የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ጢሞቴዎስ ነኝ ክፍል 11

ወጣቶችና ወጣቱ አገልጋይ

(የወጣት አገልጋይ ፈተና)

ወጣት የቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ከእኩዮቹ ጋር ያለው ግንኙነት ብዙ ዓይነት መልክ አለው ። የመጀመሪያው ወጣቶች ይህን ዓለም ገና እየተዋወቁ ያሉ ፣ ለሚያዩትን ነገር ሁሉ መደነቅ መልሳቸው የሆኑ የዕድሜ ለጋዎች ናቸው ። ብስለት ስለሌላቸው እዚህ ሲወደዱ የሚያስቡት ከዚህ የበለጠ ፍቅር ሌላ ጋ አገኛለሁ ብለው ነው ። የመወደዳቸው ምሥጢር ወጣትነታቸውና ደም ግባታቸው ይመስላቸዋል ። በዚህ ምክንያት ታላላቅ ዕድሎችን ያሳልፋሉ ። “ገንዘብ በሃያ ዓመት ፣ ልብ በአርባ ዓመት” እንዲሉ ። ወደ ቤተ ክርስቲያን የሚመጡ ወጣቶች ቢያንስ ላለፉት ሃያ ዓመታት በሌላ ዓለም ቆይተው የመጡ በመሆናቸው ቶሎ ለመተከል ያስቸግራሉ ። በየስፍራው ሲተከልና ሲነቀል የሚኖር ዛፍ በቶሎ ይደርቃል ። እነዚህ ወጣቶችም እንደ ቅምሻ ትምህርቶችን ፣ ጉባዔያትን ፣ መምህራንን ሲቀምሱ ስለሚኖሩ ለአገልጋዩ የመደናገር ስሜት ይፈጥራሉ ። የሚጀመሩ እንጂ የሚፈጸሙ ፍቅሮችን የሚያጣው አገልጋይ ግር እያለው ይመጣል ። ሕዝብ ቢያብድም አይከሰስም ። ሕዝብ አቅሙ መሪውን ከምድረ በዳ የማስቀረት አቅም አለው። ለዚህም ሙሴ የመቶ ሃያ ዓመት ዕድሜው ልምድ ፣ የአርባ ዓመት አገልግሎቱ አልረዳውም ። ባገለገለው ሕዝብ ተሰናክሎ መንገድ ቀርቷል ። በሕዝቡ ምክንያት መቃብሩ እንኳ የማይታወቅ ሁኗል ። በየዘመኑ ባገለገለው ሕዝብ ተበልቶ የሚጠፋው አገልጋይ ብዙ ነው ። ካህን ነፍሱን ባገለገለው ሕዝብ እንዴት ነፍሱን ያጣል ?

ወጣቶች አዲስ እንደ መሆናቸው መማር አለባቸው እንጂ የኃላፊነት ቦታን በቅልጥፍናቸው ሲይዙ ካልገለበጥሁ ብለው ያስባሉ ። ዙፋን የሚያጸዳ ሰው ዙፋን ያምረዋል ። ያልተረዳው ነገር ወንበሩ ንጉሥ እንደማያደርግ ነው ። በየቤቱ የንጉሥ ዙፋን አሠርተው የሚቀመጡ አሉ ። ስጦታን በትግል ማግኘት አይቻልም ። ባለስጦታውን በመግፋት ስጦታውን መውረስ አይቻልም ። በቤተ ክርስቲያን በኃላፊነት ላይ ሊቀመጡ የሚገባቸው ፣ አስተዳደርን በሚመለከት የሚታጩ ከአርባ ዓመት ዘለል ቢሉ ይመረጣል ። ጸጋ ያለው ግን በጸጋው በለጋ ዕድሜው ይገለጣል ። ለዚህም ገና ከማኅፀን የተጠራው ነቢዩ ኤርምያስና ዮሐንስ መጥምቅ ምስክር ናቸው ። ወጣቶች በከረሙ ተንኮለኞች ወጥመድ ይጠለፋሉ ። በዚህ ምክንያት አገልጋዩ ላይ በጠላትነት ይነሣሉ ። የሚያስቡት በአእምሮአቸው ሳይሆን በጉልበታቸው በመሆኑ እንደ እነርሱ ወጣት የሆነውን አገልጋይ ፈንግለው መጣል እንደሚችሉ ይሰማቸዋል ። በተንኮለኞች ሴራ የሚወድቁ ወጣቶች ሦስት ዓይነት ምድብ አላቸው ። የመጀመሪያዎቹ ትክክለኛ ጠላቶች ፣ ሁለተኛዎቹ ወላዋዮች ፣ ሦስተኛዎቹ በወዳጅነት የሚጸኑ ትዕግሥተኞች ናቸው ።

አገልጋዩም በወጣቶች በኩል ለሚነሣው ተቃውሞ ማስተዋል አለበት ። ፈረሰኛውን ትቶ ከፈረሱ ጋር መጣላት የለበትም ። ከኋላቸው የሚጋልቡአቸውን ልቡሰ ሥጋ ጋኔን የሆኑትን አካላት ማየት አለበት ። ሁለተኛ ለሕይወቱ ጥንቃቄ ማድረግ አለበት ። ጉልበት እንጂ እውቀት የሚያንሳቸው ለጋዎች አደጋ እንዳያደርሱበት ጥንቃቄ ያስፈልገዋል ። አእምሮ የሌላቸው ሰዎች አእምሮ የመጉዳት አቅም አላቸውና መጠንቀቅ አለበት ። በተንኮለኞች የተጠለፉ የወጣት ሴቶች ተሳትፎ በዚህ ግብግብ ውስጥ ምናልባት “ደፈረኝ ፣ ከእርሱ ወለድኩ” የሚል ይሆናል ። አገልጋዩ ብዙ ሥነ ልቡናዊና አካላዊ ጥቃት ይደረግበታል ። የሚሆነው ሁሉ ሲሆን የነበረ ነው ። አዲስ ነገር የለምና መጽናት ለወጣቱ አገልጋይ የውዴታ ግዴታ ነው ። ስለ ወዳጅ እሬት ይላሳል ። ስለ እግዚአብሔር ሲሉ ይህን መከራና ፈተና መታገሥ ያስፈልጋል ።

ቤተ ክርስቲያንን በጉልበታችን እናገለግላለን ብለው የሚያስቡ ብዙ ወጣቶች አሉ ። ይህ ጉልበት የሥራ ሳይሆን የመደባደብ ነው ። እኔ ጢሞቴዎስም እነዚህን ወጣቶች አስተናግድ ነበር ። ለቤተ ክርስቲያን ትልቁ ጠላትዋ የገዛ ኃጢአታችን እንጂ የውጭው ተጋፊ አይደለም ። የውጭው ጠላት ነፍሳችንን ከሥጋችን ይለይ ይሆናል ። ኃጢአታችን ግን ከእግዚአብሔር ይለየናል ። በዚህ ሁሉ ማመንታት ውስጥ ሳለሁ ከመንፈሳዊ አባቴ ከጳውሎስ መልእክት ደረሰኝ፡- “እንግዲህ ወንዶች በስፍራ ሁሉ አለ ቍጣና አለ ክፉ አሳብ የተቀደሱትን እጆች እያነሱ እንዲጸልዩ እፈቅዳለሁ።” (2ጢሞ. 2 ፡ 8) ። ወጣቶችን የጸሎት ሰዎች እንዲሆኑ ማበረታታት ይጠቅማል ። ምሁራን ቢሆኑ መከራከር ፣ ሰባኪ ቢሆኑ መፎካከር ፣ ዘማሪ ቢሆኑ ቆንጆ መኮልኮል ይቀናቸዋል ። የጸሎት ሰው ሲሆኑ ግን እግዚአብሔርን ያዩታልና ትሑታን ይሆናሉ ። በተንኮለኞች ተጠልፋችሁ ፣ የሌሎችን አእምሮ ተከራይታችሁ በጸጋው የሚያገለግለውን አገልጋይ መንገዱን ብትዘጉበት የምትጣሉት ከማትችሉት እግዚአብሔር ጋር ነው ። ደግሞም በወጣትነታቸው ተሳስተው አገልጋዮችን የወጉ ብዙዎች ዘመናቸውን በጸጸት ሲያሳልፉ ፣ ጸጸታቸውም ፍጹም ዓለማዊ ሲያደርጋቸው አይቻለሁ ። ለአገልጋዮች ዋጋ ክፈሉ እንጂ ዋጋ አታስከፍሉ ። እኔ ጢሞቴዎስ ነኝ ።

ጢሞቴዎስ ነኝ ክፍል 11

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መጋቢት 20 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ