መግቢያ » ከመጻሕፍት » ወዳጄ ሆይ » መጻፍ የነፍስ ትግል ነው

የትምህርቱ ርዕስ | መጻፍ የነፍስ ትግል ነው

 

ወዳጄ ሆይ !

ጆሮ እያለው የማይሰማ ሳያውቅ ያወቀ የሚመስለው ነው ። ተምሮ የደነቆረና ያወቀ የሚመስለው አንድ የሚሆኑት በጥፋታቸው ነው ። ጠላት ገንዘብህን ይውሰድ እንጂ ሰብእናህን እንዲወስድ አትፍቀድለት ። መሻገርህን ሳታረጋግጥ ድልድዩን አትስበር ፣ መውጣትህን ሳታረጋግጥ መሰላሉን አትገፍትረው ። ያሻገርህንና ከፍ ያደረገህን ወገን አትርሳው ። ደራሽ ውኃ ሲመጣ ዋና መለማመድ ከንቱ ነው ። ሊሄድ የፈለገን ቆይ አትበለው ፣ አካሉ ቢቀመጥም ልቡ ሂዷልና ። ለመሻገር የፈለከው ድልድይ ለመመለስ ፣ ለመውጣት የፈለከው መሰላል ለመውረድም ያስፈልጋል ። የሄደም መመለሱ ፣ የወጣም መውረዱ አይቀርምና ሁልጊዜ በትዕግሥት ኑር ።

ወዳጄ ሆይ !

ከእግዚአብሔርና ከቃሉ ውጭ እርግጠኛ የምትሆንበት ነገር በዓለም ላይ የለም ። የተራራቁትን የሚያገናኝ ፣ የተዋረዱትን ከፍ የሚያደርግ ሰው ቡሩክ ነው ። ድልድይና መሰላል ባለውለታ ቢሆኑም በእግር መረገጣቸው ግን ይገርማል ። ስትጀምር እግርህን የገፋልህንና ስትጨርስ እጁን የዘረጋልህን አትርሳ ። ለእውነተኛ ወዳጅህ ጊዜ ካጣህ መኖርህ የባከነ ነው ። መፈራራት ባለበት ፍቅር እውነተኛ አይደለም ። 

ወዳጄ ሆይ !  

የራስህን ምሁር በባዕድ መሃይም አትቀይረው ። ያወራኸው ነገር ከልብህ እያለቀ ይመጣልና ፍቅርህንና እቅድህን አትለፍልፈው ። የወጣልህን ሎቶሪ ሳታረጋግጥ አሮጌ ልብስህን አታቃጥል ። በወረት ፍቅር የከረመ ወዳጅህን ገሸሽ አትበል ። መሬትን ለቆ የበረረ መልሱ ማረፉ አይቀርም ፣ በወረት ፍቅር ያበደም እያፈረ መምጣቱ ግድ ነው ። 

ወዳጄ ሆይ !

መጽሐፍ በሽፋን ፣ ሰው በአንድ ቀን አይታወቅም ። ሁሉም ቤት ታሪክ አለ ፣ የመዘገቡት ግን ታሪክ ይሆንላቸዋል ። አብዛኛው የዓለም ታሪክ የመገዳደል ታሪክ ነውና ቃየን ብዙ ልጆች አፍርቷል ። የተቀደደ የለበሰን ብትገፈው የምታጌጠው በተቀደደ ልብስ ነው ፣ ድሀን ዘርፈው ባለጠጎች የሆኑም ሲያፍሩ የሚኖሩ ናቸው ። እግዚአብሔር መስረቅን በትእዛዙ ሲከለክልህ ፣ መብላትን ግን በፍርድ ያግድሃል ። 

ወዳጄ ሆይ !

ጠላት እንዳይገዛብህ እሳት ልጅህን ያዘው ፣ ወዳጅ እንዲያመጣልህ ውኃ ልጅህን ላከው ። ካልቸገረህ በቀር ከሞኝ ጋር አትጣላ ። ምግብ ያለ ውኃ ፣ ትምህርት ያለ ቅንነት ፣ ጀግና ያለ ደጀን ጥቅም የላቸውም ። 

ወዳጄ ሆይ !

ያለ አቅምህና ያለ ችሎታህ ትልቅ ስድብ ከሰደቡህ እያሞኙህ ነው ። ለአቅመ መሰደብ መድረስህን ሳታረጋግጥ ሰደቡኝ ብለህ አትዘን ። በተስፋ ብቻ ከጎለቱህ በጦር ያባረሩህ የተሻለ ቦታ ያደርሱሃል ። በየሄደበት ቃል የሚገባ ካልሰጠ የሚወደድ የማይመስለው ሰው ነው ። ያልተሰጠህን ስትፈልግ የተሰጠህን ታጣለህ ። ያልደረስክበትን እውቀት ስህተት ነው ለማለት አትቸኩል ፣ የደረስክበትን ስህተት እንዳይደናቀፉ ለማያውቁ አሳውቅ ። 

ወዳጄ ሆይ !

ከሚንጫጫ ብዙ ፣ ዝም ያለውን አንድ ሰው ፍራ ። ከሚጮኸው ውሻ ፣ የማትጮኸው ግመል ብዙ በረሃ ታቋርጣለች ።  በብዕር መነጋገር ካልቻልን በጥይት እንነጋገራለን ። ያነበበ ቢተኛ እንኳ ነቅቶ የተኛ ነው ። ሳታነብ ሰው ሁሉ ከሚወድህ አንብበህ ብቸኛ ብትሆን ይሻላል ። ማንበብ የነፍስ ምግብ ፣ መጻፍ ግን የነፍስ ትግል ነው ይባላል ። ዛሬ ግን የሚታገሉት ቀርቶ የሚመገቡት ደከማቸው ።

ሰላማዊ ዘመን እዘዝልን !

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ኅዳር 20 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም