የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

መናኙ ወደ መናኙ ሄደ

ጌታችን ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ ሄደ ። ገሊላ ዓለም አቀፍ አስተሳሰብ የሚንጸባረቅባት ፣ የሁሉ መኖሪያ ፣ ምቹ ስፍራ ፣ ዘረኝነት የማይታይባት ፣ ደብረ ታቦር ፣ ደብረ አርሞን ያለባት ፣ ልምላሜ ዓመት ከዓመት የማይለያት ፣ የቄሣሮች መታሰቢያ ያረፈባት ፣ የምዕራቡና የምሥራቁ ንግድ የሚተላለፍባት ፣ የአንጾኪያ ጎረቤት ፣ የሊባኖስ ቡና አጣጭ ናት ። ጌታችን ከዚህች ደማቅ ከተማ ጭው ወዳለው በረሃ ፣ አንድ የእግዚአብሔር ሰውን ፍለጋ ሄደ ። ስለ ዓለም ለማወቅ ዓለምን የመነኑ ሰዎችን ማነጋገር ያስፈልጋል ። ዓለምን ካልናቅን ሰደቡኝ ተፉብኝ ብለን እንቅልፍ እናጣለን ፣ አጣሁ ነጣሁ ብለን ሞትን እንመኛለን ፣ ተሻርኩ ካባ ተቀማሁ ብለን ሕይወትን እንረግማለን ። የመነኑትን ስናይ በኑሮም በቃልም እየገሠጹ ትክክለኛውን ማያ መነጽር ይሰጡናል ። ከሰው የራቁ ከእግዚአብሔር የራቁ አይደሉም ። አገርን በጸሎት የሚጠብቁ የእምነት ሠራዊት ፣ የተደናገረ ሰው ፈቃደ እግዚአብሔርን የሚጠይቅባቸው ፣ የከፋው የሚጽናናባቸው ገዳማውያን ያስፈልጋሉ ። እነርሱ ለእኛ መጽናናት ናቸው ፣ እኛም የእነርሱን ልብ እናሳርፋለን ። ስለ እግዚአብሔር ገለል ብለው ያሉትን አባቶች ፣ በጸሎት የጸኑትን እውነተኞች መፈለግ ከጌታችን የምንማረው ነው ።

ጌታችን ገና የዕለት ጽንስ ሳለ ያወቀው የዚያን ጊዜው የስድስት ወር ጽንስ ዮሐንስ አሁንም ጌታ ሲመጣ አወቀው ። በእናቱ ማኅፀን ሳለም ፣ በሠላሳ ዓመቱም ወደ ዮሐንስ የሄደው ጌታችን ነው። ወደ እርሱ እስክንመጣ አይጠብቅም ፣ ፍቅር ቀድሞ ይገኛል ፣ ፍቅር ይፈልጋል ። ፉክክር ባለበት ፣ ኩራት ባጠላበት ፣ መፈራራት በነገሠበት ፍቅር እየከሳ ይሄዳል ። ያኔም በማኅፀን ዝምታው ዛሬም በትሕትና ዝምታው ጌታን አወቀው ። ጌታን በቃል ብቻ የሚያውቁ አሉ ፣ እውነተኛ ወዳጆቹ ግን በዝምታውም ይበልጥ ያውቁታል ፣ እርሱ በዝምታም መፍጠር ይችላል ። አሜን ክብር ምስጋና ላንተ ይሁን ! ኢየሱስ ክርስቶስ መዓዛ ቅዱሳን ነው ። መዓዛው ያውዳል ። ቃል ባይናገር ከገነት ይልቅ ያሳርፋል ። ዝም ቢል ከብዙ የፍልስፍና ቃላት ይልቅ ነፍስን ያቀናል ። አሜን!

መናኙ ወደ መናኙ ሄደ ። የእውነተኛው ክርስቲያን መልክ መናኝነት ነው ። መናኝነት ሰዋዊ ክብርን መሸሽ ፣ እዩኝ እዩኝ ማለትን መናቅ ፣ ለሌሎች መቆረስ ፣ እኔ ዝቅ ብዬ ወንድሜ ከፍ ይበል ማለት ፣ የወገንን አበሳ መደበቅ ፣ ደግ ደጉን ማየት ፣ ከባቴ አበሳ መሆን ነው ። የእኔ ነው ስንል ጠብ ይፈጠራል ። ንብረቱ የእኔ ነው ካላልን ጠብ አይኖርም ። ዝናው የእኔ ነው ካላልን ግርግር አንፈጥርም ። በእኔ ሥራ ነው የታወቁት ካላልን ለበቀል አንነሣም ። መናኝነት “ሁሉ የእግዚአብሔር ነው” ብሎ ማረፍ ነው ። ፍትሐ እግዚአብሔርና ቀን የማይገልጡት ክዳን የለም ። ከስድሳ ከሰባ ዓመት በፊት ደራሲ የተባሉ ዛሬ “የእነርሱ ሥራ አይደለም ፣ ሰርቀው ነው” ሲባል እንሰማለን ። እኛ ተኝተን አይደለም ፣ ሞተንም እውነት አትተኛም ። እውነተኛ ሰው በቁሙ ይረገማል ፣ በአጽሙ ይከበራል ። እውነተኞች አጽማቸው ይቅርታ ይጠየቃል ። በዕድሜ በዘመናቸው የማይከብሩት በትዕቢት እንዳይወድቁ ነው ። በአንድ ተግባራቸው ከተደነቁ ረክተው ይቆማሉ ። ብዙ የሠሩ ሰዎች የተነቀፉ ሰዎች ናቸው ። አመስጋኞች በትንሹ እንድንረካና እንድንቆም ሊያደርጉን ይችላሉ ። ረጅም ርቀት የማይጓዙ ሠራተኞች አንደኛ በመንቀፍ ላይ የተመሠረቱ ፣ ሁለተኛ በጥቂት ሥራቸው የገነኑ ናቸው ። “ዶሮን ሲያታልሏት ፣ በመጫኛ ጣሏት” ይባላል ። መጫኛ ለበሬ እንጂ ለዶሮ አይወረወርም ። በትንሹ ተግባር ፣ ትልቅ ክብር የሚያገኙ እንደዚህ ናቸው ። እነዚህ ሰዎች ታዲያ የኮሰሰ ትልቅ ሰው ሲያገኙ “ጥሩ ቢሠራ ይደነቅ ነበር” ይላሉ ። ዓለም የጭቃ ጅራፏን ስታመጣባቸው ፣ ቀንበሩ ከብዷቸው ይጨነቃሉ ፣ እንኳን የሠሩትን ያልሠሩትን ኃጢአት ይናዘዛሉ ።

ሰው በድዬ ነበር አድርጌ እንደ ዋዛ ፣
ቁናውም ቁናዬ ነው ዙሩ በእኔ በዛ ።

በሰፈሩበት ሳይሠፈሩ አይቀርም ። በፈረዱበት ሳይፈረድ አይቀርም ። ያውም እጥፍ መስፈሪያ ይሰፈራል ።

የጌታችን ጥምቀት ዓለምን የናቁ አገልጋዮችን እንድናከብር ፣ የሐር ወንበር ላይ የሚቀመጡትን ሳይሆን በፍጹም ድህነት የእግዚአብሔርን ሥራ እየሠሩ ላሉት ክብር እንድንሰጥ ያስጠነቅቀናል ። ንብረት አፍቃሪ መናኝ መውደድ አይችልም ። እውነተኛ ምናኔ የልብ ነው ። የእግዚአብሔር ፈቃዱ ከዓለም እንድንወጣ ሳይሆን ዓለም ከልባችን እንድትወጣ ነው ። እኛስ ይህን በዓለ ጥምቀት ስናከብር ዝቅ ብለው የሚያገለግሉትን ፣ የኑሮ ተራራ እየገፉ ያሉትን አባቶች እያስታወስን ይሆን?

እነዚህ አባቶች ፅሙደ ጸሎት ሆነው በጉዳት የሚኖሩት ለእኛ ነው ፣ አገር ካገር እየተንከራተቱ የሚያስተምሩት ወንድሞች ለእኛ ነው ! ክብር ለሚገባው ክብር መስጠት ይገባናል ። አሊያ ከጅብ ሰርግ ላይ ይጥለናል !

ጌታ ሆይ በቀደምህበት እንድንከተልህ ፣ ለእውነተኛ አገልጋዮችህ ክብር እንዲኖረን እባክህ አግዘን!

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥር 15 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ