መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » ጥምቀት እውነት ነው !

የትምህርቱ ርዕስ | ጥምቀት እውነት ነው !

እጅግ ኃጢአት በበዛባት ናዝሬት በጽድቅ የኖረውን ክርስቶስን ፣ ራሱም ጽድቅ የሆነውን መሢሕ ለማግኘት ዮሐንስ መጥምቅ ጓጉቷል ። በዓለም ላይ እውነተኞች ይኖራሉ ፣ እውነት ግን አይደሉም። ክርስቶስ ግን ራሱ ጽድቅ ወይም እውነት ነው ። ውኃ ሲያዩ ጥማታቸው እንደሚያይልባቸው ሰዎች ክርስቶስን ባየ ጊዜ ዮሐንስ ዕረፍትን ናፈቀ ። እርሱ በስድስት ወር አገልግሎቱ የሰው ልጆች የወደቁበት አረንቋ ፣ ከገዛ አንደበታቸው በሚሰማው የጸጸት ድምፅ ጻድቅ ነፍሱ ትጨነቅ ነበር ። እኔ ለጥቂት ወራት የከበደኝን የዓለሙ ጌታ ለዘላለም ሳይጥል የሚሸከም ነው እያለ ይገረም ነበር ። ሰውን ለማዳን መፍትሔው ሰው መሆን ነው ብሎ ፣ ባሕርየ ሰብእን ገንዘቡ አድርጎ ፣ ባዕድነትን ሽሮ የመጣው ልዑል ፣ የዮሐንስ መጥምቅ የዝማሬ ርእስ ነበረ ። አዎ ዛሬም ልንታደጋቸው የምንፈልጋቸውን ሰዎች ፣ ሰው በመሆን ልንቀርባቸው ይገባል ። ደግሞም እውነተኛ ወዳጅ መሆን ያሻል ። ካልተወዳጀነው በቀር ቍስሉን የሚያሳየን ማንም የለም ። ክርስቶስ ሰው ብቻ ሁኖ ሳይሆን አምላክም በመሆኑ ድኅነትን ፈጸመ ። ለሰውነትማ ዮሐንስ መጥምቅ ቀድሞ መጥቶ ነበር ። እኛም በራሳችን ፍቅር ብቻ ሰውን ማዳን አንችልም ፣ አምላካዊ ኃይል ያስፈልገናል ።

ማዶና ማዶ ፣ ናዝሬትና ዮርዳኖስ ሆኖ ሠላሳ ዓመት አለመተያየት ይደንቃል ። ቅንድብና ዓይን ጎረቤት ቢሆኑም ተያይተው አያውቁም ። ባሻገር ያለውን የምታየው ዓይን የጎረቤቷን ማየት አለመቻልዋ ይደንቃል ። የገዛ ቤተሰባችን ያለበትን ሁኔታ መገንዘብ አቅቶን ዓለም አቀፍ የእርዳታ ተቋም ልንመሠርት እንችላለን ። ሥራ የሚጀመረው ግን ከቅርቡ ነው ። ነቢዩ በእግዚአብሔር ቤት የመኖር መስፈርትን ሲያወጣ እንዲህ አለ፡- “ዘመዶቹንም የማይሰድብ” (መዝ. 14 ፡ 3)። ለደጅ ሰው ክብር ያለው ብዙ ይገኛል ፣ የገዛ ዘመዶቹን የሚያከብር ግን ይፈለጋል ። ቤተሰብን ማክበር ራስን ማክበር ነው ። በአንዳንድ አገራት የአገር መሪ ለመሆን መልካም የቤተሰብ መሪ መሆን መስፈርት ነው ። ነቢዩ ኢሳይያስም ስለ ተወደደው ጾም ሲናገር፡- “እንጀራህንስ ለተራበ ትቈርስ ዘንድ፥ ስደተኞቹን ድሆች ወደ ቤትህ ታገባ ዘንድ፥ የተራቈተውንስ ብታይ ታለብሰው ዘንድ፥ ከሥጋ ዘመድህ እንዳትሸሽግ አይደለምን?” ይላል ። (ኢሳ. 58 ፡ 7) ። ለቅርብ ሰው ክብርና አሳቢነት ሊኖረን ይገባል ። ጌታና ዮሐንስ ግን ቅርብ ቢሆኑም ሠላሳ ዓመት አልተያዩም ። ጌታ በዓይን ያየዋል ፣ ዮሐንስ በእምነት ያስተውለዋል ።

ዮሐንስ እጅግ ወንጀለኞችን አይቷል ፣ የብዙዎችንም ንስሐ ሰምቷል ። ሰው ሁሉ በልብስ ተሸፍኖ እንጂ ያልወደቀ ማግኘት ከባድ ነው ። ያልታወቀበት ኃጢአተኛ በተጋለጠው ኃጢአተኛ ይስቃል ። አንዳችን ስለ አንዳችን ከምናወራ እግዚአብሔር ስለ ሁላችን ቢናገር ምድር የትሑታን መንደር ትሆን ነበር ። ወደር የሌላቸውን ኃጢአተኞች ባየ ዓይኑ ወደር የሌለውን ቅዱስ አገኘ ። ጽድቅ የጥምቀት ወይም የዮርዳኖስ ርእስ ነው ። ራሱ ጽድቅ ነኝ ያለው ጌታ ሥጋ ለብሶ በማዕከለ ዮርዳኖስ ቆሟል ። “እግዚአብሔር ጻድቅ ነው” የተባለለት አብ በደመና ይመሰክራል ። መንፈሰ ጽድቅ ጰራቅሊጦስ በአምሳለ ርግብ ወርዷል ። ተነሣሕያንም ጻድቃን እውነተኞች ነበሩ ፤ ስለ እውነት የሚመሰክረው የግንባር ሥጋ የሆነው ዮሐንስ መጥምቅም ጻድቅ ነው ። ዮርዳኖስ በጽድቅ ተሞልቶ ነበር ።

ጌታችን ዮሐንስ አላጠምቅህም ቢለው፡- “አሁንስ ፍቀድልኝ ፤ እንዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና አለው ።” (ማቴ. 3 ፡ 15 ) ። ጥምቀት ጽድቅ ፣ እውነት ፣ ፍትሕ ፣ ርትዕ ፣ ሚዛናዊነት የሰፈነበት ነው ። ሰው ከሕገ አራዊት ከመገዳደል ፣ ያሸነፈ ይኑር ከሚል የቃየን ሥርዓት በኦሪት ሕግ ወጣ ። ኦሪትም ያቆሰለ ይቍሰል በማለት ቍስልን በቍስል የምትከፍል ምድራዊ ሕግ ሆነች ። የገደለ ይግደል ስለምትልም ሁለት ሟች አመረተች ። ጌታችን በዮርዳኖስ የክርስትናውን ጽድቅ መሠረተ ። ስለ እውነት መቆም ፣ ለሌሎች ጥቅም ራስን መሥዋዕት ማድረግ ፣ አቅመ ደካሞች የሚኖሩበትን ዓለም መፍጠር ፣ የበደሉ ሰዎችን በይቅርታ መፍታት ይህ በዮርዳኖስ የተገለጠው ጽድቅ ነው ። እስከ ዛሬ የኖረው ጽድቅ አብርሃም በሚበልጠው በመልከ ጼዴቅ መባረኩ ፣ እስራኤል በትልቁ አሮን እጅ መናዘዛቸው ነው ። አሁን ግን በሚያንሰው ባሪያ በዮሐንስ እጅ በመጠመቅ ፣ ጽድቅ የሚያንሱንን ማክበር መሆኑን ገለጠ ።

ይህ ጽድቅ በጥምቀቱ ሊያበራ ይገባዋል ። የሃይማኖት መሪዎች ሥርዓቱን ለመፈጸም ብቻ ሳይሆን ትኩስ ቍስልን ለመሻር ፣ የበደለን በርግጥ በድለሃል ለማለት ጥምቀትን መድረክ ሊያደርጉት ፣ ሊያስታርቁበት ይገባል ። የገደለውን ኃይለኛ ፈርተው ገዳይን የሚያባብሉ ፣ መታገሥ አለብህ ብለው ካባ የሚደርቡ መሆን አይገባቸውም ። መታገሥማ የቆሰለው ፣ የሞተው ድርሻ ነው ። ሕገ አራዊት ላሸነፈ ማቀንቀን ነው ። ይህን ጽድቅ ሊፈጽሙ ይገባል ። እስካሁን በብዙ መመሳሰል ፣ ለሥጋ በማድላት ፣ የተቀየሙት ሲጎዳ በመደሰት አሳልፈው ይሆናል ። “አሁንስ” የምትለዋ ቀስቃሽ ቃል ግን እንደ መርፌ መውጋት አለባት ። “አሁንስ ፍቀድልኝ ፤ እንዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናልና አለው ።” (ማቴ. 3 ፡ 15 ) ። አዎ “አሁንስ” ማለት ይገባናል ። ዕድሜአችን ሸምግሏል ። ዓለም በቃኝ ብለን መንነናል ። ቤተ ክርስቲያን ቀለብ ሰፍራ እያኖረችን ነው ። “አሁንስ” ብለን የተጠቃውን ልንታደግ ፣ አጥቂውን ለንስሐ ልንጋብዝ ግድ ይለናል ። ጥምቀት ጽድቅ ነው ። አሜን !

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥር 24 ቀን 2016 ዓ. ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም