መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ምክር ለሰሚው » ምክር ለሰሚው /3

የትምህርቱ ርዕስ | ምክር ለሰሚው /3

ወዳጄ ሆይ !

አብረኸው ያደግኸውን ሰው አትርሳ ፣ የመጀመሪያው ንስሐ አባትህ እርሱ ነው ። አብረህ ጉዞ የጀመርከውን ሰው ታግሠህ ፈጽም ፣ የማትታገሠው ወገን የለምና ። አብረህ ያገለገልከውን ሰው አክብር ፣ በከበረው እርሻ ላይ ቆማችኋልና ። አብረህ የዘራኸውን በኅብረት እጨድ ፣ ሲካፈል የሚጣላ ሌባ ነውና ።

ወዳጄ ሆይ !

የቻለ ሰው ስታይ ያስቻለውን ጌታ አስብ ። ባቃተህ ነገር ላይም ክርስቶስ የበላይ መሆኑን እመን ። እንደ እመቤታችን መጠየቅ ተገቢ ሲሆን ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለም ብሎ ማረፍ ደግሞ እምነት ነው ። ጠይቆ ብቻ መቅረት ፣ አምናለሁና ጥያቄ ኃጢአት ነው ብሎ መፍራት ተገቢ አይደለም ።

ወዳጄ ሆይ !

በብርቱ ጥረህ ያገኘኸውን ነገር አትተወዉም ። በቀላሉ ያገኘኸው በቀላሉ ይባክናልና ልፋትህን ውደደው ። ጣዖት እንዳይሆንብህ እግዚአብሔር የሰጠህ ነገር ቢጠፋ ምን እሆናለሁ  አትበል ። ጸጋው ቢሄድ ባለጸጋው አለና ። መንገድ በመራህ ሰው ላይ መንገድ አትዝጋ ። ባስጠለለህ ሰው ላይ በሩን ቆልፈህ አትቀመጥ ። እኔ ተሻግሬአለሁ ብለህ እየመጣ ባለው ትውልድ ላይ ድልድይ አታፍርስ ። ብርሃንህ ጨለማ እንዳይሆን ከእኔነት ተላቀቅ ። ተመልክተህ እርገጥ እንጂ ረግጠህ አትመልከት ። ምንም ደፋር ብትሆን እግዚአብሔር ያከበራቸውን አታቃልል ። ያልገባህ ነገር ውሸት እንደሆነ አታስብ ።

ወዳጄ ሆይ !

የዓለም ታሪክ ሁሉ ጥሩ ስትሆን ክፉ ምላሽ እንደሚገጥምህ የሚናገር ነው ። ጥሩነትህ በሰዎቹ ሳይሆን በምክንያትህ ላይ የተመሠረተ ይሁን ። ከምክንያትም እምነት ጥሩ ሲያሠራህ ዋጋህን በሰማይ ትጠብቃለህ ። ያጽናናኸው ቢያቆስልህ የክርስቶስን የተቸነከሩ እጆች አስብ ። ያረጋጋኸው እንደ ሳኦል ጦር ቢወረውርብህ ዳዊት ልብህን ጎንበስ በል በለው ። ዝቅ ብለህ ጦሩን የምታልፈው ከሆነ ደረትን መስጠት ጀግንነት አይደለም ። ዘወር ስትልም ሰውዬውን ከገዳይነት ታድነዋለህ ። እችለዋለሁ የምትለው ሰው ሲበረታብህ አትደነቅ ። ትላንት ጊዜው ያንተ ነበረ ፣ ዛሬ ደግሞ የእርሱ ሁኗልና ዓለም ተራ መሆኑን ተረዳ ። ከሁሉ በላይ “የናቁት ያደርጋል ዕራቁት” የተባለውን አትርሳ።

ወዳጄ ሆይ !

በንጉሥ ፊት ባዶ እጅ መቅረብ ነውር ነውና ወደ ሰማይ ስትሄድ መክሊትህን እንዳተረፍህ አረጋግጥ ። ሕይወት ገበያ ናትና ለማግኘትም ለማጣትም ተዘጋጅ ። በምትሠራበት ዕድሜ ተቀምጠህ ፣ በማትሠራበት ዕድሜ መውጣት ፤ በሚቻልበት ጊዜ ተኝተህ በማይቻልበት ሰዓት መንቃት ትርፉ ቁጭት ብቻ ነው ። እግዚአብሔርን ቅጥር ሳታደርግ ከሰው ጋር አትጣላ ። በክንዱ የዘመተ በእግዚአብሔር ይሸነፋል ፣ በእግዚአብሔር ኃይል የወጣ ግን ማንም አያሸንፈውም ።

ወዳጄ ሆይ !

ዕፀ በለስ ለሞት በቂ ነበረ ብለህ ካመንህ ፣ ሥጋ ወደሙ ለሕይወት በቂ መሆኑን እመን ። እንዴት በሥጋ ወደሙ አትበል ፤ እንዴት በዕፀ በለስ አላልህምና ። መናፍቅነት አንዱን ጥሎ አንዱን አንጠልጥሎ ነው ። በአዳም መሞትህን ተቀብለህ በክርስቶስ መዳንህን ካልተቀበልህ እምነትህ ሙሉ አይደለም ። ለበደለ አዳም የካሰ መድኃኔ ዓለም ሊያስደንቅህ ይገባል ። ከፊት ለፊት ያለው ዘመን ክርስቶስ የሚመጣበት ፣ የመንግሥተ ሰማያት ርስት የሚከፈትበት ነውና የሚመጣውን አትፍራ ። ሁሉም የእኔ መድኃኔ ዓለም ሲለው ለሁሉ የሚበቃ ጌታ አለህና ደስ ይበልህ !

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ሚያዝያ 14 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም