የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ጢሞቴዎስ ነኝ ክፍል 14

ከአገልግሎት በፊት

ሰው ብቻውን አይሆንም ። ወይ ከእግዚአብሔር አሊያም ከራሱ ጋር ያወጋል ። ሰው ካገኘም ከሰው ጋር ያወራል ። ትዝታም እንደ አሁን ትኩስና ወቅታዊ ሁኖ ያነጋግረዋል ። የመምህር ቃልም ከሚኖረው ኑሮ ጋር ሲገጣጠም እንደ ገና አዲስ ፍንዳታ ሁኖ በውስጡ ይጮኻል ። መስፈርት እጅግ አስፈላጊ መሆኑን ቅዱስ ጳውሎስ የነገረኝን ከኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ጋር ማነጻጸር የጀመርኩት አሁን ነው ። ቤተ ክርስቲያን በእምነት የምትቀበል ፣ በፈሪሀ እግዚአብሔር መስፈርት የምትሾም ናት ። የአገልግሎት የመጀመሪያው መስፈርት ፍላጎት ነው ። አገልግሎት ጊዜን ሳይሆን ሕይወትን ሰጥተው የሚገቡበት ነው ። አገልግሎት የፍትፍት ሰደቃ ሳይሆን የመስቀል ጉዞ ነው ። ገሀነምን ከሚያህል የእሳት ዓለም ነፍስ ሲያወጡ ወላፈኑ አይንካኝ ማለት ሞኝነት ነው ። የአገልግሎት ጉዞ ራስን መካድ ያለበት ነው ። ራሴን ከዛሬ ጀምሮ ያለ ክርስቶስ አላውቀውም ብሎ መማል ይጠይቃል ። ይልቁንም ኦርቶዶክሳዊው/ቀጥተኛው ጎዳና ብዙ እንግልት ከውስጥና ከውጭ ያለበት ነው ። ከክርስቶስ ጋር ያልሞተ ፣ ገና ውዳሴና ክብርን ነቅዐ ሐሰት ከሆነው ከሰው ልጅ የሚናፍቅ ጉዞው ይከብደዋል ። ኦርቶዶክሳዊው አገልግሎት በመከራ እድናለሁ ሳይሆን በመከራ የድኅነት ጉዞዬን እፈጽማለሁ ብሎ የሚያምን ነው ።

ኦርቶዶክሳዊው አገልግሎት የሀብት ውድድር ያለበት አይደለም ። ኦርቶዶክሳዊው አምልኮ ስሜትን የሚያነቃቃ ሙዚቃና ጭፈራ ሳይሆን ተመሥጦ ያለበት ነው ። ኦርቶዶክሳዊው ክርስትና ስማዕትነት ያለበት ነው ፣ የጥብዐት/ቅዱስ ጭካኔ/ መንገድ ነው ። ራሱን ያልካደ ፣ የብልጽግና ወንጌል ሰባኪ ፣ የስስት ጦር የወጋው ፣ ግለኝነትን አምላኪ ፣ የራሱን ደሴት መሥርቶ ልጄ ሚስቴ እያለ ኗሪ ኦርቶዶክሳዊው መንገድ አይመቸውም ። ሃይማኖት ከሰው ያልተቀበልነው ፣ በሰው የማንጥለው ነው ።

አገልግሎት ሥራ ቢሆንም በሙያ ብቻ ሳይሆን በጸጋው የምንወጣው ሰማያዊ ግዳጅ ነው ። ወታደርበራሱ ትጥቅ እንደማይዋጋ አገልጋይም የመንፈስ ቅዱስ የጦር ዕቃ በሆነው በጸጋ ያገለግላል ። ቢሆንም የአገልግሎት መስፈርቱ ፍላጎት ነው ። አገልጋይ የሚሆነው በርግጥ መቍረጡ ፣ ዓለምን መካዱ መፈተን አለበት ። ይህን የመሰለ ቆንጆ አንድ ደብር ይገባዋል ብሎ አገልግሎትን ማርከስ ቀጥሎ ያረክስናል ። ጳጳሱ መፍራት ያለበት ዲቁና ሲናቅ ነው ። ዲቁና ሲናቅ ቅስና ይናቃል ፤ ቅስና ሲናቅ ጵጵስና ይናቃል ። አገልግሎት መስፈርት ከሌለ ሰላማዊ ሰልፍ ያማረው ሁሉ ወደ ዐውደ ምሕረቱ ይጠጋል ። ቄሣርን ለመዋጋት ቤተ ክርስቲያንን ምሽግ ያደርጋታል ። ቤተ ክርስቶስ ዘእግዚአብሔር መባሏ ቀርቶ ቤተ ክርስቲያን ዘጴጥሮስ ፣ ቤተ ክርስቲያን ዘጢሞቴዎስ ትባላለች ።

ራሱን የመራ ቤቱን ይመራል ። ቤቱን የመራ አገርና ቤተ ክርስቲያንን ይመራል ። አገልጋይ በግል ሕይወቱና በቤቱ መመዘን አለበት ። ንብረት ጠባቂ እንኳ ሥነ ምግባሩ ይታያል ፣ ተያዥም ይጠራል ። ነፍስን የሚጠብቀው አገልጋይማ ኑሮው መገምገም አለበት ። አገልጋይ በንግግሩ ፣ በአመጋገቡ ፣ በመጠጡ ፣ በግንኙነቱ ፣ በአስተያየቱ ልከኛ መሆን አለበት ። በሁለት ክንፍ በቤተ ክርስቲያንና በዓለም ካልበረርኩ ማለት የለበትም ። ቁጥብነት መከራን ባያስቀርም ይቀንሳል ። እጅግ መራራ ከሆኑ መተፋት አለ ፤ እጅግ ጣፋጭ ከሆኑም ማለቅ አለ ። ድንበር የሌለው አገልጋይ ሁሉ ይደፍረዋል ። ሁሉን ላስደስት የሚልም ሁሉ ይከፋበታል ። ሰውን ብናስደስት እግዚአብሔር ሊያዝንብን ይችላል ። እግዚአብሔርን ስናስደስት ግን እግዚአብሔርን የሚያውቅ ይደሰትብናል ።

ራስን መግዛት የአገልግሎት ትልቅ መስፈርት ነው ። በከተማ ላይ የበላይ ከመሆን በራስ ላይ የበላይ መሆን የተሻለ ነው ። ራስን አለመግዛት ለጸጸት ይዳርጋል ። በሕይወት ሰልፍ ውስጥ ታጋሽ ያልሆነ ሰው ራስን ባለመግዛት ይፈተናል ። ራስን መግዛት በሁሉም ነገሮች ውስጥ ያስፈልጋል ። በፍቅር ራሱን ያልገዛ ከመውደድ አልፎ አምልኮ ውስጥ ይገባል ። የወደደውን ሰው ሲያጣ ሞቱን ይመኛል ። በቸርነት ራስን መግዛት ይገባል ። ችግር በተወራበት ፣ መዋጮ በሚጠየቅበት ቦታ ሁሉ በስሜት እሰጣለሁ የሚሉ ሲጨነቁ እናያለን ። በቁጠባም ራስ መግዛት ይገባል ። ለጤናቸው እንኳ ገንዘብ ላለማውጣት የሚሰስቱ ሰዎች አሉ ። የሰበሰብነውን አንድ ቀን የማናውቀው ሰው ይበላዋል ። በቅጡ መጠቀም መልካም ነው ። በእውነት እያንዳንዱ ተልእኮ አገልግሎት ነው ። ሠራተኛ ሁሉ አገልጋይ ነው ። ስለዚህ ራስን መግዛት ይገባቸዋል ። አዳራሹ በስብሰባ ሲግል ራስን ባለ መግዛት ሹሞችን የሚሳደቡ ሲወጡ ይጨነቃሉ ። ያጨበጨበላቸው ሕዝብም የት ደረሱ አይላቸውም ። በርግጥ ነገሥታት የመከራቸውንም ሰደበን እንደሚሉ የታወቀ ነው። ቢሆንም ስንገሥጽም ራስን በመግዛት ሊሆን ይገባዋል ።

አዎ አገልግሎት የተገነባ ሰብእናና ፣ ያጌጠ መንፈሳዊነት መስፈርቱ ነው ።

ጢሞቴዎስ ነኝ ክፍል 14

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ሚያዝያ 14 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ