የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ሁሉ ካንተ ነው

“ሁሉ ከአንተ ዘንድ ነውና ፥ ከእጅህም የተቀበልነውን ሰጥተንሃልና ይህን ያህል ችለን ልናቀርብልህ እኔ ማን ነኝ ? ሕዝቤስ ማን ነው ?” 1ዜና. 29 ፡ 14 ።

ጌታ ሆይ ! ሁሉ በአንተ ፣ ሁሉ ከአንተ ፣ ሁሉ ለአንተ ነው ። ያላንተ ፈቃድ የሆነ ፣ ያላንተ ፈጣሪነት የተገኘ ፣ ካንተ በቀርም ክብሩን ሊወስድ የሚከጅል ማንም የለም ። ሁሉ ባንተ ነው ፣ የመሠረቶች መሠረት ነህ ፤ በውጥኖች ሁሉ ያንተ ውጥን ከሌለበት የአሳብ ቤት ሁኖ ይቀራል ። ባንተ አሳብና ባንተ ድርጊት መካከል ልዩነት የለም ። ያሰብከውን ታደርጋለህ ፣ ያደረከውንም አስበሃል ። ሁሉ ከአንተ ነው ፣ ነገርን ውብ አድርገህ ፣ አስማምተህ ፣ ለሥርዓት አስገዝተህ የምትሠራው አንተ ብቻ ነህ ። ሁሉ ላንተ ነው ፣ ሁሉን አድርገህልን ተመስገን ብቻ በሉኝ ያልከው አንተ ነህ ። ምስጋናችን የውለታህ ክፍያ ሳይሆን መታሰቢያ ነው ።

ዘመናዊው ልባችን ሁሉ በእኔ ፣ ሁሉ ከእኔ ፣ ሁሉ ለእኔ እያለ ሸፍቶብናል ። ሁሉ በእኔ ብለን በጭንቀት አምጠናል ፣ ሁሉ ከእኔ ብለን የካብን መስሎን ንደናል ፣ ሁሉ ለእኔ ብለንም ራሳችንን ማስመለክ ዳድቶናል ። ሁሉ በእኔ ብለን አሳብ የማንቀበል ሆነናል ። ሁሉ ከእኔ ብለን እኔ ያልሠራሁት አይጣፍጥም ብለናል ። ሁሉ ለእኔ ብለን በቁማችን ሐውልታችንን ሠርተን አስመርቀናል ። ሁሉ በእኔ ብለን ፈቃድህን ጥሰን ሄደናል ። ሁሉ ከእኔ ብለን የፈጠርከውን ሳይሆን የፈጠርነውን ከጅለናል ። ሁሉ ለእኔ ብለን ለራሳችን መልክዕና ውዳሴ ደርሰናል ። አቤቱ ልዑል ሆይ ሁሉ ባንተ ነው ። ነፍሴን ሳልረዳት ያወቅኸኝ አንተ ነህ ። አቤቱ አዶናይ ሁሉ ከአንተ ነው ። እጄ የሠራልኝ ፣ ሰዎች የቆረሱልኝ የመሰለኝ ነገር ያንተ ጸጋ ነው ። ኤልሻዳይ ሆይ ሁሉ ለአንተ ነው ፣ ለምስጋና መስነፌ ከንቱነቴ ነው ።

እረኛ ብሆን ንጉሥ ፣ በዱር ብኖር በቤተ መንግሥት እኔ እንጂ አንተ አትለወጥም ። እጄ ዘገነልኝ ፣ ክንዴ መከተልኝ ብዬ ራሴን አላታልልም ። ከብሬ የምበቀል ፣ አግኝቼ ሰውን የማዋርድ ብላሽ ነኝና አቤቱ ይቅር በለኝ ። ሁሉ ካንተ ነው ። ቤቴን ብሠራ ፣ ቤትህን ብሠራ የሠራኸው አንተ ነህ ። ለመወለድ አቅም ያልነበረኝ ለመኖር አቅም የለኝም ። ባንተ አሳብ ተፈጥሬ በራሴ አሳብ የምሳከር ነኝ ። ሁሉ ካንተ ነውና ዳኛ በደለኝ ፣ ባለጠጋ ነፈገኝ ፣ ንጉሥ ፈረደብኝ ብዬ አላዝንም ። ሁሉ ከአንተ ነው ። ዘመድ አላለቀሰልኝም ፣ ጓደኛ አልሳቀልኝም ብዬ በሸለቆና በተራራው አላጉረመርምም ። አጥቶም አግኝቶም መከፋት ከእኔ ይራቅ ። አጥቼ ዝም አሉኝ ብዬ ሰዎችን መኰነን ፣ አግኝቼ አልሳቁም ብዬ በሰው መደነቅ ከእኔ ይራቅ ። ሁሉ ካንተ ነውና ሁሉም ምስጋና ላንተ ይሁን ። የኀዘኔ ደራሽ አንተ ነህ ፣ የእልልታዬ አጋርም አንተ ነህ ። ሲከፋኝም ስደሰትም ያንተው ዕዳ ነኝ ።

በምድር ላይ ላንተ እንደ መስጠት የሚያስደስት ምንም ነገር የለም ። አባት ለልጁ ሰጥቶ ስጠኝ ይለዋል ። ሰጥተኸኝ ስጥ ያልከኝ አንተ አባቴ ነህ ። ቤትህን ለመሥራት ልበ አምላክ ዳዊት እንኳ ፈቃድ አላገኘም ። ያንተን ቤት መሥራት ፣ ሰብኮ ማሳመን ፣ አምልኮ ማስመለክ ዕድል ነው ። እኔ ባልሠራውም ለሚሠራው ድካሙን እንዳቀልለት እርዳኝ ። እኔ ካልሠራሁት ድርግም ይበል ማለትን ከእኔ አርቅ ። በማልኖርበት ዘመንም ያንተ ሥራ ይሠራ ። እነዚያ ባዶ እጆቼ ፣ ድቃቂ ሳንቲም የነጠፉ መዳፎቼ ዛሬ በረከት ካገኙ ያንተን ላንተ እሰጣለሁ ። ሁሉ ካንተ ነውና ለመስጠት ልቡን ፣ ለመቸር አቅሙን ለሰጠኸኝ ምስጋና እንዳቀርብ እመኛለሁ ። ሳትቆጥር ሰጥተኸኝ ሳለ ቆጥሬ እንዳልሰጥህ እርዳኝ ። ሊሰጥህ ከጅሎ እጁ ላጠረበት በረከት አፍስስለት ። ሰጥተኸው ሳለ ሰይጣን እጁን ለቆለፈበት አርነት አውጅለት ።

በምስጋና የተፈራህ ፣ ተወደህ የምትከበር ፣ ተፈቅረህ የምትመለክ አንተ እግዚአብሔር ነህና ምስጋና ለታላቅነትህ ይሁን !!!!
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ግንቦት 24 ቀን 2015 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ