መግቢያ » ትረካ » የወጣት አገልጋይ ፈተና » ጢሞቴዎስ ነኝ (1)

የትምህርቱ ርዕስ | ጢሞቴዎስ ነኝ (1)

(የወጣት አገልጋይ ፈተና)

ደጁን ስጸፋ ፈጥኖ “አቤት” ያለው ቅዱስ ጳውሎስ ነበር ። ቅዱስ ጳውሎስ፡- “የእኔን በር የሚጸፉ የጌታን ደጅ እንደሚመቱ ነው ። እርሱ በሩን በጸሎት ሲያንኳኩ ደስ ይለዋል ፣ ፈጥኖም ይከፍታል ። ደግሞም ወደ ቤቴ በእንግድነት የሚመጣው በሚታየው ሰው ውስጥ የማይታየው ክርስቶስ ነው” ብሎ ያምናል ። ስለዚህ በሩን ስመታ ፈጥኖ “አቤት” አለ ። “አቤት” ለማለትና ተነሥቶ ለመክፈት እነ ማርቆስ ፣ እነ ቲቶ ነበሩ ። ጳውሎስ ግን ክብርን በክርስቶስ ስላገኘ የፕሮቶኮልና የዲፕሎማሲ ክብርን ተጸይፎት ነበር ። ምክንያቱም ውሸት ነውና ። የፕሮቶኮል ክብር አንዱን ሰው ፣ በቀን ውስጥ ሁለት ዓይነት ሰው አድርጎ ያውለዋል ። በቀይ ምንጣፍ ላይ የሚሄዱት እቤት ሲገቡ ዳዴ እያሉ ከልጃቸው ጋር ይጫወታሉ ። የአገር በጀት አጽድቀው በቤት ወጪ ከሚስታቸው ጋር ሲጨቃጨቁ ያመሻሉ ። ብዙ ሰዓት ያነበቡ የመሰሉ ወይዛዝርት ፀጉራቸውን ሲሠሩ አንግተዋል ። በሌሎች ጭንቅላት ያስባሉ ፣ በሌሎች እጅ ይጽፋሉ ። ቅዱስ ጳውሎስ ክርስቲያን የሆነው ይህ ሰልችቶት እንጂ ፣ ይህን ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ለማምጣት አልነበረም ። እውነተኛ ክብርን የሚሰጥ ነበር ። የእውነተኛ ክብር መገኛው ፍቅር ነው ። የማንወደውን ሰው አናከብረውም ፣ የምናከብረውንም እንወደዋለን ።

ሰው ሁሉ ለራሱ ክብር አለው ። ባልንጀራውን እንደ ራሱ ሲወድድ ያከብረዋል ማለት ነው ። ዘመናዊነት ክብርን ያሳጣ ፣ ክብርንም በማታለያ የለወጠ ፣ በጥርስ እየሳቀ በልብ የሚያንቅ ነው ። ዘመናዊነት ሰውን በሕፃን ባሕል የለወጠ ፣ የተጣበቀ ልብስ ፣ ጣፋጭ የበዛበት ምግብ ፣ ተራ ንግግርን ያበዛ ነው ። ሰው በምድር የተቀመጠ ልዑል ነው ። የንጉሥ ልጅ ነውና ። ልዑል የሚናገረው የቤተ መንግሥት ቋንቋ ፣ የክብር ልሳን ነው ። ዝንቦች በቆሻሻ ቦታ እንዳሉ ፣ ውርደት ባለበትም አጋንንት አሉ ። በድን ወዳለበት አሞራ እንዲሰበሰብ ቅሌት ባለበትም ሕፃናተ አእምሮ ይከማቻሉ ። ክርስቲያን ለክብር ባይኖርም ክብሩን ጥሎ ግን አይኖርም ። ዱርዬ የሚባለው ክብር ሲሰጡት የሚቆረቁረው ፣ ሌላውንም ለማክበር የሚቸገር ነው ። ከመንግሥተ ሰማያት እንጦሮጦስን ፣ ከአኃዜ መንጦላዕት/መጋረጃ ያዥነት ስደትን የመረጠው ሰይጣን ይባላል ።

ቅዱስ ጳውሎስ ከአንጾኪያ እስከ ሮም ድረስ ያሉት አብያተ ክርስቲያናት መሥራችና አባት ነው ። በሌላ አነጋገር የዓለም አብያተ ክርስቲያናት አባት ነው ። አጭር ፣ በበሽታ ያደቀቀው ፣ ልብሱ የነተበ መሆኑን ያየ ጳውሎስ ነው ብሎ አይገምትም ነበር ። በሲላስ ጥንካሬ ፣ በማርቆስ መለሎነት በእኔ በጢሞቴዎስ ለጋነት መሐል ፤ አንድ እንደ ማታ ጀምበር ውበቱ የሚናፍቅ ሰው አለ ። ጳውሎስ ሐዋርያ በወርቅ በተሠራ አዳራሽ ፣ በዝሆን ጥርስ በተጌጠ ቤተ መንግሥት የሚኖር አልነበረም ። አንድም ቀን በጌጠኛ መቅደስ አልቀደሰም ። በዋሻና በድሆች ክርስቲያን ቤቶች ቀድሶ አቍርቧል ። ጳውሎስ መንግሥተ ሰማያት የሌለች ያህል በምድር ላይ ገነትን በሕንፃ ልሥራ ብሎ የታገለ አልነበረም ። ብርና ወርቅ የለኝም ብሎ ፈውስ ግን ያለው ሐዋርያ ነበር ። በድህነቱ ኮርቶ የሚኖር መናኝ ነበር ። ብርና ወርቅ ያላቸው ግን ፈውስ የላቸውም ። የሚሰማቸውን አያረጋጉም ። ዓለምን ለመናቅ የሄደው ሕዝብ ፍቅረ ንዋይ አድሮበት ይመለሳል ። በንብረት የሚወዳደር አገልጋይ ሌቦችን ያፈራል ። ጳውሎስ ድንግል ፣ መናኝ እንጂ መሳፍንት አልነበረም ። እንደ ወይዛዝርት በወርቀ ዘቦ የሚኵነሰነስ ፣ እዩኝ ብሎ አደባባዩን የሚሞላ አልነበረም ። የማንንም ሆድ አባብቶ የመዝረፍ ዕቅድ አልነበረውም ። ደቀ መዛሙርቱንም የልመና ስልት አላስጠናም ። ሰውን መውደድ አስተማረ እንጂ ።

ጳውሎስ የተጠጋውን እንደ እሾህ የሚያደማ ፣ እንደ ቆንጥር የሰውን ልብስ ይዞ የሚያበላሽ አልነበረም ። ደመወዝ ነሥቶ ክሰሱኝ ብሎ የሚናገር ሰውም አይደለም ። ሰው እየራበው ይሞታል እንጂ እንዴት ይከስሳል ? አጥሩ የእሳት ፣ በሩ የናስ አልነበረም ። የበሩ መወርወሪያም ከተበላሸ ቆይቷል ። አጥሩም በሩም አንድ ስለ ነበር ሲንኳኳ ቶሎ ይሰማል ። በቀላሉ የሚገኝ ፣ ልጆቹን ከማግኘት የበለጠ ተግባር ያልነበረው አባት ነበር ። እግሮቼ ወደ ጳውሎስ ቤት ይፋጠናሉ ። ያየሁትን የሮምን መውደም ፣ የሰውን በኀዘን መዋጥ ፣ በክርስትናው ላይ የተጋረጠውን አደጋ የምረሳው ጳውሎስ ሲናገር ስሰማ ብቻ ነው ። የአገልጋይ ድምፅ የሞት ሁከትን ጸጥ ያደርጋል ። ሳቁም ያጽናናል ፣ ተግሣጹም ያበረታል ፤ ዓይኑም እጁም ይናገራል ። ጳውሎስ ተቀምጦ ሲያስተምረኝ ብቻ ሳይሆን በሩን ሳንኳኳ እርሱ “አቤት” ቢለኝ ይዤው የመጣሁት ሸክም ይቀለኛል ። ችግሮች ወደ ወዳጅ ስንሄድ ከገለባ ይልቅ ይቀላሉ ። ሰነፍ ነንና ይህን አናደርግም ። ሰነፍ አይጽናናም ።

ይቀጥላል

ጢሞቴዎስ ነኝ ክፍል 1

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የካቲት 12 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም