መግቢያ » ትረካ » የወጣት አገልጋይ ፈተና » ጢሞቴዎስ ነኝ (3)

የትምህርቱ ርዕስ | ጢሞቴዎስ ነኝ (3)

(የወጣት አገልጋይ ፈተና)

የሐዋርያው ጳውሎስ ደጃፍ ላይ ስደርስ በብዙ አሳቦች ልቤ ይንገላታ ነበር ። ወጣት የቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ስለሆንሁ አብዛኛው ሰው የዕድሜዬን ትንሽነት እንጂ የጸጋውን ትልቅነት አያይም ። እግዚአብሔር በደካሞች የሚጠቀም ትልቅ አምላክ ነው ። ትልልቆች እያሉም ትንንሾችን የሚመርጥ አምላክ ነው ። ቃየን ታላቅ ሳለ አቤልን ፣ እስማኤል ሳለ ይስሐቅን ፣ ዔሣው ሳለ ያዕቆብን ፣ ሮቤል ሳለ ዮሴፍን ፣ ኤልያብ ሳለ ዳዊትን የመረጠ አምላክ አሠራሩ ድንቅ ነው ። ምንም እንኳ የቤተ ክርስቲያን መሪ ጳጳስ ብሆንም ሰዎች በቍጣ የሚፈልጉትን እንድፈጽም ያስገድዱኝ ነበር ። ቍጣ ሰዎችን የራሳቸውን ሐሰት እውነት ለማድረግ የሚጠቀሙበት ፊት መሪ ኃይላቸው ነው ። ለቍጣቸው ቍጣን ስመልስ በእኔ ስህተት ውስጥ ለመደበቅ ይሞክራሉ ። የሰዎችን ቍጣ በሚመለከት ብዙ ዓይነት አሳብ በውስጤ ይመላለሳል ። ሰዎች “ተናግሬ ማሳመን አልችልም” ብለው ሲያስቡ ፣ ሌሎች ከቀረቡአቸው ባዶነታቸውን የሚያዩ ሲመስላቸው ፣ ልዩ አሳብ የሚሰጣቸውን እንደ ጠላት ማየት ሲጀምሩ ፣ የብሶትና እኔ ትንሽ ነኝ የሚል ስሜት ሲያዳብሩ ፣ ወስነው ከሰዎች ጋር ሲወያዩ ፣ ተቃውሞን መቋቋም ሲከብዳቸው ቍጠኛ ይሆናሉ ። አስቀድሞ መቆጣት ሰዎችን አስደንግጦ የፈለጉትን ነገር አምጡ ለማለት ይረዳል ብለው የሚያስቡ ሰዎች አሉ ።

አንዳንዶች የሚቆጡት ይችለኛል ብለው የሚያስቡት ሰው ላይ ነው ። ሌላው አናድዶአቸው እኔ ጋ ሲቆጡ እርሱ ይሸከመኛል ብለው እንደ መጡ ይገባኛል ። እሳትን በእሳት ማጥፋት አይቻልምና ለመቋቋም እሞክራለሁ ። በታሪክ ውስጥ ትዕግሥት አጸጸተ ተብሎ ተነግሮ አያውቅም ። ትዕቢትን በትሕትና ፣ ፍቅረ ንዋይን በጸሊዐ ንዋይ ልንዋጋ እንችላለን ። ሁሉን ፈተና ግን በትዕግሥት እናልፋለን ። የትዕግሥታችን መነሻው ፍቅር ከሆነ ፣ በሰዎች መለወጥ ተስፋ እናደርጋለን ፣ የትዕግሥታችን መነሻ ማመቅ ከሆነ ውስጣችነ ተቃጥሎ ያልቃል ። ወጣት የቤተ ክርስቲያን አገልጋይን አንዳንድ የምግባር ችግር ያለባቸው ሰዎች ቆጣ በማለት አቅሙን ለመነቅነቅና ለመፈተሽ ይሞክራሉ ። ይህ ሲገጥመኝ ጸንቼ በመቆም ፣ ያሉበትን አድራሻ እንዲያውቁት አደርጋለሁ ። ትዕግሥት ፈሪነት ሳይሆን የልብ ስፋት መሆኑን እንዲያውቁት እፈልጋለሁ ። ሽማግሌዎችም የሚቆጡት እኛ ያልነው ብቻ ይሁን በማለት ነው ። ወጣቶች ሽማግሌ እንደሚሆኑ ረስተው ግፍ ያስቀምጣሉ ፣ ሽማግሌዎች ወጣት እንደ ነበሩ ረስተው መፍረድ ያበዛሉ ። በዚህ ሁሉ ውስጥ አገልጋዩ በትዕግሥት መገላገል አለበት ። ቤተ ክርስቲያን ቤተሰብ ናትና ችግሯ በቤተሰብ ጉባዔ ማለቅ አለበት ። የቤተ ክርስቲያንን ምሥጢር ወደ ዓለም ያወጣ ሰው ክርስቶስን በታሪኩ ለሁለተኛ ጊዜ ይሰቅለዋል ። ሊሰድበን አሰፍስፎ ባለው ዓለም ላይ የዘለፋ ርእስ ማበደር ከእኛ የራቀ ይሁን !

የሐዋርያውን ደጃፍ እያንኳኳሁ ሳለሁ የሞት ፍርደኛ መሆኑን አሰብሁ ። ዓለም አንድን ድንግል አንድን መነኩሴ እንዴት ትገድላለች ? ብዬ ማሰብ ጀመርሁ ። መነኮሳት ሞተናል ብለው ከዚህ ዓለም የተለዩ ናቸው ። የሞተን ታዲያ እንዴት እንገድለዋለን ? መነኩሴ ሀብትን ፣ ውርስን ፣ ሥልጣንን አልፈልግም ብሎ ፣ ምሎ በቃል ኪዳን የተለየን ነው ። ከእኛ ምንም የማይፈልገውን ፣ በፈቃዱ ድሀ የሆነውን መነኩሴ በሙሉ ዓይናችን ማየት እንኳ ነውር ነው ። ደግሞም የተከለከለውን ሳይሆን የተፈቀደውን እንኳ ትቶ ራሱን ብሑት ብቸኛ አድርጎ ፣ በጾምና በጸሎት ተወስኖ የሚኖርን መነኮስ ለሞት ማጨት የግፍ ግፍ ነው ። እኛ የማንፈልገውን ጫካ ቤቱ ፣ የማንበላውን ቅጠል ምግቡ አድርጎ የሚኖረውን ፣ በመካነ አራዊት በአጥር ለማየት የምንፈራቸውን አራዊት በዓይኑ እያየ ፣ ግርማ አራዊትን የታገሠውን ፣ ዓለምን በጸሎት የሚጠብቀውን ፣ በፈቃዱ የክርስቶስ እስር የሆነውን መነኮስ መግደል ትልቅ ዕዳ ለዓለም የሚያመጣ ነው።

የአምናን ቀን አማሁት ለአፌ ልጓም የለው ፣
መጣ የዘንድሮ እጅ እግር የሌለው ፤

መነኮሳት ዘማውያንን በምርጫቸው ይገሥጻሉ ። እነርሱን ባየን ጊዜ በአንድ መርጋት አቅቶን ከሆነ ፣ ስለ ክርስቶስ ፍቅር ከሴት ርቆ ፣ ንጽሕ ጠብቆ መኖር ይቻላል ለካ የምንልባቸው ፣ ልካችንን የሚያሳዩን መስተዋት ናቸው ። እነርሱ አባትና እናታቸውን የተዉ በመሆናቸው ቤተ ክርስቲያን ሁሉም ነገራቸው ናት ። ቤተ ክርስቲያን ሰጎን እንቁላልዋን ነቅታ እንደምትጠብቅ መነኮሳትን መጠበቅ አለባት ። ቤተ ክርስቲያን ለመነኮሳት እናት ብቻ ሳትሆን ልጅም ናት ። እነዚህን የክርስቶስ እጮኞች ለአደጋ የጣለች ቤተ ክርስቲያን ነገ የሚረከባት ትውልድ ፣ የሚጠብቃት መንፈሳዊ ወታደር አታገኝም ። ብሉያት በሐዲሳት ፣ ሐዲሳት በሊቃውንት ይተረጎማሉ ። ሊቃውንት ያልተረጎሙትን መነኮሳት በሕይወታቸው ይተረጉሙታል ። እናት ስትሞት ጎጆውም ይሞታል ። መነኮሳት ሲሞቱ ገዳማት ይሞታሉ ። ገዳማት ሲሞቱ ጥበብ መንፈሳዊ አብሮ ይሞታል ። መነኩሴ እንዴት ይገደላል ? የሞተን መግደልስ ምን ይባላል ?

ይቀጥላል

ጢሞቴዎስ ነኝ ክፍል 3

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የካቲት 16 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም