የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ጢሞቴዎስ ነኝ ክፍል 6

ተረት

የስህተት ትምህርት ልዩ ትምህርት ፣ ከፊል እውነት ነው ። ይህን የሚያራምዱ ወገኖች ቤተ ክርስቲያንን ለማፍረስ አሊያም ከፍለው ለመውሰድ ይጠቀሙበታል ። በኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን ሁለተኛው ቡድን ተረትና መጨረሻ የሌለው የትውልዶች ታሪክ አፍቃሪ ነበር ። የመጀመሪያይቱ ቤተ ክርስቲያን የትምህርት ነፋስን በተመለከተ ከአይሁድና ከአሕዛብ የተለያየ ውዝግብ መጥቶባት ነበር ። ከአይሁድ የመጣው ሁለት ዓይነት ቅርጽ ነበረው ። የመጀመሪያው ክርስቶስንም ክርስትናንም አንቀበልም የሚለው ቡድን ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ክርስትናን ተቀብሎ ግዝረት ያለ ጥምቀት ፣ ክርስቶስ ያለ ሙሴ ፣ ወንጌል ያለ ኦሪት ብቻውን ሊያድን አይችልም የሚል አቋም የነበረው ክልስ ማኅበረሰብ ነበር ። ከአይሁድ ሦስተኛው ወገን ግን ቤተ ክርስቲያንን የመሠረቱ መቶ ሃያው ቤተሰብና ስምንት ሺህው ማኅበረ እስጢፋኖስ ተጠቃሽ ናቸው ። አይሁድ ለብሉይም ለሐዲስም ቀዳሚ ናቸው ። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከአይሁድ ተገኝቷል ፣ እመቤታችንም አይሁዳዊት ናት ።

ከአሕዛብ የተነሣው ፈተና መዳን በእምነት ሳይሆን በእውቀት ነው የሚል ፍልስፍና ቀመስ የሆነ ፈተና ነበር ። የዚህም መነሻ የግሪክ ሐተታ አማልክትና ፍልስፍና ነበር ። ፍልስፍና ከክርስትና ጋር የተራራቀ ነው ። ፍልስፍና በምድር ጀምሮ በምድር የሚጨርስ ሲሆን ፣ ሃይማኖት ግን በሰማይ ጀምሮ በሰማይ የሚፈጽም ነው ። የፍልስፍና መገኛው የሰው አእምሮ ሲሆን ሃይማኖት ግን መለኮታዊ መገለጥ ነው ። ፍልስፍና ቁሳዊ ነገር ላይ ሲመሠረት ፣ ሃይማኖት ግን መንፈሳዊ ነገር ላይ ይመሠረታል ። ከአሕዛብ የመጣው ፍልስፍና ለብዙ ስህተቶች መወለድ ምክንያት ሁኗል ። በዋነኛነት የክርስቶስን በሥጋ መምጣት የማይቀበል ነው ። ክርስቶስ በሥጋ ካልመጣ ፣ ቤዛ ኵሉ ዓለም ሁኖ በመስቀል ላይ ካልሞተ ዓለም አልዳነም ማለት ነው ። ይህም የቤተ ክርስቲያንን መሠረትና ተልእኮ የሚያናጋ ነፋስ ነው ። እኔም ወጣት የቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ብሆንም ይህ ፈተና ገጥሞኝ ነበር ። በአንደኛው እጄ ወደ አይሁድ ኦሪታዊ ገደል ሊገባ ያለውን ልይዝ ስጥር ፤ በሌላው እጄ ደግሞ በአረማውያን ፍልስፍና እየሰመጠ ያለውን ወገን ለማትረፍ እሞክራለሁ ። እያየሁ ብዙዎች በገደሉ ይወድቃሉ ። ሕፃን ልጅ በእጁ የያዘውን ስለት ቢቀሙት ያለቅሳል ፣ የነጠቀውንም ሰው ይጠላዋል ። ምእመናንንም ከስህተት ትምህርት ስንናጠቃቸው ከማመስገን መቀየም ውስጥ ይገባሉ ። የሚበልጠንን ሰው እንደ ጠላን ፣ ለአዲስ ነገር ዝግ እንደሆንን ፣ ጸጋ እግዚአብሔን እንዳሰርን ያስባሉ ። ሕፃን ልጅ እስኪገባው ተብሎ ስለት በእጁ እንደማይተዉለት ፣ ምእመናን እስኪረዱ ተብሎ መንጋውን በአጥፊው ማስበላት ተገቢ አይደለም ። ሥልጣን አብሮ መወሰን ፣ አንዳንድ ጊዜ ወስኖ ማስከተል ነው ።

ልዩ ትምህርት ያመጡ ወገኖች ለማንበብና ለመፈላሰፍ ሲፈልጉ ተረትና መጨረሻ የሌለው የትውልድ ታሪክ ይዘው የሚመጡ ደግሞ ማንበብና ማሰብን ያቆሙ ናቸው ። የእነዚህ ሰዎች መነሻቸው ሁለት ዓይነት አመለካከት ነው ። የመጀመሪያው እነእገሌን ስላዩ ማንበብና ማወቅ ያሳስታል ብለው ያስባሉ ። ሁለተኛው አመለካከታቸው ለማንበብ ሰነፍ ፣ ለወሬ ግን ብርቱ ናቸው ። የእንቁላሉን ቅርፊቱን እንጂ አስኳሉን አይፈልጉትም ። ሰማይና ምድር የማይችሉትን ሃይማኖት አውርደው ተራና ትንሽ ነገር ያደርጉታል ። ሥርዓቱን ከሃይማኖቱ ያምታቱታል ። ሽቅብ መምህራንን ለማረም ይሞክራሉ ፣ ከሳሽ ናቸው ። ደርሰው በመሃይም ቃሌ ገዝቻለሁ ይላሉ ። መሃይም መማር እንጂ መገዘት አይችልም ። ትልልቅ ሃይማኖታዊ ምሥጢራትን ንቀው ሃይማኖትን ጥለትና የዶሮ አንገት ላይ ያሳርፉታል ። ጾምን በምግብ ለውጥነቱ ይወዱታል ። ያለ ፍቅር መጾምን ግን አይጸየፉትም ። እንደ ኪሎ ሜትር ድንጋይ ባሉበት የሚቀሩ ፣ እውቀት እንዳይነካቸው የሚጠነቀቁ ፣ ድንግል አእምሮ የያዙ ናቸው ። አለማወቅ በሰውም በእግዚአብሔርም የተጸየፈ ነው ። ቃሉም፡- “ሕዝቤ እውቀት ከማጣቱ የተነሣ ጠፍቶአል አንተም እውቀትን ጠልተሃልና እኔ ካህን እንዳትሆነኝ እጠላሃለሁ” ይላል (ሆሴ. 4፡6 ፤ ዮሐ. 17፡3) ። ከሁሉ በላይ በዚህ አመለካከት ካህን ከሆኑ የድንቁርና ጠባቂ ይሆናሉ ።

ታሪክ ደስ የሚል ነገር ነው ። ለዛሬ ማንነትም መሠረት ነው ። ታሪክን ሲተርኩት ሳይሆን ሲደግሙት ክብር ነው ። በዛሬው ውሳኔው ፣ በእምነትና በኑሮው እንጂ በታሪኩ ብቻ እግዚአብሔርን የሚያገኝ ፣ መንግሥቱን የሚወርስ ማንም የለም ፣ ለዚህ ከጸጋው የወደቁ አይሁድ ምስክር ናቸው ። ተኝተው ሲነቁ አዲስ ተረት የሚፈጥሩ ፣ የምናብ ዓለምን ከመለኮታዊ መገለጥ ጋር የሚያስተካክሉ ፣ ስመ እግዚአብሔር እንዳይነሣ ዘብ የሚቆሙ ፣ መለኪያ የሌላቸው መለኪያቸው ስሜታቸው የሆነ ብዙ ሰዎች አገልግሎትን ያውካሉ ። እነዚህ ሰዎች መናፍቃን የሚባሉ አይደሉም ፣ አላዋቂ የሚባሉ ናቸው ። መናፍቅ የሚባለው ቢያንስ በከፊል የሚያውቅ ፣ የሚያነብ ነው ። ሃይማኖትን የራሳቸው ቤተሰብ የግል ሀብት የሚያደርጉ ፣ በስድብ ብዛትና በዱላ ርስት ይዘው ለመኖር የሚፈልጉ ፣ ለሲኦል የፈረሙ ናቸው ። ቤተ ክርስቲያንን የራሳቸው ጎሣና ወገን መጠቀሚያ ፣ አገልግሎቱንም የገንዘብ ማግኛ ያደርጉታል ። ግብር የማይከፈልበት ንግድ በቤተ እግዚአብሔር ያቋቁማሉ ። ልዩ ትምህርት የሚያስተምሩት የሰውን ነፍስ ሲፈልጉ ፣ እነዚህ ደግሞ ሕዝብን አደንቁሮ በመግዛት ገንዘብ የሚሰበስቡ ናቸው ። የኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን በዚህ ጭንቅ ውስጥ ነበረች ። ችግሩ በጊዜው ስላልተወገደ ይህች ቤተ ክርስቲያን ለታላቅ ጉዳት በቅታለች ። አገልጋዩ በዚህ ስበት ውስጥ የተወጠረ ፣ በመስቀል ላይ የተሰቀለውን ክርስቶስን የመሰለ ነው ። ተረት ሕፃናትን ያሳድግ ይሆናል ፣ ጎልማሶችን ግን አያኖርም ። የዘላለም መልእክት የተሰቀለውን መድኃኒት ክርስቶስን ማወቅና ማሳወቅ ነው ።።

አንተ ቸር አገልጋይ ሆይ ! በሁለት ወገን እንደ ተሳለው እንደ ምትሰብከው ቃሉ ፣ ለማንም የማትመች በመሆንህ ሁሉ ይጠላሃል ። ሰማይ ግን ይወድሃልና በርታ ። ጌታ ሆይ ከዚህ መለኪያ ከሌለው ዘመን እባክህ አድነን !

ይቀጥላል

ጢሞቴዎስ ነኝ ክፍል 6

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የካቲት 22 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ