መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የዕለት መና » መልካም ምኞት ትንቢት አይደለም

የትምህርቱ ርዕስ | መልካም ምኞት ትንቢት አይደለም

 “የእስራኤልም አምላክ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላልና፡- በመካከላችሁ ያሉት ነቢያቶቻችሁና ምዋርተኞቻችሁ አያታልሉአችሁ፥ እናንተም የምታልሙትን ሕልም አትስሙ ። በስሜ ሐሰተኛ ትንቢትን ይናገሩላችኋልና እኔም አልላክኋቸውም ።” ኤር. 29፡8-9
“ታገኛላችሁ ፣ ይሳካላችኋል” የሚሉ ትምህርቶች “የአፍሪካ ወንጌል” በመባል ይጠራሉ ። የድሀን ሕዝብ ጆሮና ቀልቡን ለመሳብ ታገኛለህ ፣ ይሳካልሃል የሚሉ ስብከት መሰሎች የተለመዱ ናቸው ። እግዚአብሔር እንደሚሰጥ ፣ እርሱ የሥጋና የነፍስ ተንከባካቢ አንደሆነ እናምናለን ። ሰው ግን እርሱን ማመን ያለበት ስለ ህልውናው ፣ ስለ ክብሩ ፣ ስለ እግዚአብሔርነቱ እንጂ ስለ እጁ ስጦታ መሆን የለበትም ። ሃይማኖት ከራሱ ከእግዚአብሔር ጋር ያለ ግንኙነት እንጂ ከስጦታው ጋር ያለ ግንኙነት አይደለም ። ስጦታው ከሰጪው ጋር የመተባበራችን ውጤት ነው ። የተጨነቀና የማያውቅ ሕዝብ ለሐሰተኛ አስተማሪዎች ተላልፎ ይሰጣል ። አሳልፎ የሚሰጠውም የገዛ ጭንቀቱና አለማወቁ ነው ። ሐሰተኛ አስተማሪዎች የሕዝቡን የስሜት ጣቢያ እየፈለጉ የሚናገሩ እንጂ እንደ እግዚአብሔር ቃል የሚናገሩ አይደሉም ። አገልግሎትም የሚለካው በተከታዩ ብዛት ሳይሆን ያለ ተከታይም እውነት ከሆነ ብቻ ነው ። በተከታይ ብዛት የቡድሀና የሂንዱ እምነት ብዙ አማኞች አሉት ። ቊጥር የመጠን መለኪያ እንጂ የእውነት መለኪያ አይደለም ። የሐሰት መምህራን ጥንትም ነበሩ ። ባሎቻቸው የሞቱባቸውን ኀዘነተኞች አጽናኝ መስለው በመግባት ወራሽ የሚሆኑ ፣ ለተጨነቁት ሰዎች ነገ ታገኛለህ እያሉ ዛሬ በእጃቸው ያለውን የሚቀሙ ያኔም ነበሩ ። አዲስ ኃጢአትም አዲስ ጽድቅም ዛሬ የለም ።
“የቸገረው ርጉዝ ያገባል ፣ የባሰበት እመጫት” ይባላል ። አብዛኛው ወገን ከጥንቱ ጀምሮ የሚወዳጀው እነዚህን የሐሰት አስተማሪዎችና ትንቢት ተናጋሪዎች ነው ። ሰው በተፈጥሮው ስለ ነገ የማወቅ ጥማት አለው ። ይህ ከእንስሳት ልዩ የሚያደርገው ተፈጥሮው ነው ። እንስሳት ስለ ነገ የማወቅ ምንም ጉጉት የላቸውም ። ሰው ስለ ቀጣዩ የማወቅ ጉጉቱ በካርታ እንዲጠነቁል ፣ ኮከብ እንዲቆጥር ፣ ጠንቋይ ቤት እንዲሄድ ፣ አዋቂ የሚባሉትን እንዲጠይቅ ፣ ነቢያት የሚባሉትንና ያውቃሉ ተብለው የሚወራላቸውን ደጅ እንዲጠና ያደርገዋል ። የአገራችን ሰው ግን፡- “ጠንቋይ ቤት መሄድ ለወሬ መቸኮል ነው” ይላል ። ሁሉም ነገር በጊዜው ሲሆን ይታወቃልና ። ከቀኑ በፊት መስማት ልማትም ጥፋትም አለው ። ሐሰተኛ ነቢያትም ሕዝቡ ምን ይፈልጋል ? የሚለውን ያጠኑ ፣ በብልጠትም በሥነ ልቡና ጨዋታም የዳበሩና ልምድ ያላቸው ናቸው ። “የሌባ ዓይነ ደረቅ መልሶ ልብ ያደርቅ” እንዲሉ ሲያፈጥጡ ውሸት እንደሆነ ልቡ እያወቀ ሰው ይቀበላቸዋል ። በዚህም ብዙ ኑሮዎች ይፈርሳሉ ። አገኛለሁ ብለው ያገኙትን ይጥላሉ ። በመንፈሳዊ ቤት ካሉ የቁማር ጨዋታዎች አንዱ ሐሰተኛ ነቢያትና አስተማሪዎች የሚጫወቱት ነው ።
የእስራኤል ልጆች የባቢሎን ምርኮ ገና በጠዋቱ አስጨንቋቸዋል ፣ ገና ሰባ ዓመት እንደሚቀራቸው ቢሰሙም መቀበል አልፈለጉም ። ምክንያቱም የሐሰት ነቢያት በሕዝቡ ፊት ባለ ሞገስ የሚሆኑት እውነተኞቹን ካስጠሉና ካቃለሉ በኋላ ነው ። እውነተኛ አስተማሪ የነበረውን ነቢይ ኤርምያስን በጎ ከአፉ የማይወጣ ፣ ሟርተኛ ነው ብለው በሕዝብ ዘንድ አስጠልተውት ነበር ። “ሊውል ያሰበ ሆድ በጠዋት ይርበዋል” እንዲሉ ገና በጠዋቱ ወደ አገራችን እንመለሳለን ይሉ ነበር ። ይህንንም የሚያራግቡላቸው በመካከላቸው የነበሩት በአጉል ተስፋ እንደ ፊኛ ያሳበጡአቸው ሐሰተኛ ነቢያትና አስተማሪዎች ነበሩ ። “የውሸታም እንባ ባቄላ ባቄላ ያህላል” እንዲሉ ሐሰተኛ አስተማሪዎች በእንባ የሚያታልሉ ናቸው ። ስለዚህ በቀላሉ ስስ ልብ ያላቸውን ወገኖች ይማርካሉ ። ለማንም ሰው ደግ አውራ ደግ ይመጣል የሚል አስተሳሰብ አለውና እነዚህ ሰዎች በቀላሉ ተቀባይነት ያገኛሉ ። ደግ የሚመጣው ግን ደግ ሲኖሩ ነው ።
“እንኳን እህል ውኃ በበላሁ እንቆቆ ፣ አገሬ ገብቼ ሰውነቴ ታውቆ” የሚል ስንኝ አለ ። ከአገሩ የወጣ ሰው የአገሩ ክፉ አይታየውም ። ናፍቆት ጠላትን ሳይቀር ያስናፍቃል ። ብዙ እስረኞች ጠላቴ ናፈቀኝ ይላሉ ። ትልልቅ ሰዎች ውጭ አገር ሁነው ወደ አገር ቤት ደውለው የሚጠይቁት ነገር ናፍቆትን ይገልጣል ። ፀሐይ የምሞቅባት ድንጋይ ደህና ነች ይላሉ ። ይህ ናፍቆት ነው ። ናፍቆት ድንጋይን ሳይቀር ያስናፍቃል ። ታዲያ ከአገራቸው ርቀው የኢየሩሳሌም ጎዳናና ድንጋይ ሳይቀር የናፈቃቸውን እስራኤላውያንን የሚያስቱ የሐሰት ነቢያት ነበሩ ። በነቢዩ በኤርምያስ የተላለፈው መልእክት ግን እነዚህን በመስማት እንዳይስቱ ነው ። ሰው በጥሩ መማር ካልቻለ በጥሩ መቀጣት አለበት ። ቅጣቱም ትምህርት ነውና ። በባቢሎን በጅራፍ እየተማሩ ያሉት በአገራቸው በቃል መማር ስላልቻሉ ነበር ። ተማሪ ለራሱ ደውሎ ከትምህርት ቤት መውጣት ቢችል ኑሮ ብላችሁ አስቡ ። ሁለት ሰዓት ገብቶ ሁለት ተኩል ይደውል ነበር ። የሚወጣው ግን ሥልጣን ካለው ክፍል ሲደወልለት ብቻ ነው ። የመከራ ተማሪም ለራሱ ደውሎ መውጣት አይችልም ። ሲደወልለት ብቻ ይወጣል ። በእውነት እግዚአብሔር ምድራዊውን ችግር ያመጣው ዘላለማዊውን መከራ እንድናመልጥ ነው ። በሽታም በላያችን ላይ በየቀኑ ከሚበቅለውን የኃጢአት አረም ሊከላከልልን የተሰጠን ሊሆን ይችላል ። ራሳችንን ነጻ ሆነን ማየት ከባድ ነው ። ልጓም የሌላት በቅሎ ገደል ትሰዳለች ፣ መከራ የሌለበት ሥጋም ገሀነም ይከታል ።
“በመካከላችሁ ያሉት ነቢያቶቻችሁና ምዋርተኞቻችሁ አያታልሉአችሁ፥ እናንተም የምታልሙትን ሕልም አትስሙ ። በስሜ ሐሰተኛ ትንቢትን ይናገሩላችኋልና እኔም አልላክኋቸውም ።” አይጦች አብረውን ይኖራሉ ፣ የምንወደውን ነገር ያሳጡናል ። አብረውን ስለሚኖሩ መድኃኒት መሞከሪያ ይሆናሉ ። መድኃኒት ግን አይሆኑም ። የሐሰት አስተማሪዎችም ሁልጊዜ የሚኖሩት ሰው መካከል ነው ። ዓላማቸው ሰው ማትረፍ በመሆኑ ሊመንኑ አይችሉም ። ብቅ ጥልቅ እያሉ ሊኖሩ ይችላሉ ። ከሰው ግን ተለይተው መኖር አይችሉም ። ሙቀት የሚወዱና የድህነት ብርድ የሚያስፈራቸው ናቸው ። ሰው የስህተትን ትምህርት ሲመርጥ ገንዘብ ወይም ክብር እያስጨነቀው እንደሆነ እንረዳለን ። ድህነት ክፋቱ ወደ ነፍስም ወደ ቤተ ክርስቲያንም ይመጣል ። ድሀ አእምሮ ካለንም ወርቅ አንጠግብም ። ድህነት ተሰናብቶን ቢሄድም ቢመጣስ እያልን እንሰጋለን ። “እባብ ያየ በልጥ ይደነብራል” እንዲሉ ።
ምዋርተኞች ለእኛ መልካም እየተናገሩ ጠላትን በርግማን የሚገለብጡ ናቸው ። ሰይጣንን አድራሻ ያደረጉ ተግሣጾች ይሰማሉ ። በቀጥታ ወደ ሰይጣን መጸለይስ ይቻላል ወይ ? ይውደም ይወጋ የሚሉ ደርግ ጥሎት የሄደው መፈክሮች በመንፈሳዊ ቦታ በየቀኑ ሥራ ላይ ናቸው ። እግዚአብሔርን የማይፈራ ሕዝብ ሰይጣንን በመፍራት ተወጥሯል ። ሰይጣንን የምቃወመው ለእግዚአብሔር በመገዛት እንጂ የርግማን ቃሎች በማውረድ አይደለም ። ለነገሩ ሰይጣንና ጠላት በሚል ስም የምንወጋው ጎረቤቶቻችንን ነው ። እንግዲህ ለእግዚአብሔር ተገዙ፤ ዲያብሎስን ግን ተቃወሙ ከእናንተም ይሸሻል፤ ወደ እግዚአብሔር ቅረቡ ወደ እናንተም ይቀርባል።”  ያዕ. 4፡7-8 ።ዲያብሎስን የምንቃወመው ለእግዚአብሔር በመገዛት ነው ።
“እናንተም የምታልሙትን ሕልም አትስሙ” ይላል ። ዛሬ እንዲህ ታየኝ ፣ እንዲህ አቃዠኝ የሚሉ ነገሮች በመያዝ ብዙ ውሳኔ የሚወስኑ ወገኖች ነበሩ ።ዛሬ ግን እንኳን በሕልም ያዩት በውን ያዩትም እየጠፋ ነው ። የሚጸናው ምዋርትም ሕልምም አይደለም የሚጸናው በነቢዩ በኤርምያስ የተነገረው የእግዚአብሔር ቃል ነው ። ቃሉ ለጆሮ አይጥምም ። ለባቢሎናውያን ተገዙ የሚል ነበር ። ሕዝቡ ነቢዩን እንደ ባንዳ እያዩት ነበር ። ነገር ግን ባቢሎናውያንን ያመጣው የራሳቸው አለመመለስ መሆኑን አላስተዋሉም ። የእገዚአብሔርን ቃል በስሜታችን ምላስ ካጣጣምነው ነገር ይበላሻል ። ቃሉን በእውነትነቱ ብቻ በመቀበል ባይጥመንም ልናከብረው ይገባል ። የሚደንቀው ሕዝቡም የሚወደው የሚዘርፈውን መሆኑ ነው ። ለእውነተኛ አገልጋዮች ቊራሽ መስጠት እስከማይችል እጁ ተቆልፏል ። ሐሰተኞችን ሲቀልብ ግን ይኮራል ።
በምድር እንስሳትና በሰማይ አእዋፋት መካከል ትልቅ ጦርነት ተነሣ ። ጦርነቱን የምድሩ እንስሳት ሲያሸንፉ የሌሊት ወፍ በርቱ እኔ የእናንተ ወገን ነኝ ፣ እዩት ጥርሴን ትላለች ። ሥጋ በል ናትና ያምኗታል ። ጦርነቱን የሰማይ አእዋፋት ሲያሸንፉ በርቱ የእናንተ ወገን ነኝ ፣ እዩት ክንፎቼን ትላለች ። ጦርነቱ አብቅቶ ሰላምና እርቅ ወረደ ። በዚህ ጊዜ የሌሊት ወፍ ከማን ወገን ትሁን በዚህ ምክንያት በሌሊት መብረር ጀመረች ይባላል ። ዳር ላይ ቁሞ ብቅ ጥልቅ እያሉ መኖር ክርስትናን ያደክማል ። ከሊቃውንትም ከትንቢት ተናጋሪዎችም ወገን ነኝ እያሉ መኖር አንድ ቀን ብቻ ያስቀራል   ። እግዚአብሔር ሲናገር የሌሎችን ምዋርት ብቻ ሳይሆን የራሳችንን ሕልምም ማመን አይገባም ።
አምላኬ ሆይ አንተ ታየኛለህ ። ምርጫዬም በፊትህ ነው ። ዳቦ የያዝኩ መስሎኝ ድንጋይ እንዳልነክስ ፣ አንተን ያገለገልሁ መስሎኝ ለስህተት ነገር ተላልፌ እንዳልሰጥ እባክህ ጠብቀኝ ። ኑሮዬ ግራ ሲያጋባኝ የግራ መንገድ እንዳልመርጥ ፣ ስጨነቅ አጠገቤ ያገኘሁትን እንዳልይዝ የትዕግሥትን ልብ አድለኝ ። ካላሰቡበት የዋሉትን መልስ ። የቀኙን መንገድ ለሕዝብህ አሳይ ።በታላቁ እረኝነትህ ለዘላለሙ አሜን ።
የዕለቱ መና 9
ግንቦት 8 ቀን 2011 ዓ.ም.
ዲአመ ተጻፈ አዲስ አበባ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም