የትምህርቱ ርዕስ | ጥበብ

ጃፓናውያን፡- “ጥበብ የራቀው እውቀት ልክ በአህያ ላይ እንደ ተጫነ መጽሐፍ ነው” ይላሉ ።

እውቀትን የምናስተላልፍበት ሕጋዊ መንገድ አንደኛው ማስተማር ነው ። ማስተማር ደግሞ የንግግር ችሎታን የሚጠይቅ ነው ። ማስተማር ከሌለበት ምንም ቢማሩ የጋን ውስጥ መብራት ተብሎ ከመጠራት ውጭ ጥቅም የለውም ። እውቀት ተግባርና ማስተላለፍ ወይም ልግስና ይፈልጋል ። ከእውቀት ዓላማ ውጭ እውቀትን መያዝ ወንጀለኛ ያደርጋል ። ንግግርም የልምምድና የትምህርት ውጤት ነው ። በልምምድ አፍ እንደ ፈታን በልምምድም መልካም ተናጋሪ እንሆናለን ። ከዚያ ባሻገር እግዚአብሔር አንደበትን በጸጋ ይፈታል ። በመከራ ዘመን ቃልም ይሰወራልና፡- “ወደረኞቻችሁ ሁሉ ሊቃወሙና ሊከራከሩ የማይችሉትን አፍና ጥበብ እሰጣችኋለሁና” ብሎ ተስፋ ሰጥቶናል ። ሉቃ . 21፡15 ። ይህን ለዘወትር የማስተማርና የግንኙነት ዘይቤ ብንናፍቀው ላናገኘው እንችላለን ። የመከራ ዘመን ረድኤት ለሰላም ዘመን አይመጣም ። እስራኤል መናን በምድር በዳ እንጂ በከነዓን አልበሉም ። ባለ መናውም ፣ መናውም ፣ ሕዝቡም አሉ ። ያለ ጊዜውና ያለ ቦታው ጸጋ አይመጣም ። እውቀትን የምናስተላልፍበት የንግግር ችሎታ ከእውቀት ትምህርታችን ጋር አብሮ መጓዝ ይኖርበታል ። ምክንያቱም መኪና መንዳት የሚለማመድ ሾፌር ለመሆን እንጂ ወረቀቱን ለመያዝ አይደለም ። በተፈለገ ሰዓት አለሁ ለማለት መኪና ይለማመዳል ። መኪና ካልገዛሁ አልለማመድም የሚል የለም ። አዋቂም የሚፈለግበት ብርሃናዊ ዘመን ይመጣል ። በሕፃንነትና በብልግና ባሕል የተያዘው ዘመናዊ ትውልድ ግራ የገባው ቀን አዋቂዎችን ይፈልጋል ። ሰይጣናዊ እውቀቶች አሉ ፣ ጥይትን የሠራ እውቀት ቢሆንም ለሰው መድኅን የማይሆን እውቀት አጋንንታዊ ነው ። መድኃኒትን የሚሠራ እውቀት ደግሞ ከእግዚአብሔር ነው ።

የሚማር የኋላ ዕዳው ማስተማር ነውና የንግግር ችሎታን ማዳበር አለበት ። በማስተማር ውስጥ የሰው እውቀቱ ሕያው እየሆነ ይመጣል ። “ማስተማር እንደገና መማር ነው” ይላሉ ። የበታቾቹን የሚያስጠና ተማሪ እየተማረ ያልገባው ትምህርት ሲያስተምር ይገለጥለታል ። ንግግር የማናደርግ ከሆነ ለመርሳት በሽታ እንጋለጣለን ። ጭንቀትም እያጠቃን ይመጣል ። መንደር ውስጥ ችግር እንጂ ጭንቀት የለም ። ሲለፈልፉ አእምሮአቸው ነጻ እየሆነ ይመጣል ። ባለመናገር ቃላት እየተረሱ ይመጣሉ ። ቋንቋ ኋላ የመጣ ነውና በየዕለቱ ካልተጠቀምንበት ወደ አገሩ ይመለሳል ። የንግግር ችሎታ የሌላቸው አዋቂዎች ወይ ዝምታን ይመርጣሉ ካልሆነ ግን ቃላትን የማይመርጥ ተራ ተናጋሪ ይሆናሉ ። “ሞኝ ባያፍር ዘመዱ ያፍራል” እንዲሉ በንግግራቸው ወዳጆቻቸው ሳይቀር ይሳቀቃሉ ። ከሃያ አምስት ዓመት በፊት አንድ የገጠር ከተማ ለአገልግሎት ሄድሁ ። በዚያች ከተማ የነበረው ትልቅ ምግብ ቤት ምሳ ተጋበዝሁ ። ምሳው ግን የቀረበው በአዲስ ፖፖ ነው ። የዚያ አገር ሥጋ እንደ ጥጥ ያለ ፣ ጣዕሙ ልዩ ነው ። አሁንም ግን ከሥጋው ማቅረቢያውን ሳስብ እስቃለሁ ። ቃላት ወይም ንግግር እውቀትን ማቅረቢያ ሰሐን ነውና ልንጠነቀቅለት ይገባል ።

ጃፓናውያን፡- “ጥበብ የራቀው እውቀት ልክ በአህያ ላይ እንደ ተጫነ መጽሐፍ ነው” ይላሉ ። ጥበብ የንግግር ችሎታ ነው ። ጥበብ ጊዜን ፣ ቦታንና ሁኔታን መመዘን ነው ። እውቀትን የእጅ ስልካችንም ተሸክሞታል ። ኮምፒዩተርም አህያ ልትሸከመው የማትችለውን ሺህ መጽሐፍ ተጭኗል ። የመቅጃ መሣሪያም ብዙ እውቀትን ሰምቶ ያሰማል ። ሰውን ግን ከእነዚህ ቁሳቁሶች ልዩ የሚያደርገው ጥበብ ነው ። የምንጠቅሳቸው ጥቅሶች ከእግዚአብሔር ቃል ቢሆኑም ጊዜውን የማይመጥኑ ከሆነ ጥበብ ከድቶናል ማለት ነው ። ለፈውስ የተሰጠውን ቃል ሰው ለማቍሰል የምንጠቅሰው ከሆነ የበቀል መሣሪያ አድርገነዋል ፤ እግዚብሔርንም የዓመፃችን ተባባሪ አድርገነዋልና ቅጣት አለው ።

ማስታረቅ ሰው እግዚአብሔርን የሚመስልበት ትልቅ ግብር ነው ። እግዚአብሔር ራሱ ሰው ሁኖ ዓለምን ከራሱ ጋር አስታርቋል ። ማስታረቅ የእግዚአብሔር ልጆች የምንባልበት ትልቅ ተግባር ነው ። የእግዚአብሔር ልጅ የዲያብሎስን ሥራ በደሙ አፍርሷል ። እኛም የእግዚአብሔርን ልጅ መስለን የዲያብሎስን ሥራ ለማፍረስ ሰውን በንስሐ ከፈጣሪው ጋር ፣ በይቅርታ ከጎረቤቱ ማስታረቅ ይገባናል ። ማስታረቅ ግን ጥበብ ይፈልጋል ። በእውቀት ብቻ ማስታረቅ የበለጠ ማጣላትን ይወልዳል ። በማስታረቅ ውስጥ ያዩትንና የሰሙትን በልብ መያዝ ፣ መታዘብን ማራቅ ፣ ታረቁልኝ ብሎ ደግ ደጉን ብቻ ማውራት ይገባል ። ማስታረቅ አንድ ሳለ በስብራት ሁለት የሆነውን አጥንት መጠገን ነውና ጥንቃቄና ጥበብ ይፈልጋል ።

ማጽናናት ሰውን ከሲኦል ጨለማ ወደ ገነት ብርሃን ማምጣት ነው ። ሰይጣን በትካዜያችን ተጠቃሚ ነው ። ሰው ሲተክዝ ችግሩን ያያል ፣ ሲጽናና ግን እግዚአብሔርን ያያል ። ያልተጽናና ሰው ልበ ዕውር ነውና ያለውን ነገር ማየት አይችልም ። ማጽናናት ጥበብ ይፈልጋል ። ጻድቁ ኢዮብ ባልንጀሮቹ ምሁራንና ፈላስፎች ነበሩ ። ጥበብ በማጣታቸው ግን በቍስል ላይ ጥዝጣዜ ጨመሩበት ። አጉል አጽናኝ ኀዘነተኛን ያደክማል ፣ ከፈጣሪው እንዲጣላ ያደርገዋል  ። ዘመናዊ ፈሪሳውያን የሆኑ ሰዎችም ሰው የሚታመመውና የሚያጣው ስላላመነ ፣ የተሰወረ ኃጢአት ስላለበት ነው እያሉ ይናገራሉ ። ይህ የአጽናኝ አቁሳይ የሚወለድበት አስተሳሰብ ነው ። ገና የሚሞት ሥጋ ተሸክመው ስለ መታመም ይደነቃሉ ፣ ዕርቃናቸውን መቃብር ሊወርዱ ተራ እየጠበቁ ስለ ዕለት እጦት ይገረማሉ ። ብቻ ማጽናናት በእውቀት ብቻ ሳይሆን በጥበብም ነው ።

የሰውን የስሜት ሕዋሳት በመግዛት ዓለም ትውልድን ይዛለች ። ስብከት ብቻውን አያስተምርምና ቤተ ክርስቲያን የስሜት ሕዋሳትን ሁሉ የሚገዙ ማስተማሪዎችን አድርጋለች ። ይህ ጥበብ ነው ። ዓይን ቅዱሳን ሥዕላትን ያያል ፣ ጆሮ ዝማሬ ያደምጣል ፣ አፍንጫ ዕጣን ያሸታል … ። ጥበብ ለወንጌል ሥራ አስፈላጊ ነው ። መዳናችንም በጥበብ ነው ። “እግዚአብሔር ዓለምን ከፈጠረበት ጥበቡ ፣ ሰው ሁኖ ዓለምን ያዳነበት ጥበቡ ይበልጣል” እንዲሉ ።

ጌታ ሆይ እውቀትን ከጥበብ ጋር አድለን!

የብርሃን ጠብታ 5

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ነሐሴ 30 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም