መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » ጥምቀትና ንስሐ

የትምህርቱ ርዕስ | ጥምቀትና ንስሐ

የዮሐንስ መጥምቅ ስብከት ፣ የጌታችንም የመጀመሪያ አዋጅ “ንስሐ ግቡ” የሚል ነው ። ንስሐ ከሰማይ ወደ ምድር የተላከች የሕይወት ሳሙና ናት ። ንስሐ በጥምቀት ትመሰላለች ። ንስሐ የእንባ ፈሳሽ አላትና ። ንስሐ የሰውን መጸጸት እግዚአብሔር በምሕረቱ ሲያከብረው ማለት ነው ። ሰይጣን ፣ ሰይጣን ሆኖ የቀረው ንስሐን በመጥላቱ ነው ። ሰውንም ሰው የሚያሰኘው ይቅርታ ሲጠይቅ ነው ። ንስሐ ጀርባችንን ለሰጠነው ጽድቅ ፊትን መስጠት ነው ። ንስሐ መመለስ ነውና የኃጢአትን ጉዞ አለመጨረስ ነው ። ንስሐ መዶሻ ነውና ሰማይ ጠቀስ የሆነውን ጥቅመ ሰናዖር/የኃጢአት ግንብ ማፍረስ ነው ። ንስሐ ስለት ነውና እኛንና ደጉን አባት የከለለውን ጥቁር መጋረጃ መቅደድ ነው ። በሕይወት ውስጥ ፣ በመንፈሳዊ ዓለምም ንስሐ ቀዳሚ ነው ። ጸጋን ከመለመን ንስሐ መግባት ፣ የበደልነውን ሰው ጥቅሙን ከመፈለግ ይቅርታ መጠየቅ ቀዳሚ ነው ። ንስሐ ቀዳሚ ጸጋ ነው ። ይቅር ከመባል የበለጠ ጸጋ የለም ። በምድር ላይ ሰዎች ይቅር እንዲሉን እንፈልጋለን ፣ ያንን ማግኘት ግን ከባድ ነው ፤ ሰዎች ይቅር እንዲባሉ እንጂ ይቅር እንዲሉ አይፈልጉም ። እግዚአብሔር ግን የምሕረት እጁን ዘርግቶ ይቅር እላችኋለሁ ኑ ሲለን እንዘገያለን ። ጌታችንም ፣ ዮሐንስ መጥምቅም ንስሐን የመጀመሪያ ስብከታቸው ማድረጋቸው እውነት ነው ።

ጌታችን ወደ ዮሐንስ መሄዱ የዮሐንስን አገልግሎት ለማጽደቅም ነው ። ይህን የመሰለ ዕድልና አንደበት ይዞ በበረሃ መቀመጡ ብዙዎችን አስገርሞ ይሆናል ። ጌታችን ግን የሚሻል ነገር እንደ መረጠ ለመመስከር ወደ ዮሐንስ ሄደ ። ዮሐንስ የወንጌል መድረክን ያነጠፈ ፣ ንጉሡ ሲመጣ የተሰወረ ሎሌ ፣ ሙሽራውን እንዳይጋርድ ቁመቱን የደበቀ ሚዜ ነው ። ንስሐ ግቡ የሚለው ትምህርት ከሮማ ባርነት ነጻ ለመውጣት ፣ ለዕድላችን መኮላሸት ምክንያቱ ቄሣር ነው ለሚለው ሰበበኛ የሚጥም አይደለም ። ጫካ ለገባው ቀነናዊ ቡድን ፣ ወኔን ለሚቀሰቅሱ ፈሪሳውያን የማይጥም መልእክት ነው ። ትልቁ ባርነት ግን ከቄሣር ይልቅ የዲያብሎስ ነው ። ትልቁ ነጻነትም ከሥጋ የነፍስ አርነት ነው ። ኃጢአት ጨለማ ነውና ዓይንን ያውራል ። ኃጢአት ባርነት ነውና በፍላጎት ብቻ ቀንበሩ አይሰበርም ። ያማ ቢሆን ኖሮ ኢየሱስ ከኃጢአት ሊያድነን ባልመጣ ነበር ። ኃጢአት ግዛት ነውና ከዚያ ለመውጣት ነፍሱን አሲዞ የሚታደግ ነጻ አውጪ ይፈልጋል ። ኃጢአት በሽታ ነውና በዙሪያ ያሉትን ሁሉ ይበክላል ። አዎ ተላላፊ በሽታ ነው ። ንስሐ የሚባል ክትባት ይፈልጋል ። ኃጢአት ውስጥ ያለውን ሰው የሚያማክሩ አባቶች ሳይቀር በጸሎትና በኃይለ መንፈስ ቅዱስ መሸፈን አለባቸው ። “ጨው ውኃ ልትቀዳ ወደ ወንዝ ወረደች ፣ እንኳን ልትቀዳ ውኃ ሆና ቀረች” እንዲሉ ።

እኛ እኮ የአብርሃም ልጆች ነን እያሉ የሚኩራሩ ከንስሐ ይዘገያሉ ። እምነት ራስን በመስጠት እንጂ በታሪክ ብልጽግና የሚድኑበት አይደለም ። ታሪክ መልካም ነው ። በውስጡ ብዙ ዋጋዎችን ያሳያል ። ታሪክ ግን ካልደገሙት ሕመም ነው ። ክርስትና ሕያው ነው ። ታሪክን እንደ ጣኦት የሚያመልኩ አይሁድ ክርስቶስን ለመቀበል ተቸግረዋል ። ንስሐ እምነት ነው ። ሰው በገዛ አፉ በደሉን የሚያምንበት ነው ። ፍርድ ቤት ትልቁ ክርክር ሰው ጥፋቱን እንዲያምን ወጥመድ መዘርጋት ነው ። በንስሐ ግን ሰው ያለ ከሳሽ ራሱን ይከስሳል ፣ ያለ ዳኛ በራሱ ይፈርዳል ። ውጤቱም በራሱ የፈረደ አይፈረድበትም ። እኛ የአብርሃም ልጆች ነን እያሉ የአብርሃምን አምላክ መስቀል የሚገርም ነው ። ትምክሕት ማንም ባልወደቀበት በደል እንድንወድቅ ያደርጋል ። ትምክሕት ምሽግ ነውና ሰባኪ ይህን ምሽግ ሲያፈርስ የተጠላ ይሆናል ። በአገራዊ ቋንቋ ባንዳ ፣ በመንፈሳዊ ቋንቋ መናፍቅ ይሰኛል ።

ጌታችን በተነሣሕያን መካከል መገኘቱ ንስሐን የሚወድድ አምላክ መሆኑን ያሳያል ። ሊቀ ካህኑ በተነሣሕያን መካከል ተገኘ ። ካህን ፣ ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ ኃጢአትን ይቅር የሚል አበሳን የሚደመስስ ነው ። ይቅር ሲል እንደ ትላንትናው ቀን ፣ ተመልሶ እንደማይመጣው ያሳልፈዋል ። ሲደመስስ ጽሕፈቱ ዳግም ላይታይ ይፍቀዋል ። አዎ በበደልን ቍጥር ራሳችን ላይ ሞትን እየመዘገብን ነው ፤ ጽሕፈቱ ፣ የእኩይ ፍልስጣ ብዕሩ በንስሐ ይደመሰሳል ። /እኩይ ፍልስጣ የሚባል ሰይጣን እየተከታተለ የሰውን በደል የሚመዘግብ ነው ይባላል/

ዮሐንስ ተነሣሕያኑን በውኃ የሚያጠምቀው ይቅር መባላቸው እንዲሰማቸው ነው ። ንስሐ የራስን ኃጢአት ብቻ ሳይሆን የእግዚአብሔርን ምሕረት ማመን ነውና ። መታጠቡ ኃጢአት የሚያቆሽሽ ጭቃ ስለሆነ ነው ። ጭቃን ለልብሳችን እንሰቀቀዋለን እንኳን ለነፍሳችን ። ጭቃ ቶሎ የመታጠብ ፍላጎትን ያሳድራል ። በንስሐ ከታጠባችሁ ስንት ዓመት ሆናችሁ ?

ልባችንን ለንስሐ ያነቃቃልን !

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥር 17 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም