የትምህርቱ ርዕስ | ጾመ እግዚእ /3/

“ዲያብሎስም፡- የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንህ ፥ ይህን ድንጋይ፡- እንጀራ ሁን ብለህ እዘዝ አለው።” ሉቃ. 4፡3 ።
ጌታችን አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ጹሞ ከፈጸመ በኋላ ዲያብሎስ ለፈተና መጣ ። ዲያብሎስ የእግዚአብሔርና የመልካም ነገር ተቃዋሚ ነው ። ሰዎች በእግዚአብሔር ላይ ያላቸውን እምነት እንዲጠራጠሩ ያደርጋል ። ጥርጣሬና ፍርሃትን ካልዘራ ሰዎችን ባሪያ ማድረግ አይችልም ። ሰዎች የተደገፉትን እግዚአብሔር ሲጥሉ እንደሚወድቁ ያውቃል ። ዲያብሎስ መፈተኑ በራሱ የአቅሙን አናሳነት ያሳያል ። ማስገደድ አይችልም ማለት ነው ። ዲያብሎስ በአርባ ቀንና በአርባ ሌሊት ጾም ጸሎት ወደ ጌታ የሚቀርብበት ምክንያት አላገኘም ። ጌታችን እንደ ተራበ ባየ ጊዜ ግን ቀረበ ። ዲያብሎስ ጉድለት እየፈለገ የሚቀርብ ነው ። በጉድለቱ አማካይነት እግዚአብሔርን ለማማት ይሞክራል ። ወደ ሔዋን በቀረበ ጊዜ እንዳይበሉ የተከለከሉትን ነገር በመጠየቅ ንግግሩን ጀመረ ። ጉድለት ላይ ብቻ ስናተኩር የዲያብሎስ ፈተና ውስጥ ገብተናል ማለት ነው ። ያለንን ስንቆጥር ደግሞ የእግዚአብሔር መንፈስ እየረዳን ነው ማለት ነው ። መራብ ምኞትን ሊገልጽልን ይችላል ። በምንመኛቸው ነገሮች ላይ ብዙ ፈተናዎች ይነሣሉ ። ምኞት ጥቁሩን ነጭ ፣ ነጩንም ጥቁር አድርጎ ያሳያል ። ምኞት በጊዜ የተለካውን የዓለም ሥርዓት ያፈርሳል ። አሁን ካልሆነ ይላል ። ዲያብሎስ በምኞታችን በኩል በብርቱ ይዋጋናል ። አንድን ነገር በጣም ስንፈልገው በጣም መተው አለብን ። ምክንያቱም ቢመጣም ሰላማችንን ይነሣናል ። እምነታችንን ይወስድብናል ። በዓለም ላይ የሚበረክተው ጣል ፣ ጣል ያደረጉት ነገር ነው ። በአንድ ነገር ላይ ያለን ቅዱስ ጭካኔ የዚያን ነገር ዕድሜ ያረዝመዋል ። “ያለ ምንምና ያለ ማንም እኖራለሁ ፣ ያለ ጌታዬ ግን አልኖርም” ብለን ስናስብ ውስጣችን ይጠገናል ። የፈተናም በር ይዘጋል ።
ጌታችን በተራበ ጊዜ ፈታኝ ቀረበ ። ወደ ሔዋን ግን የቀረበው ባለመርካቷ እንጂ በመራቧ አይደለም ። ሔዋን ሳትራብ ታዘዘች ። ድንጋይን ዳቦ ለማድረግ ሞከረች ። ማለትም ከዕፀ በለስ አምላክነትን ፈለገች ። ከዕፀ በለስ አምላክነትን መፈለግ ድንጋይ ዳቦ ይሁን ማለት ነው ። ሰይጣን በሔዋን የለመደውን ወደ ጌታ ይዞ መጣ ። የሰይጣን ቀላልነት ለክፋቱ ተስፋ የማይቆርጥ ብቻ መሆኑ አይደለም ፤ አንድን ሰው በጣለበት መንገድ ሁሉንም እጥላለሁ ብሎ ማሰቡ ነው ። በመደጋገም አንድ ድምፅ በማሰማት ድምፁን ከባዕድነት ወደ ዘመድነት ያመጣዋል ። በዚህም ብዙዎችን ሲጥል ኑሯል ። ጌታችን ተአምራት በማድረግ ረሀቡን እንዲያስታግሥ እየመከረው ነው ። አዎ ጌታችን አምስት እንጀራና ሁለት ዓሣ አበርክቶ መግቧል ። አሁንም ተአምራትን ለራሱ ረሀብ ቢያውለው ተገቢ አይደለም ወይ ? ብለን እንጠይቅ ይሆናል ። ተአምራት ግን ሌሎችን ለመርዳት እንጂ ለራስ ጥቅም የማይውል መሆኑን ለማስተማር ጌታ እሺ አላለም ። ተአምራት የራስ ዝና መገንቢያ ፣ ገንዘብ መሰብሰቢያ አይደለም ። በከንቱ የተቀበሉትን በከንቱ ለመስጠት ፣ ብዙ ተአምራት ካደረጉ በኋላ “እኔ የማልጠቅም ባሪያ ነኝ” ብሎ መሰወርን የሚጠይቅ ነው ። ዛሬ እንደምናየው ሰይጣንን ቃለ መጠይቅ እያደረጉ በምስል ለዓለም እንደሚያሰራጩ ሰዎች ጌታ አላደረገም ። ተአምራት የማድረግ ጸጋ ቢኖረኝ እኔ ጋ የተቀመጠ ለሰው የማደርሰው አደራ ማለት ነው ። አደራውን በቪድዮ የሚያስቀርጽ ሰው ለአደራ የሚበቃም አይደለም ። ራሱን ተጠራጥሯል ማለት ነው ። እግዚአብሔርን ይህን አደረገ እያሉ ማስታወቂያ የሚሠሩ እንደሚያደርግ ቀድሞም ይጠራጠሩ ነበር ማለት ነው ።ይህች ቀንም ተአምር መሆኗን አላወቁም ።
ጌታችን የዲያብሎስን ምክር ቢሰማና ድንጋይን ዳቦ ቢያደርግ ኑሮ ሰይጣን በእኔ ምክር ነው ይህን ያደረገው ፣ እኔ የአምላክ አማካሪ ነኝ ይል ነበር ። የሰይጣንን አሳቡን አንስተውም የተባለው ለዚህ ነው ። ሰይጣን ክፋቱን የሚፈጽመው በደግነት ድምፅ ውስጥ ነው ። ሔዋንን ሲጠይቃት በአሳቢነት ድምፅ ነው የጠየቃት ። ለጌታችንም በረሀቡ ያዘነ ይመስላል ። ያዘነማ አያማክርም ዳቦ ይዞ ይመጣል ። ሰይጣን አይሰጥም ፣ ግን ይህ የለህም እያለ አእምሮን ይበጠብጣል ።
“ዲያብሎስም፡- የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንህ ፥ ይህን ድንጋይ፡- እንጀራ ሁን ብለህ እዘዝ አለው።” ሉቃ. 4፡3 ።
የዲያብሎስን ንግግር ልብ በሉ ። ማር የተቀባ መርዝ ነው ። ሰይጣን ግማሽ ደግ ነው ። ሙሉ ክፉ ቢሆን ኑሮ ሁሉ ያውቅበትና ይርቀው ነበር ። ወደ ሔዋን የመጣው በእባብ ሥጋ ተሰውሮ እንጂ እውነተኛ መልኩን ይዞ አይደለም ። ጌታችንን እያለው ያለው “የእግዚአብሔር ልጅ ሁነህ እንዴት ትራባለህ ?” ነው ። ዛሬም እግዚአብሔርን እያመንሁ ይህ ችግር እንዴት ወደ እኔ መጣ የሚል ፈተና ብዙ ሰውን እየናጠ ነው ። አንዳንዶችም እምነት ማለት ፉከራ መስሏቸው፡- “የንጉሥ ልጅ ምን ይሆናል ?” ይላሉ ። የንጉሥ ልጅ ጳውሎስ ግን በረሀብ ፣ በእርዛት ፣ በእስራት ፣ በግርፋት ፣ በመጨረሻም በሰይፍ ውስጥ አልፏል ። ዛሬ የአፍሪካ ወንጌል ተብለው የሚጠሩ ትምህርቶች “ታገኛለህ” ፣ “ትፈወሳለህ” የሚሉ ናቸው ። ታገኛለህ የሚለው የድሀን ጆሮ እንጂ የባለጠጋ አገሮችን ጆሮ አይከፍትም ። ስለዚህ ይህ ወንጌል የአፍሪካ ወንጌል ነው ። ሰዎች ታገኛላችሁ ተብለው ተሰብከው ሲያጡ በመጨረሻ፡- “እምነት ውሸት” ነው ይላሉ ። ሰይጣን በረጅም አቅዶ እየሠራ ነውና መጠንቀቅ ይገባል ። ይህንን የሚሰብኩ ጤነኞች ናቸው ። ምክንያቱም አመጋገባቸው ፣ ስፖርታቸው የተጠበቀ ነው ። ደግሞም በሰው የሚያላግጥ አይታመምም ። የሚጨነቅ ነው የሚታመመው ።
የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን ሰይጣን እንዴት አወቀ ? በዮርዳኖስ ከአርባ ቀን በፊት እግዚአብሔር አብ፡- “የምወደው ልጄ ይህ ነው” ብሎ ሲመሰክርለት ሰምቷል ። የሰማውን ግን ለጥርጥር ተጠቀመበት ። ሰይጣን የራሱ መጽሐፍ ስለሌለው እውነተኛውን ቃል በማጣመም አሳቡን ያስፈጽማል ። ጌታችን ድንጋይን ዳቦ ማድረግ ይችላል ። ነገር ግን ራሱን ለመርዳት ብሎ ተአምር አድርጎ አያውቅም ። ተአምር ለሰዎች ካደረገ በኋላም ብዙ ጊዜ አትናገሩ ይል ነበር ። በእግዚአብሔር መንግሥት ከተአምራት ይልቅ የእግዚአብሔር ፍቅርና የዘላለም ሕይወት ዋጋ አለው ።
ጌታችን በመራቡ ፍጹም ሰው መሆኑ ታወቀ ። የእግዚአብሔር ልጅ በመባሉ ደግሞ ፍጹም አምላክ መሆኑን ተረዳን ። ሰው ሁኗልና ተራበ ። እርሱ ሰው ሁኖ ከተራበና ከታመመ ፣ እኛም ሰው ስለሆንን በችግር ውስጥ እናልፋለን ። ችግር ሰው የመሆን ጉዳይ እንጂ የመንፈሳዊነት ጉድለት አይደለም ። መንፈሳዊነት ሰውነትን ይቀድሳል እንጂ አያስቀርም ። ያለ ኃጢአት እንድንሆን እንጂ ያለ ችግር እንድንሆን አልተጠራንም ። ችግር ባይኖር ብልሃት አይኖርም ነበር ። በረዶ ባይኖር ፈረንጆቹ ማሞቂያ አይሠሩም ነበር ። ዕድገት ተግዳሮት ዋዜማው ነው ። ያለ ችግር መሆን በራሱ ችግር ነው ። ጌታ በሥጋ ታሞ መታመም አይገባኝም ማለት አስደናቂ ትዕቢት ነው ። ፈውሰኝ ማለት ግን ትሕትና ነው ።
የሰይጣንን አሳቡን እንዳንስተው መንፈሳዊ ዓይናችንን ያብራልን !!
ይቀጥላል
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም