የትምህርቱ ርዕስ | ለማስተማር የሚበቃ

“እንግዲህ ኤጲስ ቆጶስ እንዲህ ሊሆን ይገባዋል ፤ … ለማስተማር የሚበቃ” 1ጢሞ. 3 ፡ 2
ፀሐይ ስትጠልቅ ሁሉም ወደ ቤቱ ይሰበሰባል ፤ ፀሐይ ስትወጣ ሁሉም ወደ ተግባሩ ይሰማራል ። ብርሃን የመውጣት ድፍረት ነውና ። ብርሃን የዓይን ዋጋ ነው ። ብርሃን ራስን መመልከቻ ነው ። ብርሃን ሌላውን የምናይበት ነው ። ብርሃን ውበትን ማድነቂያ ነው ። ብርሃን መገናኛ ነው ፤ ብርሃን ማታ የተሰነባበተ ጠዋት “እንዴት አደርህ ?” የሚባባልበት ነው ። ብርሃን ነጻ ስጦታ ነው ። ብርሃን ተስፋ ሰጪ ነው ። ብርሃን መንገድን መመልከቻ ነው ። ብርሃን እግርን ከገደል የሚያድን ነው ። ብርሃን መታከሚያ ነው ። ብርሃን ማፍቀሪያ ነው ። “ዓይን ነው ዘመዱ” እንዲሉ ። ብርሃን የወደቀውን አይቶ ማዘኛ ነው ። ብርሃን አራዊትን የሚገሥጽ ነው ። ብርሃን የፈሩትን የሚያደፋፍር ነው ። ብርሃን ሕመም የጠናባቸውን የሚያስታግሥ ነው ። በሽተኛ ሌሊት ሲብስበት ቀን ይሻለዋልና ። ብርሃን የልብ ድፍረት ነው ። በአጠቃላይ ራሱ እግዚአብሔር ብርሃን ነው ። ነቢዩም፡- በብርሃንህ ብርሃንን እናያለን” ብሏል ። መዝ. 35 ፡ 9 ። በብርሃን ቃልህ ብርሃን ልጅህን/ወልድን/ እናያለን ማለቱ ነው ።

እውቀት ብርሃን ሲሆን ማስተማርም ብርሃን ማብራት ነው ። ብርሃን የሰው ልጆች መሠረታዊ ፍላጎት እየሆነ መጥቷል ። ትምህርትም የሰው ልጆች መሠረታዊ ፍላጎት ነው ። የሚያስተምር ብርሃን የሚያበራ ብቻ ሳይሆን እንደ ገና የሚወልድም ነው ። ፀሐይ ስትጠልቅ ሁሉ እንዲሰበሰብ አላዋቂነት ሲነግሥም አዋቂ ይሸሸጋል ። ፀሐይ ስትወጣ ሁሉ እንዲወጣ እውቀት ዋጋ ሲያገኝ ጨዋዎች ድፍረት ያገኛሉ ። ሴቶች ከማጀት ወደ አደባባይ የሚወጡት በትምህርት ነው ። ብርሃን ድፍረት እንዲሰጥ እውቀትም ድፍረት ይሰጣልና ። ዓይን ያለ ብርሃን ለጌጥ እንኳ እንደማይሆን ፣ እንደ ተፈጠረ ያለ ሰውም ያለ ትምህርት ብቁ አይሆንም ። ብርሃን ራስን መመልከቻ እንደሆነ እውቀትም ያሉበትን አድራሻ የሚያሳውቅ ነው ። ብርሃን ሌላውን እንደሚያሳይ እውቀትም ስለ ሌሎች ማሰብን ይሰጣል ። ብርሃን ውበትን ማድነቂያ እንደሆነ እውቀትም በተፈጥሮ ላይ ያረፈውን የእግዚአብሔርን ጥበብ ያሳያል ። ብርሃን መገናኛ እንደሆነ እውቀትም የተራራቁትን ያቀራርባል ። ብርሃን ነጻ ስጦታ እንደ ሆነ እውቀትም አይሸጥም ። ከዋጋ በላይ ነውና ። ብርሃን ተስፋ ሰጪ ነው ፤ ብርሃን በሚሰወርባቸው ወራት ብዙ ሰዎች ድብርት ውስጥ ይገባሉ ። እውቀትም በዛሬው ነገር እንዳንዳከም ይነግረናል ። ብርሃን መንገድ ማመልከቻ እንደሆነ እውቀትም መድረሻን ያሳያል ። ብርሃን እግርን ከገደል እንዲያድን እውቀትም ከጥፋት ይመልሳል ። ብርሃን መታከሚያ እንደሆነ እውቀትም አስተሳሰብን ይፈውሳል ። ብርሃን ማፍቀሪያ እንደሆነ እውቀትም ከጥላቻ ነጻ ያወጣል ። ብርሃን የወደቀውን አይቶ ማዘኛ እንደሆነ እውቀትም ለተጎዱት መራራትን ይሰጣል ። ብርሃን አራዊትን እንዲገሥጽ ፣ እውቀትም ጨካኞችን ይገሥጻል ። ብርሃን ለፈሪዎች ድፍረት እንዲሰጥ እውቀትም ለምስኪኖች ሞገስ ይሆናል ። ብርሃን ሕመም እንዲያስታግሥ ትምህርትም ከንቱ ጉዳትን ይቀንሳል ። ብርሃን እግዚአብሔር እንደሆነ ሁሉ ልንማረው የሚገባን አምላክ ነው ።
በዚህ ዓለም ላይ ገዳይ መሣሪያ የሠሩ አዋቂዎች አሉ ። ዘረኝነትን ያስፋፉ የተማሩም አልጠፉም ። እውቀት ያልነው ግን እግዚአብሔርን ማወቅ ነው ። የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው እንዲል እግዚአብሔርን መፍራት የጥበብ ሀሁ ነው ። እግዚአብሔርን መፍራት የሌለበት እውቀት ያልተጀመረ እውቀት ነው ። ጨለማን የፈራ ጤነኛ ነው ፤ ብርሃንን የፈራ መታገዝ ያለበት ታማሚ ነው ። አለማወቅን መፍራት ሲገባ እውቀትን መፍራት ግን ሕመም ነው ።
ኤጲስ ቆጶስ ለማስተማር የሚበቃ መሆን አለበት ። ባለ ማወቅ ምክንያት ወደ ራሳቸው በጣም በማየት ተስፋ የቆረጡ ፣ ወደ ሰዎች በጣም በመመልከት ድንጉጥ የሆኑ ብዙ አሉ ። ኤጲስ ቆጶስ ለማስተማር ሲነሣ እነዚህን ምንዱባን ያድናል ። ካሉበት ዓለም ውጭ ሌላ ዓለም አልታይ ብሏቸው የሚኖሩ የኅሊና እስረኞች ፣ እኔ ዋጋ የለኝም ብለው ባርነትን አጣጥመው ለመቀጠል የፈቀዱ ሞኞች ዛሬም አሉ ። ተምረው የደነቆሩ ፣ አውቀው የደነዙ ብዙ ሰዎች በየዕለቱ እየፈሉ ነው ። ከልብስ ዘልቀው ማየት የማይችሉ ፣ ሰውን በቤቱ የሚለኩ ብዙ ሚዛን የለሾች እየተስፋፉ ነው ። ራሳቸውን አጽድቀው ሌላውን የሚኰንኑ ፣ እኔን ብቻ ይድላኝ ብለው ጎረቤታቸውን የሚያውኩ አያሌ ናቸው ። የእኔ የግሌ ፣ የእነ እገሌ የጋራችን ነው ብለው የሚያስቡ ፣ ለእነርሱ የተፈጠረውን ዓለም ማየት ያልቻሉ ፣ በጉዳተኝነት ስሜት የሚያነክሱ ፣ ተጎዳሁ እንጂ ጎዳሁ የማይሉ ፣ የሚያገናኙ ድልድዮችን አፍርሰው የሚለያዩ ግንቦችን የሚሠሩ ፣ መሰናበት እንጂ መገናኘት የማይችሉ ፣ ቆጥበው የማይጣሉ ፣ ገርበብ አድርገው ሳይሆን በር ቆልፈው የሚሄዱ ፣ መመለሻ ድልድያቸውን የሚያፈርሱ የትየለሌ ናቸው ። ነጻ የሆነውን ፍቅር ፣ ነጻ የሆነውን መልካም ቃል ለመስጠት የተቸገሩ ፣ ለክፋት ነቅተው ለደግነት የሚተኙ ፣ ነገ አልታይ ብሏቸው ዛሬ ለመጫረስ የወጡ ፣ አይተው መርገጥ ተስኖአቸው ረግጠው የሚያዩ ፣ ገደል አፋፍ ላይ የሚጨፍሩ ፣ ታስረው የሚዘፍኑ ፣ ምነው የሰው ሁሉ አንገት አንድ በሆነልኝ ብለው በአሳብ የሚፈጁ ፣ ከራሳቸው ጋር ላለመገናኘት መምህራንን የሚጠሉ ብዙ ናቸው ። ኤጲስ ቆጶስ ለማስተማር የሚበቃ መሆን ያለበት እነዚህ ሁሉ ስለሚጠብቁት ነው ። ወታደር ሰይፍ ይይዛል ፣ ካህንም ትምህርት ሊይዝ ይገባዋል ። ያለ መሣሪያ ወታደርነት ፣ ያለ ትምህርት ክህነት ለመሸነፍ ነው ።
“የየጁ ደብተራ ቅኔ ቢያልቅበት ቀረርቶ ሞላበት” እንዲሉ በአደባባይ ስድብ የሚያስጠኑ አስተማሪዎች ትምህርት ያለቀባቸው ናቸው ። አደባባይ መቆም ሥራው የሆነ መናገር ግዴታው ነው ። የሚያስተምረው ከሌለው የሚሳደበው አያጣም ። ለማስተማር የማይበቃ ለመበጥበጥ የሚበቃ ነው ። ወታደርን ወታደር የሚያሰኘው ልብሱ ብቻ አይደለም ፣ ስልጠናውም ነው ። ካህንንም ካህን የሚያሰኘው ማስተማሩ ነው ።
አስተማሪ ፣ ገበሬና ወታደር አገር የሚጠብቁ ናቸው ። አስተማሪ ካለ ማወቅ ፣ ገበሬ ከረሀብ ፣ ወታደር ከወራሪ የሚያድኑ ናቸው ። ወላጅ ልጁን በጠዋቱ አምኖ የሚሰጠው ለአስተማሪ ነው ። አስተማሪ ሁለተኛ ወላጅ ፣ የትውልድ ተንከባካቢ ፣ ብርሃን ገላጭ ፣ የቡሩክ እግዚአብሔር ተንታኝ ነው ። አስተማሪ ፊደል ቀርፆ ፊደል የሚያስጠና ፣ ንባብን ከነትርጓሜ ፣ ትርጓሜን ከዜማና ከቅኔ ጋር የሚያሰርጽ ፣ የነፍስ ምጽዋት የሚሰጥ ደግ ነው ። አይሁዳውያን ልጃቸውን ከሰባት ዓመቱ እስከ አሥራ ሁለት ዓመቱ ለረቢው ወይም ለመምህሩ ይሰጡታል ። ፊደልን ከሕጉ ጋር ተምሮ በአሥራ ሁለት ዓመቱ ሙሉ ሰው ይባላል ። አስተማሪ ሙሉ ሰውን የሚያወጣ ነው ። አሪስቶትል ትምህርት ቤት ደጃፍ ላይ፡- “ልጆቻችሁን አምጧቸው ሰው አድርገን እንመልሳቸዋልን” የሚል ጽሑፍ ይነበብ ነበር ። በኢትዮጵያ ቤተ  ክርስቲያንም ከፊደል እስከ ትርጓሜ ፣ ከዜማ እስከ ቅኔ ትምህርት ይሰጣል ። ዛሬ በገዛ ፊደሏ የሚሰድቧትና የሚጽፉባትን ስናይ ይደንቀናል ። መሳደቢያ ፊደሉንም ያገኙት ከቤተ ክርስቲያን ነው ። ቤተ ክርስቲያን እየጠሏትም እንጀራ ናት ።
ኤጲስ ቆጶስ ለማስተማር የሚበቃ መሆን አለበት ። ሥልጣኑ ያለው ማስተማር ላይ ነውና ። ካላስተማርን ነገ ተከታይ አይኖረንም ። ማስተማር ዘር መዝራት ነው ። ማስተማር የተዘራውን ማሳደግ ነው ። ማስተማር ያደገውን ፍሬ መሰብሰብ ነው ።
ልዑል አምላክ መምህራንን ያብዛልን ።
1ጢሞቴዎስ 39
ጥር 15 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲ.አ.መ.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም