘረ ነው ። መንገዱ ግን የሚያደርስ ፣ ብርታቱም ኋላ የሚያኮራ አይደለም ። ዘመኑ ብርታታችን ነው ። ክፋትን እንዳፈጠንበት ደግ ነገርን ብናፈጥንበት ይቻል ነበር ። ብርታታችን የሥላሴ ሕንፃ የሆነውን ሰውን ለማፈረስ ፣ የሰውን ቅስም ለመስበር ነውና ፈጥነን መመለስ ያስፈልገናል ።

በእኛ አገርና በእኛ ዘመን ያልተቋሰለ ማነው ? ያለ ርኅራኄ ስንወጋጋ ከርመናል ። አንድ ሰው ሲነካ ዝም ብለን ነበርና ሕዝብ መነካት ጀመረ ። ስም ማጥፋትን ቸል ብለን ነበረ ፣ አሁን ሐሰተኛ ታሪክ መፈጠርና መነገር ጀመረ ። ከፊታችን ያለው ወንድም ላይ ድንጋይ ሲወረወር ምን ቸገረኝ ? ብለን ነበር ። የቀደሙትን አባቶች ጭምር የሚጠራርግ ተሳዳቢ መጣ ። አካሄዳችን የሚያደርስ አይደለም ፣ ዋናው መሄዳችን ሳይሆን ወዴት እንደምንሄድ ማወቃችን ነው ። ብርታታችን የሚያስመካ አይደለም ። መሪ የሌለው ኃይል መድረሻው ገደል ነው ። የመኪናው ኃይል ያለው ሞተሩ ላይ ነው ። ለመድረስ ግን ትንሽዋ መሪ ታስፈልጋለች ። ያጠፍናቸው ጉባዔዎች ፣ የበተንነው ሕዝብ ይኸው ጦርና እሳት ይዞ መጣ ። ክፉ ሆኖ የተፈጠረ የለም ፣ ክፉዎችን የምንፈጥር እኛው ነን ። ያለን መፍትሔ ከበደልናቸው ሰዎች ጋር መታረቅ ፣ ከእግዚአብሔር ጋር በንስሐ መስማማት ነው ።

ስለ አካሄድህ ሳይሆን ስለመድረሻ ፣ ስለ ብርታትህ ሳይሆን ስለ ቅንነትህ አስብ።

አቤቱ ዘመናችንን አድስ !

ዲያቆን አሸናፊ መኮንን
ሐምሌ 20 ቀን 2012 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም