መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የዕለት መና » ለእኛም እዘንልን

የትምህርቱ ርዕስ | ለእኛም እዘንልን

“ብዙ ሕዝብም ባየ ጊዜ ፥ እረኛ እንደ ሌላቸው በጎች ተጨንቀው ተጥለውም ነበርና አዘነላቸው ።” ማቴ. 9፡36 ።
ጌታችን ይህን ቃል በሚናገርበት ጊዜ ጲላጦስና ሄሮድስ የሮማን መንግሥት ወክለው የሕዝቡ መሪ ነበሩ ። የሕዝቡ መንፈሳዊ ራስ ነን የሚሉ ካህናትና ሊቃነ ካህናት በመብዛታቸው በተራ ያስተዳድሩ ነበር ። የእግዚአብሔር ቤት ጠባቂ ነን የሚሉ አእላፋት ሌዋውያን የዘር ተዋረዳቸውን ጠብቀው አደግድገው ቆመዋል ። ከቤተ ክህነት ሥልጣን አንፈልግም ነገር ግን የአገርና የሃይማኖት ነገር ያሳስበናል የሚሉ ፈሪሳውያን በዘርፋፋውና በደማቁ ልብሳቸው ከተማውን ሞልተዋል ። ሰዱቃውያንም ሃይማኖትን ከምቾት ጋር መያዝ አለብን ብለው በሀብትና በባለሥልጣኖች ዘንድ ሞገስ በማግኘት ተደስተዋል ። ይህን ሁሉ አናይም ብለው ደግሞ የመነኑ በኩምራን ዋሻዎች ተደብቀው ቅዱሳት መጻሕፍትን በመገልበጥ ሥራ የተሰማሩ ኤሴያውያን  የሚባሉ ወገኖችም ነበሩ ። ጌታ ግን ሕዝቡ እረኛ የለውም በማለት ተናገረ ። ቊጥራቸው ስድስት ሺህ የሚያህሉ ፈሪሳውያን ምኩራባቱን ተቆጣጥረው በየመንደሩ ያለውን አገልግሎት በእጃቸው አስገብተው ነበር ። ሰዱቃውያን ደግሞ ቤተ መቅደሱን ያስተዳድሩ ነበር ። የእኔ አስተሳሰብና ሃይማኖት ይልቃል እያሉ ፈሪሳውያንና ሰዱቃውያን ይጣላሉ ። ለሕዝቡ የሚበጀውን የማሳየው እኔ ነኝ እያሉ የሃይማኖት ቡድኖች ይደባደባሉ ። ጌታ ግን ሕዝቡ እረኛ የለውም እያለ ነው ።
ጌታችን እረኛ አለመኖሩን የተናገረው ሕዝቡን እንጂ እረኞችን አይቶ አልነበረም ። ሕዝቡን በማየት እረኛ መኖር አለመኖሩን ማወቅ እንደሚቻል እያሳየን ነው ። ራስ ምታት የአንድ ሕመም ማሳያ መገለጫ ነው ሲባል እንሰማለን ። የመሪዎች መገለጫም ሕዝቡ ነው ። ሕዝቡ ብዙ ነው ፣ እረኛ ግን አልነበረውም ። የቊጥር አለመመጣጠን ሳይሆን የእረኝነት ልብ ያለው አልነበረም ። የከረሩ የሃይማኖት ክርክሮች ፣ ጠንካራ የሆኑ ስብከቶች ሊካሄዱ ይችላሉ ። ሕዝቡ ግን እረኛ አልነበረውም ። ሃይማኖትን በዕብራይስጥ ፣ በግሪክ ፣ በላቲን ፣ በሱርስት ቋንቋ የሚተረጉሙ ነገር ግን ሕዝቡን ማሰማራት ያልቻሉ እረኞች ነበሩ ማለት ነው ።
ሕዝቡ በመንደርም በምኩራብም ፣ በጲላጦስም በቀያፋም ኀዘነተኛ ነበረ ። ከቤተ መንግሥቱ ባይደላው የሚጽናናበት መንፈሳዊ እረኛ አልነበረውም ። ለሥጋው አድሮ ነፍሱን በደለ እንዳይባል ረሀብተኛ ነው ፤ ለነፍሱ አድሮ ሥጋውን በደለ እንዳይባል በክፋት የተያዘ ነው ። ጌታ እረኛ እንደሌላቸው አየ ። እረኛ የሌለው ሕዝብ ምልክቱ መጨነቅና መጣል ነው ። መጨነቅ ነገሮች አጋንኖ ማየት ነው ። ነገሮችን ያለ እግዚአብሔር ማየት እርሱ መጨነቅ ነው ። መጨነቅ ወደ ጎረቤት እንጂ ወደ እግዚአብሔር መጮህ አለመቻል ነው ። መጨነቅ የታወቁና ያልታወቁ በሽታዎች መነሻ ነው ። መጨነቅ ምግብ የሚዘጋ ወይንም ብዙ ምግብ የሚያስበላ ነው ። መጨነቅ በውስጡ ቀጥሎ እንዲህ ቢሆንስ የሚል ስጋት ያለው ነው ። የሚገልጥለት አጥቶ የሚያጋልጠው አገልጋይ ያተረፈ ሕዝብ የተጨነቀ ነው ። የተንሸራተተበትን ቦታ ትቶ የወደቀበትን ቦታ የሚያሳየው እረኛ ያለው ሕዝብ የተጨነቀ ነው ። ራሱን የሚያሰማራና ሕዝቡ ምን ይሆናል ? ሳይሆን እኔ ምን እሆናለሁ ? የሚል መሪ ያለው ሕዝብ የተጨነቀ ነው ። ጌታችን ሕዝቡ እረኛ የለውም እያለ ነው ። እረኝነት ጸጋ ነው ። እረኝነት ለአንዳንዶች የሚሰጥ ጸጋ ነው ። እረኝነት በዙር የሚደርስ የደቦ ሥራ አይደለም ። እረኝነት በተራ እንብላ የሚባልበት የጅብ ሰርግ አይደለም ።
የተጣለ ሕዝብ ፈላጊ ያጣ ሕዝብ ነው ። ከውጤቱ ይማር ተብሎ የተተወ ወገን ነው ። ለትልቁም ለትንሹም ትምህርት ሕይወቱን አስይዞ የሚማር ነው ። ገንዘቡ እንጂ እርሱ የማይፈለግ ነው ። “የትም ፍጪው ዱቄቱን አምጪው” የሚሉ እረኞች ሲነሡ ሕዝብ የተጣለ ይሆናል ። ሕዝቡን ሳይሆን ሥልጣናቸውን የሚጠብቁ መሪዎች የገጠመው ሕዝብ የተጣለ ይሆናል ። ሲያመሽ የት አመሸህ ? የማይባል ተስፋ የተቆረጠበት ፣ ሞቶ የሚኖር ሕዝብ እረኛ የሌለው ሕዝብ ነው ። በነውርና በጭካኔ የሚወዳደር ሰብሳቢ ያጣ ሕዝብ ነው ። ያ ሕዝብ ክርስቶስ ሲያስተምረው የሚቆጡ ፣ በጭንቀት ሲወድቅ ግን የማያስቡለት መሪዎች ገጥመውት ነበር ። ስለዚህ ጌታ አዘነላቸው ። በሥጋም በነፍስም እረኛ ያጣ ሕዝብ ነበርና አለቀሰላቸው ። ይህ ርኅራኄውን ያሳያል ።
እረኛ ያጡ በጎች የመጡበትን አስታውሰው ለመመለስ አይችሉም ። በየተራራውና በየዋሻው ይመሽባቸዋል ። የአራዊትን ድምፅ ሲሰሙ የሞት ጥላ ይጫናቸዋል ። ስለዚህ ይፈራሉ ፣ ይጨነቃሉ ። ሰዎች ወደ እግዚአብሔር ቤት በመጡበት ፍጥነት የሚመለሱት እረኛ ካጡ ነው ። እንደ እረኛ የሚያሰማራ ፣ ማልዶ የሚፈልግ ፣ ከፊት ቀደሞ የሚወጣ ፣ ለምለም መስክ ላይ የሚያሰማራ ፣ ከጥሩ ውኃ አጠገብ የሚመራ ፣ ሲመሽ የሚሰበስብ ፣ ሲቆስሉ የሚያክም ፣ ሲደክሙ የሚሸከም ፣ አደራ አለብኝ ብሎ በቅዱስ ፍርሃት የሚጠብቅ እረኛ ያስፈልጋል ።
አዎ እረኛ የለም ብሎ የበሸቀው ሕዝብ ከጌታ ቃል በኋላ በእረኝነት ወንበር ላይ በተቀመጡት እንዳይነሣሣ ጌታችን በመቀጠል ተናገረ፡- በዚያን ጊዜ ደቀ መዛሙርቱን፡- መከሩስ ብዙ ነው ፥ ሠራተኞች ግን ጥቂቶች ናቸው፤ እንግዲህ የመከሩን ጌታ ወደ መከሩ ሠራተኞች እንዲልክ ለምኑት አላቸው ።” እረኛን የሚሰጥ እግዚአብሔር ነው ። ነገር ግን ምእመናን መጸለይ አለባቸው ። ሲጸልዩ እረኞች ይሰጡአቸዋል ። እረኞች ሲገኙም ምእመናን መጋቢና ተቆርቋሪ ያገኛሉና ከጭንቀትና ከተስፋ መቊረጥ ይድናሉ ።
ጌታችን ደቀ መዛሙርቱን ጸልዩ ካለ በኋላ በማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 10 ላይ ወደዚህ ሕዝብ ላካቸው ። ጌታ ማንን ልላክ ? ሲል ነቢዩ ኢሳይያስ እኔን ላከኝ እንዳለ ደቀ መዛሙርቱም እንዲጸልዩ ከታዘዙ በኋላ ለአገልግሎት ተሰማሩ ። እግዚአብሔር ሰውን እንዲጠቁሙለት አይፈልግም ፣ አሟልተህ እኔን ላከኝ እንዲሉት ይፈልጋል ። ተግባር የሌለው ጸሎት አያርግምና ። የእኛን ድርሻ በቅጡ ከተወጣን እግዚአብሔር ማድረግ ያለበትን ያለ አሳሳቢ ያደርጋል ።
በአገራችን በኢትዮጵያ በቅርቡ በምንሰማው ጥናት ሃያ ሰባት በመቶ የሚሆን ሕዝብ በአእምሮ ጭንቀት የተያዘ ነው ። ይህ ማለት ከመቶ ሚሊየን ሕዝብ ሃያ ሰባት ሚሊየን ሕዝብ በጭንቀት ይሰቃያል ማለት ነው ። ይህ ወደ ሐኪም ቤት የሄደው ቊጥር ይመስላል ። ከዚህም ሊልቅ ይችላል ። የዚህ ችግር እረኞች መታጣታቸው ነው ። ሕዝቡ የተጣለ ነው ። ሲሞት እንኳ የሚጮህለት የለውም ። የሚሞተው ሰው እኮ ነገ ሠርቶ አሥራት የሚያመጣ መሆኑን አሥራት ሰብሳቢዎች እንኳ መረዳት አልቻሉም ። ብዙ ትዳሮች ይፈርሳሉ ። ሊያስታርቅ የሚደክም ግን እየጠፋ ነው ። ወጣቶች በአደንዛዥ ዕፅ ተይዘው ይሰቃያሉ ። ራርቶ የሚያክማቸው እረኛ ግን አላገኙም ። መጠጥ ቤቶች ሙሉ ናቸው ፣ ይህ ሁሉ ሕዝብ ግን ቀበጥ ስለሆነ ብቻ አይደለም ፤ ሰብሳቢ ስላጣም ነው ። ወደ እግዚአብሔር ቤት የሚመጡትን የቡድናችንና የጠባችን አባል እንጂ የክርስቶስ ወገን አላደረግናቸውም ። በእያንዳንዱ ቀን ሰው ይወድቃል ፤ ይህ ሁሉ እኛ ወንጌልን ስላላስተማርን ነው ብሎ ራሱን ያየ ግን እየጠፋ ነው ።
በዚያው መጠን ምእመናን መዳፈርና ሥልጣን ያላቸውን ማዋረድ እንጂ መጸለይ አልቻሉም ። የሚጸልይ ሲቀበል ፣ የሚሳደብ ግን ያንን የቀረውን ጥቂት ነገርም እያጣ ይመጣል ። ጌታ ግን ዛሬም ያዝናል ። በእኛ ልብ ሁኖ ለተጨነቀውና ለተጣለው ሕዝብ ማዘን ይፈልጋል ። ለሕዝቡ እንዘንለት ።
የዕለት መና /3/
ግንቦት 2 ቀን 2011 ዓ.ም.
ዲአመ ተጻፈ በአዲስ አበባ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም