የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

መዳን ሥላሴያዊ ነው!

“የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ ጴጥሮስ፥ እግዚአብሔር አብ አስቀድሞ እንዳወቃቸው በመንፈስም እንደሚቀደሱ፥ ይታዘዙና በኢየሱስ ክርስቶስ ደም ይረጩ ዘንድ ለተመረጡት በጳንጦስና በገላትያ በቀጰዶቅያም በእስያም በቢታንያም ለተበተኑ መጻተኞች፤ ጸጋና ሰላም ይብዛላችሁ።” 1ጴጥ. 1፥ 1-2 ።

ሐዋርያው ስለ ሥላሴ ይናገራል። እግዚአብሔር አብን ፣ እግዚአብሔር ወልድን ፣ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስን ያነሣል ። በስም ፣ በአካል ሦስት መሆናቸውን ይናገራል ። እንዲሁም የኩነት ሦስትነታቸውን ይገልጻል። አብ ልብ ፣ ወልድ ቃል ፣ መንፈስ ቅዱስ እስትንፋስ መሆኑ የኩነት ወይም የመሆን የኋኝነት ሦስትነት ይባላል ። እግዚአብሔር አብ አስቀድሞ እንዳወቃቸው ማለት ፣ ማወቅ የከዊነ ልብ ተግባር ነው ። አብ ለራሱ ልብ ሁኖ ለወልድና ለመንፈስ ቅዱስ እወቀታቸው ፣ ማሰቢያቸው ፣ ማቀጃቸው ነውና ። ሥላሴ አንድ ፈቃድ አለው የምንለው በአብ ልብነት ነው ።

ቅዱስ ጴጥሮስ አሁንም ስለ ወልድ ይናገራል ። የደሙን መረጨት ንዝሓተ ደሙን ያነሣል። ደም የሥጋ ነው ፣ አዳኝ ደም መሆኑ ጌታችን ፍጹም ሰው ፣ ፍጹም አምላክ መሆኑን የሚገልጥ ነው። መታወቅ ፣ መረጨት ፣ መቀደስ የሚሉት ቃላት ለአማንያን ተነግረዋል። በሥላሴ መታወቅ ፣ መረጨትና መቀደስ ፍጹም ደስ ይላል ። ዓለም ሳይፈጠር በልበ ሥላሴ ታወቅን ፣ በዘመን ፍጻሜ በልጁ ደም ተዋጀን ፣ በመንፈስ ቅዱስም ተቀደስን ። ስላወቀን ሞተልን ፣ ስለሞተልን ተቀደስን። መዳናችን ሥላሴያዊ ነው ። ዮሐ. 3፡16 ። ኢየሱስ ብቻ የሚል አስተሳሰብ የሰባልዮስ ኑፋቄ ነው። ስለ ምእመናን ሲናገር የተመረጡ ይላል ። የሚገርመው የተመረጡት ተበትነዋል ፣ እንግዶች ሁነዋል ። መመረጣችን ላለመሰደዳችን ዋስትና አይደለም ። ከሰማይ አገራችን ርቀን መኖራችን እንዲታወቀን እንገፋለን ፣ እንደ ባይተዋር እንታያለን ።

በቡራኬውም ከሥላሴ ጸጋና ሰላም ይብዛላችሁ ይላል ። ጸጋ ሰው የዳነበት ምሥጢር ነው ። ሰላምም ፍሬው ነው! ጸጋ ይቀድማል ፣ ሰላም ይከተላል ። ድኅነተ ነፍስ ያላገኘ ሰው ፣ ሰላም ሊኖረው አይችልም። /ማቴ. 16፡26/ ። ጸጋ ሥሩ ፣ ሰላም ዘለላው/ፍሬው ነው ! በመቀጠል አማንያን ያሉበትን ሁኔታ ይገልጣል ። የተበተኑና መፃተኞች ይላቸዋል ። መበተናቸው አገር አጥተው መንከራተታቸው ነው ። መፃተኛነታቸው ባይተዋር መደረጋቸው ነው ። አሁን ያሉበት ሥጋዊ አድራሻ ጳንጦስ፤ ገላትያ፣ ቀጰዶቅያ ፣ እስያ ነው ። የነፍሳቸው አድራሻ ግን ልበ ሥላሴ ነው። በዚህች ዓለም እንግዳ ነኝ ብሎ መቀበል የአማኝ ወጉ ነው ! እንግዳ ምንም ቢመቸው መሄዱ አይቀርም ።

አባት እናትን ቢያጡ ሥላሴ አባት እናት ነው ። ርስት ጉልት ቢቀሙ ሥላሴ አገር ነው ። ቅ/ ጴጥሮስ ስለ ራሱ ይናገራል። የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ ይላል ። ሐዋርያ ሂያጅ ገስጋሽ ፣ መልእክተኛ ፣ የንጉሥ ደብዳቤ አድራሽ ነው ። ሐዋርያ በሥልጣን የተላከ ነው ። ሐዋርያ ጌታችንን ያየ ፣ የሰማ ነው ። የቄሣር ሳይሆን የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ መሆን መታደል ነው ።
በእግዚአብሔር አብ ታውቀናል ። ነቢዩ እንዲህ ይላል፡- “አብርሃም ባያውቀን እስራኤልም ባይገነዘበን አንተ አባታችን ነህ አቤቱ፥ አንተ አባታችን ነህ፥ ስምህም ከዘላለም ታዳጊያችን ነው።” ኢሳ. 63፡16 ። ያለመታወቅ ሕመም ለሚሰማን እግዚአብሔር ያውቀናል ። መረጨትም መንፃት ፣ የእግዚአብሔር መሆን ፣ የደሙን ማኅተም መቀበል ነው ። የሚቀድሰንም መንፈስ ቅዱስ ነው ።

“ይታዘዙ ዘንድ” ይላል ። የመታወቁ ፣ የመረጨቱ ዓላማ መታዘዝ ነው ።

ጸጋ መንፈስ ቅዱስ ከሁላችን ጋር ይሁን !

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ተጻፈ ሚያዝያ 24 ቀን 2015 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ