መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ምክር ለሰሚው » ምክር ለሰሚው /34

የትምህርቱ ርዕስ | ምክር ለሰሚው /34

ወዳጄ ሆይ!

የተገፉ ነገሥታት ፣ ያጽናኑ ወዳጆች ፣ የተዳፈነ ፍትሕ ፣ የሰዎች መልካምነት ፣ የወላጆች ደግነት ተደብቀው የማይቀሩ ሐቆች ናቸው ። በህልውናቸው የተወቀሱ በሞታቸው የተመሰገኑ መሪዎች ብዙ ናቸው ። በቍስላችን ስፌት የሚለማመዱትን ስናይ ያጽናኑንን ነገር ግን የረሳናቸውን እነዚያን የጨለማ መብራቶች እናስባለን ። ለጊዜው ሐሰት ያሸነፈ ቢመስልም ለዘላለም የሚያሸንፈው እውነት መሆኑን በግፈኞች ውርደት እንማራለን ። መልካሞችን የምናውቃቸው ካለፉ በኋላ መሆኑ የዓለምን ስቃይ በእጥፍ እንዲጨምር አድርጎታል ። ወላጆችንም ምን ያህል እንዳሰቃየናቸው ስንወልድ ይገባናል ፣ ውለታ ለመክፈል ስንዘጋጅ ግን እነርሱ አልፈው ይሆናል ። እግዚአብሔር በዚህ ብሩህ ሰማይ ላይ የተቀመጠው የተደበቀውን እውነት ሊያወጣ ነው ።

ወዳጄ ሆይ!
ዛሬ ላይ የተደላደሉ ፣ ለዘላለም የሚኖሩ መስሎህ አትፍራ ፣ ፀሐይም ትጠልቃለችና ። ጨርሶ አይጨልምምና ባጣኸው ነገር ውስጥ ያገኘኸው አስብ ። ክፉዎች ከሚወስዱብህ የሚሰጡህ ትምህርት ይበልጣል ። ከደጎች ይልቅ ጨካኞች ጉዞህን በማስተዋልና በጥንቃቄ እንድታደርግ ያስተምሩሃል ። የምቾት ቀጠናህ ሲነካ መብረር ትጀምራለህ ፣ ገፊ አድራሽ ነው ። እውነት ማር አይደለችምና አትጣፍጥም ፣ እየመረረች ግን ታድናለች ።

ወዳጄ ሆይ!
ያለ እውነት ፍቅር ሽንገላ ፣ ደግነት ማስታወቂያ ፣ ንግግር ቅጥፈት ፣ ትምህርት የተሳሳተ መረጃ ፣ ጥበብ ዝሙት ፣ ጉዞ ግብ የለሽ ፣ ጾም ረሀብ ፣ የሃይማኖት ልብስ ግብዝነት ነው ። የእግዚአብሔር ዙፋን እውነት ነውና ሥራህን በእውነት ሥራ ። በመጀመሪያ ቀን ግንኙነት የሰውን ጨዋነትና ደግነት አወቅሁ አትበል ። ሰው እንደ መጽሐፍ ነው ። ቀጣዩን ገጽ ካልገለጥከው መጽሐፍን አታውቀውም ፣ እያንዳንዱ ቀንና አጋጣሚም ሰውን በጥቂቱ የሚገልጠው አደባባይ ነው ። እስክትሞት ድረስ እንኳን የሰውን የራስህንም የማታውቀው ጠባይ አለ ። ሰው ታውቆ የማይጨረስ ፍጡር ነው ።

ወዳጄ ሆይ !
በፍቅር የጀመረው የሰው የሕይወት ጉዞ የሚጠናቀቀውም በፍቅር ነው ። ፍቅር ትግሎችን ያቀላል ። እግዚአብሔር የጻፈው ሕይወትህ ርእሱ “መልኬ” የሚል ነው ። መቅድሙ ትእዛዜን ጠብቅ ፣ መግቢያው ኅብረት አስፈላጊ ነው የሚል ነው ። ምዕራፉ ለሌሎች ኑር ፣ ማጠቃለያው የዘላለም ቤት ደርሰሃል የሚል ነው ። እንዲህ የጻፈልህን አምላክህን አመስግን ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የካቲት 26 ቀን 2017 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም