የትምህርቱ ርዕስ | ግን ለምን ?

“ስለዚህ ምድር ብትነዋወጥ፥ ተራሮችም ወደ ባሕር ልብ ቢወሰዱ አንፈራም።” (መዝ. 45፡2 ።)

ቀጥሎ ያለውን መጠይቅ ስናነብ ከራሳችን ጋር ሙግት ውስጥ ሳንገባ አንቀርም፡-

“የሚፈልጉንን ችላ እንላለን ፣ ችላ የሚሉንን እንፈልጋለን ፤
የሚጎዱንን እናፈቅራለን ፣ የሚያፈቅሩንን እንጎዳለን ፤ ግን ለምን ?”

“የወላጅና የልጅ ፍቅር እንደ ጅረት ውኃ ከላይ ወደ ታች እንጂ ፣ ከታች ወደ ላይ አይፈስም” ይባላል ። ለሚወዱን ምላሽ የለንም ። በሚጠሉን እንበሳጫለን ፣ የሚወዱንን ግን እንደ ስጦታችን ማየት አንችልም ። ስልክ አላነሣ ያሉንን እንደውልላቸዋለን ፣ ስልክ የሚደውሉልንን ወዳጆች ግን ዝም እንላለን ። እነዚያ ሰዎች ስንወዳቸው የጣሉን ፣ እኛም የሚወዱንን ስለጣልን ነው ። መዝራትና ማጨድ በምድር ነው ። “ጠላትህን ውደድ” ከሚል ትእዛዝ ጋር ብዙ ጊዜ እንታገላለን ። ጠላትን መውደድ የሚቻለው ግን ወዳጅን ሲወድዱ መሆኑን እንረሳለን ። ጠላትህን ውደድ የተባለው አፍቅረው ማለት ብቻ አይደለም ። ጠላትህ ባይኖር ዝርክርክ ሆነህ ትቀር ነበር ። ሁሉም ዘመድ አለመሆኑን ያስታወቀህ ጠላትህ ነው ። ወዳጆችህ ሊነግሩህ የፈሩትን ቆሻሻ ያለ ይሉኝታ የነገረህ መስተዋትህ ጠላትህ ነውና ውደደው ። እርሱ እንዳያገኝህ ስትሸሽ ከመጠጥ ቤት ርቀሃል ፣ ጠላትህ “ተቀደስ” እያለ የሚጮህ ንስሐ አባትህ ነው ። ራስን ችሎ መቆም ፣ አንሶ አለመገኘት ፣ ጥገኛ አለመሆን ፣ ጸንቶ መታገል … እነዚህን ሁሉ ያስተማረህ ጠላትህ ነው ። ወዳጆችህ እየተንቀጠቀጡ መርፌውን አልወጉህም ፣ ዓለምን የምታውቅበትን መድኃኒት ጨክኖ የወጋህ ግን ጠላትህ ነው ። ሰው ማለት ማን መሆኑን ያወቅህበት ትምህርት ቤትህ ነውና ጠላትህን ውደደው ።

“ምቀኛ ጎረቤት ዕቃ ያስገዛል” እንዲሉ ጠላትህ ባይኖር ኖሮ ቤት አትሠራም ነበር ። ጸሎተ ሃይማኖትን በጣም ትወደዋለህ ፣ ያ ጸሎት ግን የተረቀቀው ቤተ ክርስቲያን ጠላት ተነሥቶባት ነው ። የተደላደለ የነገረ መለኮት ትምህርት የመጣው አጽራረ ቤተ ክርስቲያን በመነሣታቸው ነው ። ስለዚህ ጠላት ከሚያሳጣህ የሚሰጥህ ይበዛልና ውደደው ።

ምድር ብትነዋወጥ ፣ ወዳጆች ግልብጥብጣቸው ቢወጣ አትፍራ ። የእኔ የምትለው ሰው ይቅርና የእኔ የምትለው አካል የለህምና በከዱህ ሰዎች አትዘን ። እጅና እግርህ እንኳ ያንተ ካልሆነ ሰዎች ለምን የእኔ አልሆኑም ብለህ ትጨነቃለህ ? ሰው የገዛ ልቡ የሚከዳው ፣ ለራሱ እንኳ ዘመድ የማይሆን ነው ። አንዲት ሕይወት ሺህ ፈተና አለባት ። አንዲት ቅጽበት ብዙ ወዳጆችን ታሳጣለች ። ስላጠፋህ የሚሸሹህ ቀድሞም ወዳጆችህ አይደሉም ፣ እውነተኛ ወዳጅ ለሚወድደው የእንደገና ዕድል የሚሰጥ ነው ። ራሳቸውን ይቅር እያሉ አንተን ይቅር ካላሉህ እንደ ራሳቸው አልወደዱህም ማለት ነው ። ድንገተኛው መከራ ለዘመናት የማታውቃቸውን የሰዎችን ማንነት ይገልጥልሃል ። ማዕበሉ ባሕሩን የሚያናውጠው ባሕር ከረጋ ስለሚሸት ነው ። መከራም ከመሞት የሚያድንህ ነው ። እግዚአብሔር ሞትን በሕመም ይለውጣል ። ሁሉን መቀየም ሞኝነት ፣ ሁሉን መለማመጥ ደካማነት ፣ ሁሉን ነገር አክብሮ ማየት ጅልነት ነው ። ንቆ በመተው ብቻ የሚድን ብዙ ሕመም አለ ። የስሜት ስብራት ንቆ በመተው ይድናል ። በቀል ሽንፈት ነው ፤ ይቅርታ ራስን ማዳን ነው ፤ ከዳተኞችን ችላ ማለት ግን አስተዋይነት ነው ።

የኢየሩሳሌም ነፋስ አሥራ ሁለት እንዲሉ ፣ የሰው ልጆች ተለዋዋጭነት እየበዛ ነው ። በሳንቲም የሚሠሩ ማሽኖች ካልከተቱባቸው የያዙትን በጎ ነገር እንደማይሰጡ ፣ ካልበሉ የማይስቁ ጥቅመኞችን ይህ ዘመን ተሸክሟል ። እስከ ዛሬ የነበረው የመደነቅ መግለጫ “ፐ” የሚል ነው ። ዘንድሮ “ፑ” ደርሷል ። በዚህ ሁሉ ውስጥ ግን እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ነው ። እኛ ስለ እግዚአብሔር ፍቅር እንማራለን ፣ እርሱ ግን ፍቅርን አልተማረም ። በባሕርዩ ፍቅር ነው ። እኛ ሰዎችን ስለማንጠላ እንወዳቸዋለን ብለን እናስባለን ፣ እግዚአብሔር ግን መጥላት ስለማይችል የወደደን ሳይሆን ፍቅር ስለሆነ የወደደን ነው ። አዎ ምድር ብትነዋወጥ ከአጠገባችን የነበረው ርቆ ቢተኩስ ፣ አለሁ ያለን ቢሰወር እግዚአብሔር ግን ከእኛ ጋር ነው ። በርግጥም ጣኦት የሆነብን ነገር ተሰብሯልና በመከዳታችን ማዘን አይገባንም ። እግዚአብሔር መሥራት ሲጀምር በእኛ መሠረት ላይ አያንጽም ፣ እግዚአብሔር መሥራት ሲጀምር በማፍረስ ይጀምራል ። አጠገባችን የሚፈርሱትን ነገሮች ስናይ እግዚአብሔር እየሠራ ነውና ደስ ይበለን ! ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን !

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ታኅሣሥ 13 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም