የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

ለምስጋና ተመለሱ

“ኢየሱስም መልሶ፦ አሥሩ አልነጹምን ? ዘጠኙስ ወዴት አሉ ? ከዚህ ከልዩ ወገን በቀር እግዚአብሔርን ሊያከብሩ የተመለሱ አልተገኙም አለ ።” ሉቃ. 17፡17-18 ።
አንዲት እናት በጣም ችግረኛ ናቸው ። አንድ ቀንም እንጀራ ያስፈልጋቸዋል ብሎ ቁራሽ የሰጣቸው ሰው የለም ። እርሳቸው የባሰባቸው ቢሆኑም ከእርሳቸው የተሻሉ ድሆች ሲረዱ ያያሉ ። ቢሆንም የቀድሞ ጥሩ ኑሮአቸው እንቅፋት ሁኖባቸው መለመን አፍረው ተቀምጠዋል ። ታዲያ አንድ ቀን የአጥሩ ኮሽም ፣ እሾህ ያላቸው አበቦች ተቆርጠው ሳለ ለእኒያ ድሀ ውሰዱላቸው ተባለ ። አሳቡ አድርቀው ማገዶ ያደርጉታል ተብሎ ነው ። እሾሁ ግን አላስደርስ ብሏቸው እጃቸውን ደም በደም አደረገው ። እርሳቸውም በቤታቸው ደጃፍ ላይ ተከምሮ ያዩታል ። በዚህ ጊዜ “በእሾሁ እንዳስታወሳችሁኝ በእንጀራውም አስታውሱኝ” ብለው መልእክት ላኩ ። ይህ በእኔ ላይ የደረሰ ታሪክ ነው ። ይህ ንግግራቸው ሕመም ሁኖ ለረጅም ጊዜ በውስጤ ቆየ ። አሁን ግን እርሳቸውም እየተረዱ በመሆናቸው ደስ ይለኛል ።
በእሾሁ እያስታወሱ በእንጀራው አለማስታወስ የሚገርም ነው ። ለማገዶው ያሰብንለት ሰው የሚጋግረው ግን የሌለው መሆኑ በጣም የሚያስደንቅ ነው ። ከእሳቱ ዱቄቱ ይቀድማል ። ዱቄት በሌለበት ማገዶ ምንም አይጠቅምም ። አብዛኛዎቻችን እግዚአብሔርን የምናስታውሰው በእሾሁ ነው ። ስንወጋ ፣ ስንደማ ፣ ስንቆስል እናስበዋለን ። ጸልዩልኝ ብለን እንማጸናለን ። በእንጀራው ግን አናስበውም ። እግዚአብሔርን እሾህ ጎታች ፣ ዓለምን ግን የእንጀራ ወዳጅ አድርገናልና ሊያመን ያስፈልጋል ። ትላንት ራሳቸውን ሊያጠፉ ብለው ቤተ ክርስቲያን የመጡ ሰዎች ያ ጭንቀት ሲያልፍ አገልጋዮቹን በገመድ ካላነቅን ብለው ሲጋበዙ አይተናል ። ትላንት በመራራ ሕይወት ሁሉም ነገር ጨልሞባቸው የነበሩ ያ ቀን ሲያልፍ በእግዚአብሔር ቤት ደጃፍ ለማለፍ እንኳ ተጸይፈዋል ። ትላንት እግዚአብሔርን ብቻ ፈልገው ከዚህ ጉድ ልውጣ ይሉ የነበሩ ዛሬ ሰዎችን እያየን ተሰናከልን ይላሉ ። ሊሄድ ያሰበ ሰበቡ ብዙ ነው ። ለምስጋና ከተመለሰ ቀምቶ የሮጠ ይበዛል ። የዛሬው እርካታ የሁልጊዜ አይሆንምና አሁንም በሌላ እሾህ እግዚአብሔርን ማስታወስ አይቀርም ። እርሱ ግን ማንንም ሳይታዘብ ይቀበላል ።
የለምጽ በሽታ እንደ ዛሬው ያለ የቆዳ በሽታ አልነበረም ። የመጀመሪያ ተላላፊ በሽታ ነው ። ሁለተኛ ከርኩሰት ጋር የተያያዘ ነው ። ለምጽ ያለበት ሰው በካህኑ አዋጅ ራሱን ከሕዝቡ ለይቶ በምድረ በዳ ይኖራል ። ከተፈወሰ ሲመለስ ፣ ካልተፈወሰ በዚያው ይሞታል ። የሚወዳቸው ቤተሰቦቹም ቤዛ ሊሆኑለት አይችሉም ። “ርኩስ ነኝ” ብሎ በራሱ ላይ ያውጃል ፣ ሰው ከቀረበውም እየሮጠ ይሸሻል ። ከባድ ጭንቅ ነው ። ጌታችን በሰማርያ ሲያልፍ አሥር ለምጻሞችን በምድረ በዳ አገኘ ። እነዚህ ለምጻሞች ያገናኛቸው ኑሮ ሳይሆን ችግር ፣ ከተማ ሳይሆን ምድረ በዳ ነው ። ሐኪም ቤትና ጠበል ደግሞም ስደት ያፋቅራል ። ችግሩ ያ ሲያልፍ መረሳሳት ይመጣ ይሆናል ። የችግር ቦታዎች ጥላቻና ራስ ወዳድነት የሚገረዝባቸው የግርዛት ኮረብታዎች ናቸው ። ጌታችንን ባገኙት ጊዜ አልሮጡም ፣ እንደውም እየጮኹ ቀረቡት ። እርሱ የሚያነጻ ነውና ርኩሶችን አይሸሽም ። የሰው ቅድስና ግን ከራሱ አልተርፍ ስትል መሸሽ ይጀምራል ። “ኢየሱስ ሆይ አቤቱ ማረን አሉት ። ማረን ቢበድሉም ባይበድሉም ትልቅና የመጨረሻ ጸሎት ነው ። ቢታመሙም ባይታመሙም ሐኪም ጋ መሄድ መልካም ነው ። ስለ መፈወስ ቢለምኑ አንድ ልመና ነው ። እርሱ ከማራቸው ግን ሁሉም ጸጋ የእነርሱ ነው ። ማረኝ የጸሎት አባ ጠቅል ነው ። ምሕረት ያለውን ጌታ ማረኝ አሉት ። ማረኝ የሚባልም እርሱ ብቻ ነው ። ሰው ይቅር ይላል ፣ መማር ግን የአንድ አምላክ ግብር ነው ። ሰው ይተዉልናል ፣ እግዚአብሔር ግን እንዳልበደለ አድርጎ ይቀበለናል ።
ጌታችን “ራሳችሁን ለካህን አሳዩ” አላቸው ። ለምጻም ናችሁ ብሎ ያረጋገጠውና በአዋጅ የለያቸው ካህኑ ነውና የሚመልሳቸውም ካህኑ ነው ። ፈውሱን ጌታ አደረገና አዋጁን ግን ለባለሥልጣኑ ካህን ተወለት ። እግዚአብሔር ራሱ የሠራውን ሥርዓት ራሱ አያፈርስም ። “እነሆም ሲሄዱ ነጹ” ይላል ። በጣም ድንቅ ነገር ነው ። ከእነርሱም አንዱ እንደ ተፈወሰ ባየ ጊዜ ጌታችንን ሊያመሰግን ወደ ኋላ ተመለሰ ። ሌሎቹ ግን ቤተሰቦቻቸውንና የተለዩትን መንደር ለማግኘት ገሰገሱ ። አንገታቸው ወደፊት እንጂ ወደኋላ ዞር ብሎ የሚያይ አልነበረም ። ይህ አንዱ ሰው በጌታ እግር ላይ ወድቆ ማመስገን ጀመረ ። ያ ሰው ግን የተናቀ ሳምራዊ ነበረ ። ከተናቀው ሰው የከበረ ምስጋናና ውለታ አክባሪነት ወጣ ። በማይጠበቅ ቦታ የማይጠበቅ ግብር ይገኛል ። ዝናብ የሌላቸው ደመናዎች ብዙ አሉ ፣ ይህ ሰው ግን በቀትር የዘነበ ምስጋና አለው ። ድብልቅ ከሚባል ሕዝብ የጠራ ምስጋና ወጣ ። ወገኑ ሳምራዊ ሳለ እንዴት አብሯቸው ከረመ ብንል የከፋ ችግር የሚያንሰውን ዘረኝነት አስረስቷቸው ነው ። በዘረኝነት የሰከሩ የባሰ ችግር ሲመጣ ይረሱታል ። “እዬዬ ሲዳላ ነው” ይባላል ። ሰው በጦርነት መሐል ልቅሶ አይቀመጥም ። ተደላድሎ ሲቀመጥ ግን ስለሞተው ወንድሙ ማልቀስ ይጀምራል ። ካልበሉ እንባም አይመጣም ።
“ኢየሱስም መልሶ፦ አሥሩ አልነጹምን ? ዘጠኙስ ወዴት አሉ ? ከዚህ ከልዩ ወገን በቀር እግዚአብሔርን ሊያከብሩ የተመለሱ አልተገኙም አለ ።” ለምስጋና የሚመለስ ከአሥር አንድ መሆኑ ይገርማል ። ዘጠኙ ተፈውሰዋል ውለታው የነካው ግን አንዱ ነው ። ዛሬም ከአሥሩ አንዱ ብቻ ለምስጋና ይመለሳል ። እነዚያ ዘጠኙ የገሰገሱት ግን ወደሚያልፉት ወዳጆቻቸው ነው ።ደግሞም ርኩስ ብላ ወደ ገፋቻቸው ዓለም ነው ። ዛሬም ሰዎች ሲፈወሱ ወዳወገዘቻቸው ዓለም ይመለሳሉ ። ለምስጋና የሚመለሱ ጥቂቶች ናቸው ። የሚበዛው የምስጋና ዕዳ ያለበት ነው ። ወዳጆቼ ትልቁ በደል የእግዚአብሔርን ውለታ መርሳት ነው ።
መቃብራችሁ የተደፈነላችሁ ፣ ከጫካ ሕይወት ወጥታችሁ ከሰው ቊጥር የተደመራችሁ ፣ የክረምትን ያህል በእንባ የታጠባችሁ ፣ ከሩቅ አገር ወደ ክርስቶስ የመጣችሁ ፣ … ለምስጋና ተመለሱ ። ፈውስም ማግኘትም ዘላለማዊ አይደሉም ። ዘላለማዊ እግዚአብሔር ብቻ ነው ።
እግዚአብሔር ጌታዬ ሆይ አመሰግንሃለሁ ። ለጸሎት ብዙ ቃል አለኝ ለምስጋና ግን ምንም ቃል የለኝም ። እያደረግህልኝ የምታደርግልኝ ሌላ ነገር ይታየኛል ። ለምስጋና ቆም እንድል እባክህ እርዳኝ ። ለማያጠግብ እንጀራ ስንት ዘመን መለስ ቀለስ አልኩኝ ። ላይሞላ ኑሮ ጀርባዬን ሰጠሁህ ። በበረከትህ ተመዝኜ እንዳልወድቅ እባክህ እርዳኝ ። ሌላውስ አጥቶ ካደህ ፣ እኔ አግኝቼ እንዳልክድህ ፣ እግዚአብሔር ማነው ? እንዳልልህ ልቡናዬን ጠብቅልኝ ። ፈጥሮ በማይጥለው አባትነትህ ለዘላለሙ አሜን ።
የዕለቱ መና 12
ግንቦት 11 ቀን 2011 ዓ.ም.
ዲአመ ተጻፈ አዲስ አበባ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ