መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ማለቂያ የሌለው እኔ

የትምህርቱ ርዕስ | ማለቂያ የሌለው እኔ

 በአገር ላይ ጦርነት ተነሥቶ ዘጠኝ ባልንጀሮች በአንድነት ዘመቱ ። ጦርነቱ አይሎ ስለ ነበር ስምንቱ ሞተው አንዱ ብቻ በሰላም ተመለሰ ። የጦርነቱ ማየል ፣ የስምንቱ መሞት ፣ የአንዱ በሰላም መመለስ የሰሙ ዘመድ አዝማድ በሕይወት ወደ ተመለሰው ሰው ጋ ሄደው፡- “ለመሆኑ ጦርነቱ እንዴት ነበር ?” አሉት ። እርሱም ኮራ ፣ ደራ ብሎ “ጦርነቱ ያን ያህል አስፈሪና አስከፊ አልነበረም ፣ ዘጠኝ ሆነን ዘምተን እኔ ብቻ ተመልሻለሁ” አለ ይባላል ። 

የባልንጀሮች ፍቅር የሚኖረው አገር ሲኖር ነው ። አገር በሌለበት መፋቀርም የለም ። የባልንጀርነት ፍቅር ዘላቂ የሚሆነው የአገር ፍቅር ሲኖር ነው ። ብዙ ባልንጀሮችና ትዳሮች የአገር ሳይሆን የጎጥ ፍቅር በመምረጣቸው ተለያይተዋል ። አገር ሁሉን የሰበሰበች ጥላ ናት ። አንድነት የሚለው ቃል የሚቀጸለው ብዙዎች በአንድ አሳብ ለመስማማት ሲወስኑ ነው ። የጋራ አሳብ የሌለው ሕዝብ ይወድቃል ። አንድ ሰው አንድ ነው ይባላል እንጂ አንድነት አለው አይባልም ። አንድነት ማጣፋት ሳይሆን ኅብረት ነው ፣ መተባበር ነው ። 

ያደጉ አገሮች ለሕፃናቱ የአገርን ፍቅር ያስተምራሉ ። የቀደሙ አባቶቻቸውን መልካም ታሪክ አጉልተው ያሳያሉ ። እኛ ጋ ስንመጣ ደግሞ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው ሕፃን የሕንድ ትምህርት ቤት የሚማር ከሆነ የሕንድ ጀግኖችን ታሪክ ይማራል ። በገዛ አገሩ ተሽጦ ያድጋል ። “ድንጋይ መወርወርና አማርኛ መናገር ክልክል ነው” የሚል ትልቅ ማስታወቂያ የለጠፈ አንድ ትምህርት ቤት ከተማችን ላይ እንደ ነበር እናውቃለን  ። የምዕራባውያን ወንጌል ሰባኪዎችም “አገራችን በሰማይ ነው” በሚል ፈሊጥ ብሔራዊ ስሜት እንዳይኖር ብዙ ሥራ ሠርተዋል ። አፍሪካን የወረሩት አገራችን በሰማይ ነው እያሉ እየሰበኩ ፣ ከኋላ ጦር እያስከተቱ ነው ። ራሳችንን ጠልተን እነርሱ የለበሱትን እንድንለብስ ፣ የራሳችንን ታሪክ ደምስሰን ዛሬ እንደ ተፈጠርን ሆነን እንድናምን ብዙ ጥረዋል ። ክፋቱ የተሳካበት ስፍራም ይታያል ። ዛሬ ሁከት ያለባቸው ስፍራዎች ሁሉ ሚስዮናውያን የረገጡት ቦታ ነው ። እነርሱ ግን ሲሰብኩ በሚሰብኩበት አደባባይና አትሮኖንስ ላይ የአገራቸውን ባንዲራ ተክለው ነው ። እኛን አገራችሁ በሰማይ ነው እያሉ ባንዲራ ያስጥላሉ ፣ እነርሱ ግን ከወንጌል ጋር አጣምረው ይሰብኩታል ። በደቡብ ኢትዮጵያ የገቡ ሚስዮኖች “ከአራተኛ ክፍል በላይ መማር ኃጢአት ነው” እያሉ ይሰብኩ ነበር ። አንድ ዶክተር ይህ ስብከት ደርሶባቸው ነበርና የሚስዮኑ ልጅ ስምንተኛ ክፍል በመግባቱ በቸርች ውስጥ ጸሎት ይዘን ነበር ብለውኛል ። “የሰባኪው ልጅ ገሀነም እንዳይገባ በብርቱ እናለቅስ ነበር” በማለት አጫውተውኛል ። ሰማይን የተቀበልነው በምድር አገራችን ላይ ሆነን ነው ። ዛሬ ወንጌል ገባን በሚል ስም ምንም የአገር ስሜት የሌላቸው እንደውም ኢትዮጵያንና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አምርረው የሚጠሉ ወጣቶች እያየን ነው ። ስለ አገሩ ስለ ቤተ ክርስቲያኑ የሚናገር ከተገኘ እገሌ ይሸቃቅጣል ፣ ንጹሕ ወንጌል አይሰብክም ይላሉ ። “ኢየሩሳሌም ሆይ ፥ ብረሳሽ ፥ ቀኜ ትርሳኝ ። ባላስብሽ ፥ ምላሴ በጕሮሮዬ ይጣበቅ ከደስታዬ ሁሉ በላይ ኢየሩሳሌምን ባልወድድ” የተባለው እኮ ስለ ብሔራዊ ስሜት አይደለም ወይ ?” /መዝ. 136 ፡ 5-6 ።/ አገራችን በሰማይ ነው ያለው ጳውሎስ፡- “ብዙ ኀዘን የማያቋርጥም ጭንቀት በልቤ አለብኝ ስል በክርስቶስ ሆኜ እውነትን እናገራለሁ ፤ አልዋሽምም ፤ ሕሊናዬም በመንፈስ ቅዱስ ይመሰክርልኛል ። በሥጋ ዘመዶቼ ስለ ሆኑ ስለ ወንድሞቼ ከክርስቶስ ተለይቼ እኔ ራሴ የተረገምሁ እንድሆን እጸልይ ነበርና” ብሎ የለም ወይ ? /ሮሜ. 9፡1-3/ ። ነጠላ ለብሶ የሚያስተምረውን እያወገዝን ሱፍ ለብሶ የሚያስተምረውን ካደነቅን የፈረንጅን የኢንዱስትሪ አብዮት እያሟሟቅን አይደለም ወይ ? አገር የምንኖርላት ብቻ ሳይሆን የምንሞትላትም ናት ። 

የአገር ፍቅር የሚገባን ከአገር ስንወጣ ነው ። ፀሐይ የሞቅንባት ድንጋይ ሳትቀር ትናፍቃለች ። የአገር ዋጋ የሚገባን አገር የሌላቸውን ሕዝቦች ስናይ ነው ። ዛሬም አንድ ጥቁር አፍሪካዊ ነጭ ሲያይ ይንቀጠቀጣል ። እመቤቴ ጌታዬ ይላል ። ለነጭ የማይርገበገብ ጥቁር ሲያዩ ራሳቸው ነጮቹ “ኢትዮጵያዊ ነህ ?” ይላሉ ። የነጻነት ዋጋው ትልቅ ነው ። አፍሪካውያን የራሳቸውን ቋንቋ አጥተው የፈረንሣይና የእንግሊዝ ቋንቋ ተናጋሪ ሁነዋል ። እኛ በራሳችን ቋንቋ ስንናገር ይቀኑብናል ። እኛ ደግሞ እንግሊዝኛ ባለመናገራችን ሐፍረት ይሰማናል ። አባቶቻችን ለነጻነት ዋጋ ባይከፍሉ ኑሮ ዛሬ ስማችን የጣሊያንና የሌሎች ሕዝቦች ስም ይሆን ነበር ። ምንም ረሀብተኛ ሕዝቦች ብንሆንም የበታችነት ስሜት እንዳይሰማን አባቶች የከፈሉት ዋጋ ሊታወስ ይገባዋል ። 

ጦርነት የሚያስከፍለውን ዋጋ ስናይ ምክንያቱ ትንሽ ሁኖ እናየዋለን ። የሰው አገር ለመውረር ብለው የሚሞቱ ምክንያትና እውነት ስለሌላቸው ደስታ የላቸውም ። ፍላጎታቸው ቁሳዊ ዘረፋ ብቻ ነው ። ለነጻነታቸው የሚሞቱ ግን እውነትና ምክንያት ከእነርሱ ጋር ናትና በደስታ ይሠዋሉ ። በጽናት የሚያዋጋ እውነትና ምክንያት ነው ። እውነትና ምክንያት የሌለው ትልቅ መሣሪያ ቢይዝም አያሸንፍም ። 

በአገር ላይ አብረው የበሉ የጠጡ ባንጀሮች አገር ስትጠቃ ደግሞ አብረው ሊዘምቱ ፣ ታሪካቸውን በወርቅ ቀለም ሊጽፉ ፣ በአንድ ላይ እንደኖሩም በአንድ ላይ በክብር ሊያርፉ ይገባል ። ነጻነት የሌላቸውን ልጆች ከመውለድ አለመውለድ የተሻለ ነው ። አጋር ልጅዋን በባርነት ሳለች በመውለዷ ምንም የአብርሃም ልጅ ቢሆን ከቤት ተባሯል ፣ አገር ለቆም ሂዷል ። ከትልቅ ሰው ከመወለድ በነጻነት አገር ላይ መወለድ ይበልጣል ። አገር ስሜቱ ጥልቅ ነው ። ጣልያን ያልጨረሰውን አጀንዳ ለመጨረስ ብሔራዊ ስሜቴን ያጠፉ መሪዎች ትውልድን በሱስና በሞራል ውድቀት ተንቀሳቃሽ ሬሳ አድርገውታል ። 

ስምንቱ አልቀው የተረፈው አንዱ ከሆነ ጦርነቱ አስፈሪ ነበር ። ጦርነቱን ግን በራሱ መትረፍ ብቻ የለካው ፣ የባልንጀሮቹ ሞት ያላሳዘነው ያ ሰው ጀግና ነኝ ለማለትና እኔ ከተረፍኩ ቀላል ነው በማለት ዜናውን እንዳነበበ ሰምተናል ። ከራስ ነገር አንጻር ብቻ ቀኑን ፣ ዘመኑንና ሁኔታዎችን መለካት በእውነት አለመታደል ነው ። የችግሩን ብርታት ለመለካት የራስን ደህና መሆን አንዱ ሰሐን ላይ አውጥቶ መመዘን ራስ ወዳድነት ነው ። 

ዛሬ በወንጌል ስም እየተሰበከ ያለው ደረቅ የሥነ ልቡና ፍልስፍና ነው ። ትችላለህ ፣ እምቅ ኃይል ውስጥ አለ የሚለው የወንድነት ትምህርት ነው ። የሳይኮሎጂ ቅኝቶች የሌለ ዓለም የሚፈጥሩና ለፍላፊ የሚያደርጉ ናቸው ። ብዙ ሰው እያለቀም አስፈሪ አይደለም ማለት ፣ ወገን እየረገፈም “ያን ያህል ነው” የሚል ክርስቲያን ማትረፍ እኔነትና ወንጌል መሳይ ስብከቶች ያመጡት ጣጣ ነው ። ጌታ አልዓዛርን እንደሚያስነሣው እያወቀ አልቅሷል ። ከአርባ ዓመት በኋላ ለምትፈርሰው ኢየሩሳሌምም አልቅሶላታል ። የዚህ ሩኅሩኅ ተከታዮች እንዴት ጨካኝ ይሆናሉ ? በመከራ ሰዓት እንኳ ቤተ ክርስቲያን ስትቃጠል ፣ ምእመናን ሲታረዱ እግዚአብሔር ያጽናችሁ ለማለት አለመቻላቸው ያሳዝናል ። እንዲህ ዓይነት ስሜት በውስጣችን ካለ መመርመርና ማውጣት ይገባናል ። ክርስቲያን ለመሆን መጥተን ሰብአዊነትም ከተለየን አስቸጋሪ ነው ። 

የሱነም ሴት ደህና ነው ያለችው ለእግዚአብሔር ሰው ለመንገር እየገሰገሰች ነው ። በሞተ ተስፋዋ ላይ ልጅ የሰጣት እግዚአብሔር በሞተው ልጇ ላይ ሕይወት እንደሚሰጥ ስላመነች ነው ። ለማይመለከተው ሰው ደህና ነው አለች ። የሞት ነገር የሚመለከተው እግዚአብሔር ብቻ ነው ። ለእርስዋ ኤልሳዕን ማግኘት እግዚአብሔርን እንደ ማግኘት ነበር ። ዛሬ ያለው ስሜት አልባነት ፣ አዘኔታ የራቀው መንፈሳዊነት እንደገና መፈተሸ አለበት ። እኛ ተርፈናል ፣ ስለሞቱት ግን ማሰብ ፣ ምን እንሥራ ማለት ያስፈልገናል ። እኛ ስንጠግብ ሌሎች በረሀብ ቢረግፉም “ያን ያህል ከባድ አይደለም” ማለት ራስ ወዳድነት ነው ። ብዙ ነገሮች እኔ ከሚለው መለኪያ አልወጡምና ማዘን አልቻልንም። የሌሎችን ሞት እያቃለልን የእኛን ጉንፋን እናብራራለን ። ማለቂያ የሌለው እኔ ! 

ጌታ ሆይ ስለ ሌሎች የማስብበትን ፍቅር ስጠኝ ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ነሐሴ 20 ቀን 2012 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም