መግቢያ » ትረካ » የወጣት አገልጋይ ፈተና » ጢሞቴዎስ ነኝ ክፍል 7

የትምህርቱ ርዕስ | ጢሞቴዎስ ነኝ ክፍል 7

ሕጋውያን

(የወጣት አገልጋይ ፈተና)

በኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን የነበሩት ልዩ ትምህርት የሚያስተምሩ ፣ ተረትና የታሪክ ትምክሕት ያለባቸው ሰዎች ብቻ አይደሉም ። ሕጋውያንም ነበሩ ። እነዚህ ሕጋውያን የሕጉን አሉታዊ ቅድስና የሚጠብቁ እንጂ አዎንታዊ ቅድስናውን የሚጠብቁ አልነበሩም ። አያመነዝሩም ፣ ለትዳራቸው ግን ፍቅር የላቸውም ። አጠገባቸው ላሉት ሰዎች ቅን ሳይሆን ቅንቅን ናቸው ። አይሰርቁም ፣ ለተቸገረ ለመስጠት ግን ይፈተናሉ ። ባዕድ አምልኮ አያመልኩም ፣ ለእግዚአብሔር ግን በመንፈስ አይሰግዱም ። ለተቀረጸ ምስል አይንበረከኩም ፣ ሰማያዊ መቅደስ ተገኝተው ማምለክ ግን አይችሉም ። ሥርዓትን ያከብራሉ ፣ ለፍቅር ግን ግዴለሾች ናቸው ። ሰዎችን በክብር ቃላት ይጠራሉ ፣ ሲወድቅ ግን አያነሡትም ። ሁሉን ነገር ሂሳብ ውስጥ አስገብተው ሰላምታንም እንደ ውለታ ያያሉ ። አይገድሉም ፣ እነርሱን ካልነካቸው ግን ማንም ቢያልቅ ግድ የላቸውም ። በሰንበት በእግዚአብሔር ቤት ይገኛሉ ፣ የሰንበት ሥራ የሆነውን የተጎዱትን መጠየቅ ግን ይቸገራሉ ። አሥራትን ያወጣሉ ፣ የድሀ መባን ግን ያስቀራሉ ። ውብ ቃላትን ይናገራሉ ፣ ውብ ልብ ግን የላቸውም ።

ክርስትናን የማይገፋ ተራራ አድርገው ይስላሉ ፣ ያስተምራሉ ። የፍቅርን አምላክ በልጅነት ስሜት መጥራት ግን እንደ መዳፈር ይቆጥሩታል ። እግዚአብሔርን በፕሮቶኮል ያወሩታል ፣ በልባቸው ጭካኔ ግን ያስቀይሙታል ። ምስኪን ፊት ያሳያሉ ፣ በዓለም ላይ ካሉ ጨካኞች ጋር በክፋት ይወዳደራሉ ። ስለ ሩቅ አምላክ ያወራሉ ። እግዚአብሔርን ምሕረት እንደሌለው ዳኛ ይስሉታል ። ስለ አስከፊው ፍርድ ይናገራሉ ፣ ነገር ግን አይቀደሱም ። በእንባና በቁጭት ስለ ንጽሕና ሕይወት ያወራሉ ፣ ልባቸው ግን በክርስቶስ ላይ የሸፈተ ነው ። ለእግዚአብሔር የቅድስና ፖሊስ አድርገው ራሳቸውን ሰይመዋል ፣ የወደቀን ሰው ግን በሰበር ዜና ያጣድፉታል ። በንስሐ አያምኑም ፣ ሰው ተመለሰ ቢባልም ማመን ይቸገራሉ ። ወደ እግዚአብሔር ቤት አይገቡም ፣ ለሚገባም በሩን ይዘጋሉ ።

ሕጋውያን አክራሪዎች ናቸው ። አክራሪነት የራስን እምነት በግለት መያዝ አይደለም ። ከእኔ ወገን ውጭ ማንም አይኑር ብሎ ማሳደድ ነው ። ቀኝ ጉንጭህን ለሚመታህ ግራውን አዙርለት የሚለውን እንኳን ለመፈጸም ለማሰብ ይቸገራሉ ። ክርስቶስንም ቢያገኙት የሚጠይቁት ነገር ቢኖር እንዴት እንዲህ ያለ ትምህርት ታስተምራለህ ? የሚል ነው ። የትዳር አጋራቸውን እንደ ዕቃ ይመለከታሉ ። ለራሳቸው ፍላጎት እንጂ ለሌላው ስሜት አይጨነቁም ። በአገር በምድር ያሉት እነርሱ ብቻ መስሎ ይሰማቸዋል ። ለሚሊየኖች የሚያወሩት ነገር ለራስ እንኳ ደግሞ የማያስቡትን ነው ። ኃጢአተኛ ነኝ በማለት ማንም እንዳያያቸው መከላከያ ያበጃሉ ፣ የሌላውን ኃጢአት ግን ሲያውጁ ይውላሉ ። ሕጋውያን የሕይወት ድራማ የሚሠሩ ነው ። የተጠጋቸውን የሚቆርጡ ስለቶች ናቸው ። ልጆቻቸውን በነጻነት ይለቃሉ ፣ የሌሎችን ልጆች በወግ ያስጨንቃሉ ። መለኪያው ስሜታቸው እንጂ መጽሐፍ አይደለም ። የራሳቸው ስህተት ስለሚያስጨንቃቸው በሌሎች ስህተት መደበቅ ይፈልጋሉ ። ሁሉን ማርከስ ይፈልጋሉ ። የራሳቸው ወገን ቢሳሳትም ጽድቅ አድርገው ይደግፉታል ፣ የሌላውን ጽድቅ ኃጢአት ፣ ትምህርቱ ስህተት ይሆንባቸዋል ። ሕጉን እንደ ዜና ያነቡታል ፣ ግን አይፈጽሙትም ። ሕጉን እንደ መዶሻ ሌላውን መምቻ ያደርጉታል ።

ሕጋውያን ከፍቅር የተራቆቱ ናቸው ። በፍቅር ቤት በቤተ ክርስቲያንም ነፍስ በማባረር ፣ ሰዎችን በመክሰስ ፣ ሰላማዊውን ሰው ገፍቶ አውሬ በማድረግ ፣ ለክርስቶስ መንግሥት ጠላት የሚያበዙ ናቸው። ወጣት የቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ከእነዚህ ሰዎች ጋር ወይ በእልህ አሊያም በሽንገላ ሲመላለስ መንፈሳዊ አደራውን ይጥላል ፣ ሰውን ከክርስቶስ በላይ ያከብራል ። እነዚህ ሰዎች መማርን የጨረሱ ፣ ሳያውቁ የሚያውቁ የሚመስላቸው ናቸው ። ሌላው ሰው በይሉኝታ አይሰድባቸውም ፣ እነርሱ ግን የሚያቆማቸው የሕሊና ክብር ስለሌላቸው ትኩስ ጭቃ ይለጥፋሉ ። “ሞኝ ባያፍር ዘመዱ ያፍራል” እንዲሉ ሌላው ይሳቀቅላቸዋል ፣ የብልግና የምስክር ወረቀት የያዙ ስለሚመስል ተዋቸው ከእነርሱ ጋር አትነካኩ ይባልላቸዋል ። ስለ ሠሩ ሳይሆን እንዳይሳደቡ ደመወዝ ይከፈላቸዋል ። ወጣት የቤተ ክርስቲያን አገልጋይን እነዚህ ሕጋውያን ያሳድዱታል ፣ ስህተቱን ፍለጋ ረጅም ርቀት ይሄዳሉ ። ሰው ግላዊ ኑሮ እንዳለው ይዘነጋሉ ። አቃቂር ለማውጣት ይማራሉ ። እንከን ለመፈለግ ወደ አግዚአብሔር ቤት ይመጣሉ ።

እነዚህ ሕጋውያን መንፈሳዊ አገልግሎትን ይጎዳሉ ። ሙያ ስለሌላቸው ለማገልገል ስለሚቸገሩ በአክራሪነት አገልግሎትን እንደ መዥገር ይጣበቃሉ ። ለጽድቅ መጥቼ ለምን ኵነኔ እገባለሁ ? የሚለው ሰው በቀላሉ በእነዚህ ሰዎች ምክንያት ከቤተ ክርስቲያን ይርቃል ። አዳዲስ ነፍሶችን የራሳቸው ለማድረግ ይጋደላሉ ፣ የእግዚአብሔር ነኝ ካለ ስም ይሰጡታል ። በዚህ ምክንያት ለብዙዎች መጥፋት ፣ ለመንጋው ሰላም ማጣት በብርቱ ይሠራሉ ። አሁንም ለእግዚአብሔር ቀናዒ እንደ ሆኑ በውሸት እንባ ይገልጻሉ ። በቍጣ ሲናገሩ እውነታቸውን ያስመስላሉ ። ፊትን መቋጠር የቅድስና ምልክት ያደርጋሉ ። ደረጃን ስለሚያበዙ ወንድማማችነትን ያርቃሉ ። ጥርጣሬን ስለሚዘሩ እረኛውንና መንጋውን ይለያያሉ ። ለሰገደላቸው የቅድስና ማዕረግ ሲሰጡ ፣ ተዉ ያላቸውን ከሥሩ ለመንቀል ይታገላሉ ።

የኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን በእነዚህ ሕጋውያን ፣ ስርየተ ኃጢአትን ፣ ጸጋ መንፈስ ቅዱስን ፣ ንጹሕ ፍቅርን ፣ የመንፈስ አምልኮን በማያውቁ ሰዎች ትናጥ ነበር ። እነዚህ የሳጥናኤል የውስጥ ካድሬዎች ሆነው አገልግሎቱን ያውኩ ነበር ። ሐዋርያውም በዚህ አዝኖ ነበርና እንድበረታ ጻፈልኝ ። (1ጢሞ.1 ፡ 5-11) ። እነዚህን ሰዎች በማባበል ሳይሆን አድራሻቸውን እንዲያውቁ መገሠጽና በውሳኔ ወደ ፊት መገስገስ ይገባል ። ሕልም ተፈርቶ ሳይተኛ አይታደርም ፣ ይሉኛልን ፈርቶ አገልግሎት አይኖርም ።

ይቀጥላል

ጢሞቴዎስ ነኝ ክፍል 7

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የካቲት 25 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም