መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » መዓትህን በምሕረትህ መልስልን

የትምህርቱ ርዕስ | መዓትህን በምሕረትህ መልስልን

መሳይ የሌለህ ብቸኛ ፣ ተመሳሳይ የሌለህ ልዑል ፣ ተቀራራቢ የሌለህ ምጡቅ ፣ የማትመረመር ምሥጢር ፣ የማትያዝ እሳት ፣ የማትወሰን መንፈስ ፣ የማትታፈን ምሉእ ፣ የማትቀየም የዋህ ፣ የማያደርጉልህ አድራጊ ፣ የማይናገሩህ የበላይ ፣ የማይከስሱህ ትክክል አንተ እግዚአብሔር ነህና አመሰግንሃለሁ ። የምድር መኸር ለአጨዳ በተቃረበበት ፣ የፍጥረት ሩጫ ሊገታ በደረሰበት ፣ የሚታየው ታጥፎ የማይታየው ሊዘረጋ መድረኩ በሚዘጋጅበት ፣ ሰው የሰውነቱን ክፋት ሁሉ ጨርሶ ለመጫረስ የመጨረሻ ቀጠሮ በያዘበት ፣ አገሩ ሰላም ነው ወይ ? የሚባልበት ጊዜ አልፎ ዓለሙ ሰላም ነው ወይ ? በምንልበት ዘመን ያለን ልጆችህ ሰላም እንልሃለን ። እየሰማን ደንቍረን ፣ እያየን ፈዝዘን ፣ ወንድም ወንድሙን ለሞት ሲያስበው መገረም አቁመን ፣ የትዳር መሠረቶች ሲናጉ የዕለት መጫወቻ ርእስ አድርገን ፣ ልጆች ያለ አሳዳጊ ጎዳና ሲወጡ እንዳላየን አልፈን ፣ የመጣውን ዕዳ ሳንከፍለው ሌላ ዕዳ እያቆየን ፣ እንደ አራዊት በመጫረስ ያሸነፈ የሚገዛበትን ዓለም ተመኝተን ፤ ልባችንን ለገንዘብ ስስ ፣ ላንተ ጠንካራ አድርገን ፣ ስለ ጸሎት እያነበብን መጸለይን አቁመን ፣ መፍትሔ እግዚአብሔር ነው እያልን በየዕለቱ ካንተ ርቀን ያለነውን ልጆችህን ስታስበን ምን አልከን ይሆን ? ለሰው ጠላቱ ቤተሰቡ የሆነበትን ፣ እርስ በርስ አሳልፈን የተሰጣጣንበትን ፣ ምስኪኖችን አፈናቅለን ፣ ችግረኞችን አይበቃችሁም ብለን ሞትን ከፍለን ፣ ከእኛ አስተሳሰብና ፍልስፍና ውጭ ያለውን ወገን መራገጫ ሜዳ አድርገን አድቅቀነዋል ፤ ይህ ሁሉ ሲሆን የማያዝነውን ልባችንን ይቅር በለው ። የሞትን ትርጉም የማያውቁ ሕፃናት ሲሞቱ ፣ ማለዳቸው ሠርክ ሲሆንባቸው ልባችን አላዘነምና ይቅር በለን ። በሽታ የዓለም ገዥ ሁኖ ድንበር የማያግደው ፣ ጠቢብ የማይመልሰው ሁኗልና በመገረፍህ ቍስል እባክህ ፈውሰን ። መዓትህን በምሕረት መልስልን ። አሜን ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ታኅሣሥ 12 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም