መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ማዳን መዳን ነው

የትምህርቱ ርዕስ | ማዳን መዳን ነው

October 6, 2021 by ዲያቆን አሸናፊ መኮንን

ማዳን መዳን ነው

“የወንድሙ ሞት ወንድሙን ካልከፋው ፣

ቅበሩት ከደጁ በድኑ እንዲከረፋው ፤”

የሰው ልጅ ከወደቀው አዳም የወረሰው ጠባይ እኔነት ነው ። እኔ ብቻ ልኑር ፣ እኔ ብቻ ይድላኝ ፣ ለእኔ ያልሆነ ዓለም ይደምሰስ ፣ እኔ ከሌለሁ ሁሉም ነገር አይኑር የሚል ራስ ተኮር ሕይወት የአሮጌው ሰው ማንነት ነው ። የሰው ልጅ ራሱን በእኔነት አጥር አስሮ የሚሰቃይ ፍጡር ነው ። የእርሱ ቤተሰብ ፣ የእርሱ ወገን ካልወደቀ ዓለም ሰላም ነው ብሎ የሚያስብ ነው ። በሌሎች ጫማ ውስጥ እግሩን አስገብቶ ማዘንና መጸለይ አይሆንለትም ። ስለተሰቀለው ክርስቶስ መናገር ቀላል አይደለም ። ራሱን ስለሌሎች ሕይወት አሳልፎ የሰጠ ነው ። ክርስትና ሌሎች እንዲኖሩ እኔ ልሙት ከሚል ወግ ወጥቶ እኔ እንድኖር ሌሎች ይሙቱ ወደሚል አስተሳሰብ ከወረደ ከባድ ነው ። ሲጠሩት ቀላል ፣ ሲቆጠሩትም ሁለት ፊደል የሆነው “እኔ” ለብዙ ውጥንቅጦች መነሻ ነው ።

በሌላው ቍስል ያማል ወይ ? ብሎ እንጨት የሚሰድድ ፣ እኔ ቆሜአለሁ አልወድቅም ብሎ የሚያስብ ፣ ከትላንት ዕድለ ቢሶች መማር የማይችል እኔነት ነው ። በሰው ቦታ ሁሉም ሰው መሆኑን እግዚአብሔር በሰጠው ዕድል ሰዎችን ታዝቦአል ። እንዴት እንዲህ ይደረጋል ? ሲል የነበረ ሰው ያንን በእጥፍ ያደርገዋል ። ጊዜውን ሲቀበል በቅን ከመፍረድ በግፍ ይፈርዳል ። /መዝ. 74፡2 / ይህችን ዓለም የሚታደጋት የክርስቶስ ልብ ያለው ነው ። እኔነት ግን በክርስቶስ ልብ ላይ ጦር የሚወረውር ነው ። ክርስቲያን በጨከነበት ዓለም ፣ ዓለማውያን የበለጠ ሊጨክኑ ይችላሉ ። እኔነት እኔን ካልነካኝ ምን አገባኝ ? ባይ ነው ። እኔነት በራስ ዙሪያ መታሰር ነውና ነግ ለእኔ ብሎ አያስብም ። ሕይወት የመዝራትና የማጨድ ሕግ ናት ። ጭካኔን ከዘራን ጭካኔን እናጭዳለን ።

“አሽሟጣጭ ዝናብ ወንዝ ዳር ያካፋል” ይባላል ። ብዙ ደረቅ ምድር ፣ ብዙ በረሃ ፣ ብዙ ዋዕይ ፣ ብዙ ቃጠሎ ባለበት ትቶ ዘባች ዝናብ ወንዝ ዳር ያካፋል ። በሚመሰገንበት ሳይሆን በማያስፈልግበት ቦታ ይዘንባል ። ድሆችን ትቶ ለባለጠጋ የሚደግስ ፣ ደካሞችን ረግጦ የጉልበተኞችን ክንድ የሚደግፍ ፣ ተስፋ ያጡትን ትቶ ለሚዘሉት ምንጣፍ የሚያነጥፍ ፣ የሚያለቅሱትን ቸል ብሎ የሳቅ ኮክቴል ለሚያዘጋጁት መድረክ የሚያሳምር እኔነት የተባለው የሰው ጠባይ ነው ። እኔነት የሌለውን ሰው አይወድም ፣ ላለው ግን ያረግዳል ። የሚያለቅስን አይፈልግም ፣ ለሚቦርቅ መስክ ይደለድላል ። እኔነት የኋላውን የማያስብ ተላላ ነው ። ቀን ከፍቶበት የተሰቀቀበትን ዘመን ረስቶ ቀን ለከፋበት ይጨክናል ። እግዚአብሔር ክፉ ቀንን የሚያሳየን ቀን ለከፋባቸው ሩኅሩኅ እንድንሆን ነው ። ይገባዋል ብለን የፍርድ ማረጋገጫ እንድንሰጥ አልተጠራንም ። “እኔን አድነኝ” ብለን በምናየው በምንሰማው እንድናለቅስ ተጠርተናል ። የሚያለቅሰውን ትተን የሚመታውን ማባበል ፣ ምስኪኑን ረስተን ለጠገበው መዘመር የእኔነት ጦስ ነው ። ራሳችንን የምናጣው ራሳችንን ስናመልከው ነው ። እንኳን የሰው ሞት የውሻ ሞትም ያሳዝናል ። እኔነት ግን ከእኔ ቤተሰብ አልሞተም ብሎ የሞት መረጃ ያስሳል ።

“የእብድ ገላጋይ ድንጋይ ያቀብላል” ይባላል ። ጨዋ ገላጋይ ሰይፍን ማረሻ ፣ ጦርን ማጭድ ያደርጋል ። የእብድ ገላጋይ ግን ማረሻን ሰይፍ ፣ ማጭድን ጦር ያደርጋል ። የእብድ ገላጋይ የበዛበት ይህ ዘመን የሚያበርድ ሳይሆን የሚያጋግል ፣ የሚጸልይ ሳይሆን ጭር ሲል አልወድም የሚል ብዙ ፀላዔ ሰናያትን አፍርቷል ። ቀድመው ባያስተምሩ ዘግይተው እንኳ እንዳያስታርቁ ካህን ደመኛ ፣ መምህራን ጠብ ዘሪ ሁነዋል ። በእብድ ገላጋይ የቤተ ክርስቲያንና የአገር አንድነት ፈተና ውስጥ ገብቷል ። አዎ ያልፋል ። የሚያሳልፈው ክቡር ነገር እንዳለም መረዳት ያስፈልጋል ። የተወረወረው የሚያልፈው ዝቅ ብለን ስናሳልፈው ነው ። እገሌ ሞተ ሳይሆን ይህን ያህል ሰው ሞተ የሚባለው ሰው ቍጥር የሆነበት የእኛ ዘመን ነው ።

ሌላ ትርፍ አገር ያለን ይመስል አንድ አገራችንን ጎድተናታል ። ምዕራባውያን በዐረብ አገራት ላይ ባደረጉት እየቆጨን እኛ የገዛ አገራችን ላይ ጨክነናል ። ስለሚሞተው ስለሚፈናቀለው የሚሰማን እንደ ክርስቲያን ነው ወይ? ብለን ራሳችንን መጠየቅ ይገባናል ። “ፀጉራም ውሻ አለ ሲሉት ይሞታል” ይባላል ። እንደ ፀጉራም ውሻ መክሳታችን ፣ መጎዳታችን አልታወቀ ይሆናል ። ለማንም በሞቱ ሳይሆን በሕመሙ ብንደርስለት ባለ ትርፍ ነን ። የዕለት ነዋሪ የሆነው ከተሜው ፣ መብላትና መዝፈንን ትቶ ለሚሰደዱትና ለሚሞቱት ወገኖቹ ማዘን ያስፈልገዋል ።

እዚያ የሚሞተው ፣ የሚፈናቀለው ወንድሙ መሆኑ ሊሰማው ይገባል ። ስለሚሞት ሰው ለማመን ሬሳ መገነዝ ፣ ስለሚፈናቀል ሰው ለማዘን ስደተኛ ማነጋገር አያስፈልገንም ። ደግሞም “እንጨት ካልነሡት እሳት አይጠፋምና” ጠብና ጦርን የምንዘራ መሆን አይገባንም ። ስለ እርቅና ስለ ፍቅር አሁንም ደግመን ዋጋ መክፈል ይገባናል ። የሰው ልጅ ኑሮ የተሳሰረ ነውና በሩቅ ያለው ጉዳት እኛንም ዋጋ ያስከፍለናል ። እንኳን የቅርቡ ወንድማችን የሶርያ መፍረስ እኛንም ጎድቶናል ። በምድራችን ላይ ያሉ ስደተኞች አገራቸው ሰላም ሆኖ ቢመለሱ በብዙ እናተርፋለን ። ዛሬ እየዘፈንን የምንናገረው ጠብ ነገ እያለቀስን የምንኖረው ይሆናልና ጥንቃቄ ማድረግ አለብን ።

ለሞተ ሰው ለማዘን የሟቹን ማንነት ማወቅ አያሻንም ። ሰው ሞቷልና የተፈጥሮ ጓዳችንን መውደቅ እያሰብን ማዘን ይገባናል ። የሚፈናቀልን ለመቀበል ማንነቱን መጠየቅ አያሻንም ። እንግዳ ተቀባይ የነበረው አሁን ስደተኛ በመሆኑ ልንቀበለው ይገባል ። የዚህ ዓለም መልክ ተለዋዋጭ ነውና እንዳለን የምንኖር ከመሰለን ሞኞች ነን ። ክፋት ማስቆም ባንችል መቀነስ ይቻላል ። ለዚህም የሁላችን የቅንነት ምላሽ ያስፈልጋል ።

ጌታ ሆይ ያንተን የርኅራኄ ልብ አድለን ።

የብርሃን ጠብታ 12

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

መስከረም 26 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም